TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#PressRelease

በአማራ ክልል ከ 2014 የጥምቀት በዓል አከባበር ጋር ተያይዞ በእስልምና ተቋማት ላይ የተፈፀሙ ሃይማኖታዊ ትንኮሳዎችን በተመለከተ የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት መግለጫ አውጥቷል።

በ2014 በተከበረው የጥምቀት በዓል በበርካታ ቦታዎች ህዝብን ለግጭት የሀገርንም ሰላም የሚያናጋ ትንኮሳ ተካሂዷል ብሏል።

ምክር ቤቱ በመግለጫው ላይ ፦

- ጥር 10 ከቀኑ 8 ሰዓት በባህር ዳር ከተማ የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ግንብ አጥር በከፊል መፍረሱን ፣ በተጨማሪ በወቅቱ በነበሩት የምክር ቤቱ ሰራተኞችና የመላውን ሙስሊም ህብረተሰብ ክብረነክ ስድብ በመስደብ ግጭት ለማስነሳት ሙከራ መደረጉን ፣

- በመሸንቲ ከተማ የሙስሊሞች የበዓል ማክበሪያ ቦታ ላይ መስቀል መትከል

- በተመሳሳይ ቀን በባህር ዳር ከተማ አባይ ማዶ በሚኖሩት ትልቅ የሙስሊም አባት ሼኽ አደም ሼኹ የመኖሪያ ቤት በድንጋይ መደብደብ

- በተመሳሳይ ቀን በጎንደር ቀበሌ 18 በሚገኘው ነስረላህ መስጂድ አጥሩ እና ጣሪያው በጥይት መመታት፣

- በተመሳሳይ ጥር 10 በሰ/ጎንደር ዞን ደባርቅ ከተማ ከበርካታ እንግልት በኃላ የተፈቀደውን መሥጂድ ቦታ ድንኳንና መስቀል ካላስቀመጥን በማለት ከፀጥታ አካላት ጋር ግጭት መፍጠር ፣

- ጥር 11 ከቀኑ 10 ሰዓት በደሴ ከተማ በሚገኘው አረብ ገንዳ መስጂድ ሙስሊሞች በሶላት ላይ ባሉበት ሰዓት መስጂድ በጥይት መደብደብ ፣

- በተመሳሳይ ቀን በቡሬ ከተማ በሙስሊሞች የመካነ መቃብር ላይ መስቀል መትከል፣ በደ/ሜጫ ወረዳ መራዊ ከተማ የመቃብር ቦታ ላይ መስቀል መትከል ትንኮሳዎች ተፈፅመዋል ብሏል።

ምክር ቤቱ የሁላችንም ወኪል ነው ብለን እምነት የጣልንበት የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ከሰሞኑ ከጥምቀት በዓል ጋር በተያያዘ ስለተፈጠረው ችግር አዲስ አበባ ላይ በመታጠር የሰጠው መግለጫ ጉባኤውን የአንድ ወገን ብቻ ጉዳይ አስፈፃሚ ሆኖ እንደተመለከተው ገልጿል።

የምክር ቤቱ ስራ አስፈፃሚ በቀን 16/5 /2014 ባካሄደው ስብሰባው በተፈፀመው ሃይማኖታዊ ትንኮሳ ዙሪያ የተለያዩ አቅጣጫዎችን ማስቀመጡን አሳውቋል።

ይኸውም ፦

- የተፈፀሙት ድርጊቶች በእምነቱ እና አማኞች ሰብዓዊ መብት ላይ ያነጣጠሩ ፣ በሰላም የሚኖረውን ህዝብም ለግጭት የሚዳርግ በመሆኑ በጥብቅ አውግዞ አጥፊዎች በህግ እንዲጠየቁ ጠይቋል።

- በባህር ዳር ከተማ የክልሉ ምክር ቤት ግንብ አጥር ሲፈርስ በእለቱ የነበሩ ለአካባቢው ጥበቃ ስምሪት የተሰጣቸው የፖሊስ እና ሚሊሻ አባላት በዝምታ የተመለከቱ በመሆናቸው በስምሪታቸው መርሃግብር መሰረት እንዲጠየቁ።

- የአማራ ክልል መንግስት እና በየደረጃው ያለው አስተዳደር በእስልምና ተቋማት እና አማኞች ላይ በተደጋጋሚ የሚፈፀሙትን ሃይማኖታዊ ትንኮሳዎች አደጋውን አርቆ በማሰብ ህግ የማስከበር እና ወንጀለኞችን በህግ አግባብ እንዲታረሙ በማድረግ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ሲል ጠይቋል።

@tikvahethiopia
" ... የሀገሪቱን ጥቅም የሚያስቀድም ምክንያታዊ ድርድር ይካሄዳል ብለውናል " - አቶ መስፍን ተገኑ

ጠ/ሚ ዶ/ር ዐቢይ አህመድ መንግስታቸው ከህወሓት ጋር የተኩስ አቁምን በተመለከተ እንደሚደራደር መናገራቸውን አሶስየትድ ፕሬስ አንድ የዳያስፖራ ቡድን ሊቀ መንበርን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።

የዳያስፖራ ቡድን አባላት ከጠ/ሚ ዶክተር ዐቢይ አህመድ ጋር ባካሄዱት የግል ውይይት ከትግራይ ኃይሎች ጋር ተኩስ አቁምን የተመለከተ ድርድር ይካሄዳል ሲሉ ዶ/ር ዐቢይ እንደነገሯቸው የአሜሪካን ኢትዮጵያውያን ህዝባዊ ጉዳዮች ኮሚቴ ሊቀመንበር መስፍን ተገኑ ለአሶሼትድ ፕሬስ ተናግረዋል።

የቡድኑ አባላት ከዶ/ር ዐቢይ ጋራ ቅዳሜ ዕለት ለ5 ሰዓታት መነጋገራቸውን የገለጹት አቶ መስፍን ተገኑ ፣ ዶ/ር ዐቢይ የሀገሪቱን ጥቅም የሚያስቀድም ምክንያታዊ ድርድር ይካሄዳል ማለታቸውን ጠቅሰዋል።

ባለፈው ሳምንት ኢትዮጵያን የጎበኙት የአሜሪካን ልዩ ልዑክ አምባሳደር ዴቪድ ሳተርፊልግ ስለሂደቱ ሃሳብ ሳይኖራቸው እንደማይቀርም ገልጸዋል።

ሁለቱ ወገኖች እንዲደራደሩ ዓለም አቀፍ ጥረቶች እየተደረጉ ቢሆንም ዶ/ር ዐቢይ ግን ድርድር እንደሚካሄድ በይፋ ተናግረው አያውቁም።

ጦርነቱ ከተጀመረ በኋላ የኢትዮጵያ መንግሥት ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት)ን አሸባሪ ሲል መፈረጁ የኢትዮጵያን መንግስትና ህወሓትን ወደ ድርድር ማምጣትን ፈታኝ አድርጎት ቆይቷል።

የህወሓት ኃይሎች ወደ ትግራይ ካፈገፈጉ በኋላ መንግስት ትግራይ ላለመግባት መወሰኑ አቶ መስፍን ፣ የበርካታ ኢትዮጵያውያንን ፍላጎት የሚጻረር ነበር ሲሉ ተናግረዋል።

በዚህ ምክንያት ኮሚቴያቸው በጉዳዩ ላይ ከመንግስት ጋር ለመነጋገር ጠይቆ የዶ/ር ዐቢይ ምክትል ወይም የጽህፈት ቤታቸው ሃላፊ ያነጋግሩናል ብለው ሲጠብቁ ዶ/ር ዐቢይ ራሳቸው መጥተው እንዳነጋገሯቸው ተናግረዋል።

በዚሁ ወቅት ዶ/ር ዐቢይ " ወደ ትግራይ ክልል አለመግባት የትግራይ ህዝብ ለተዋጊዎቹ ስለሚሰጠው ድጋፍ ቆም ብሎ እንዲያስብ የሚያስገድድ እንደሚሆንና ለመንግሥትም ጊዜ እንደሚሰጥ " ነግረውናል ብለዋል።

ከጠቅላይ ሚኒስቴር ፕሬስ ሴክሬተሪያት ቢልለኔ ስዩም ሆነ ከህወሓት ቃል አቀባይ ጌታቸው ረዳ አስተያየት ለማግኘት ቢሞክርም እንዳልተሳካላት አሶሼትድ ፕሬስ በዘገባው አስፍሯል።

@tikvahethiopia
#DrTedrosAdhanom

በዓለም አቀፍ ደረጃ ለኢትዮጵያ እጥብቅና በመቆም ሚንቀሳቀሰው የተቆርቋሪ ኢትዮጵያውያን ማህበር ፥ የዓለም ጤና ድርጅትን መርህ በመጣስ ይንቀሳቀሳሉ ባላቸው የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ላይ አቤቱታ ቀረበ።

ማህበሩ ለዓለም ጤና ድርጅት ስራ አስፈጻሚ ቦርድ የዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖምን ህገወጥ እንቅስቃሴ በተመለከተ ደብዳቤ ጽፏል።

በደብዳቤው ዳይሬክተሩ የድርጅቱን መርህ በመጣስ ከሙያ ስነ ምግባር እንዲሁም ከገለልተኝነት ውጪ እየፈጸሙት ስለሚገኘው ከስነምግባር ውጭ የሆኑ ተግባራት አስረድቷል።

ዶ/ር ቴድሮስ የሚያካሂዱትን ህገ ወጥ ተግባር የተ.መ.ድን ታማኝነት ጥያቄ ውስጥ የሚከት መሆኑን አመልክቶ በኢትዮጵያ መንግስት በአሸባሪነት የተፈረጀውን ድርጅት ሽፋን በመስጠት በሚያከናውኑት ተግባር ላይ ምርመራ እንዲደረግ አቤቱታ አቅርቧል።

#ENA

@tikvahethiopia
" ... ህወሓት በከፍተኛ ደረጃ ሀይል እያሰባሰበና ሊወጋ እየተዘጋጀ መሆኑን የሚያሳዩ እንቅስቃሴዎች እያደረገ ነው " - አቶ ግዛቸው ሙሉነህ

የአማራ ክልል መንግስት ህወሓትን ማጥፋት ካልተቻለ የኢትዮጵያ ስጋት ሆኖ መቀጠሉ አይቀሬ ነው አለ።

የክልሉ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ግዛቸው ሙሉነህ ለአሀዱ ቴሌቪዥን በሰጡት ቃል " አሸባሪውን የሕወሓት ቡድን ተባብሮ ሙሉ በሙሉ ማጥፋት ካልተቻለ የኢትዮጵያ ስጋት መሆኑን ይቀጥላል " ብለዋል።

ቡድኑ አሁንም በአማራ ክልል የተለያዩ ስፍራዎች ላይ በየቀኑ ጥቃቶችን እየሰነዘረ ንፁሃንን እያሰቃየና እየገደለ ነው ሲሉም አቶ ግዛቸው ከሰዋል።

አክለው ፥ "በማይፀብሪ ፣ አዳርቃይ ፣ ቆቦ ፣ኮረም ፣አላማጣ በየቀኑ ጥቃት የሚሰነዝርባቸው እና ከጦርነት አርፈው የማያውቁ አካባቢዎች ናቸው። ቡድኑ በእነዚህ አካባቢዎች አሁንም ፍላጎት እንዳለው ያሳያል " ብለዋል፡፡

ዳይሬክተሩ ፤ ህወሓት በከፍተኛ ደረጃ ሀይል እያሰባሰበና ሊወጋ እየተዘጋጀ መሆኑን የሚያሳዩ እንቅስቃሴዎች እያደረገ እንደሆነም አመልክተዋል። አሁንም ልክ እንደ በፊቱ በሀሰት ትርክቱ እያሳመነ እንዲሁም እያስገደደ የትግራይ ህዝብን እያሰለጠነ እና እያዘመተ ነው ብለዋል፡፡

አሁን ባለዉ ሁኔታም ወረራ ለመፈፀም የተለያዩ ሙከራዎችን ቢያደርግም እንዳልተሳካለት እና ለሌላ ጥቃት እየተዘጋጀ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

ይህ ኃይል እስካልከሰመ ድርስ አርፎ የሚተኛ አይደለም ያሉት ዳይሬክተሩ እሰካሁንም ሽንፈቱን አምኖ ያልተቀመጠ እና ከስህተቱ የማይታረም መሆኑን እያሳየ ነዉ ብለዋል ለቴሌቪዥን ጣቢያው።

ምንጭ፦ አሀዱ ቴሌቪዥን

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#BREAKING በመላ ሀገሪቱ ውስጥ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ ዛሬ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ያሳለፈው ውሳኔ ከዛሬ ጀምሮ ተፈፃሚ የሚሆን ሲሆን በ48 ሰዓታት ውስጥ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ይፀድቃል። @tikvahethiopia
#BREAKING

የጠ/ሚኒስትር ፅ/ቤት ፦

" የሚኒስትሮች ም/ቤት ዛሬ ባካሄደው 2ኛ አስቸኳይ ስብሰባ የሃገር ህልውና እና ሉዐላዊነት ላይ የተደቀነን አደጋ ለመከላከል የወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 5/2014 ቀሪ የሚሆንበትን ጊዜ በሚመለከት በቀረበው የውሳኔ ሃሳብ ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ፡፡

ሕውሃት እና ግብረአበሮቹ በሃገራችን ህልውና እና ሉአላዊነት ላይ ከፍተኛ አደጋ የደቀኑ በመሆኑ እና ይህን አደጋ በመደበኛው የህግ ማስከበር ስራ መከላከል የማይቻል ሆኖ በመገኘቱ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ጥቅምት 23 ቀን 2014 የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 5/2014ን ያወጀ ሲሆን፣ ይህ አዋጅ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ በአዋጅ ቁጥር 1264/2014 ፀድቆ በስራ ላይ የሚገኝ መሆኑ ይታወቃል፡፡

ሆኖም ግን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማውጣት የግድ አስፈላጊ እንዲሆን አድርጎ የነበረው ሁኔታ የተቀየረ በመሆኑ እና ስጋቱን በመደበኛው የሕግ ማስከበር ስራ መከላከልና መቆጣጠር የሚቻልበት ደረጃ ላይ በመደረሱ ለስድስት ወራት የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የተፈፃሚነት ጊዜ ማሳጠር አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል።

በመሆኑም በአዋጅ ቁጥር 1264/2014 አንቀጽ 11(2) በተደነገገው መሰረት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስድስት ወራት የጊዜ ገደቡ ከመጠናቀቁ በፊት ለአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መታወጅ ምክንያት የሆኑ ሁኔታዎች ከተቀየሩ እና በመደበኛው የሕግ ማስከበር ስርዓት ሊከሰቱ የሚችሉ ጉዳዮችን መቆጣጠር ይቻላል ብሎ ካመነ የስድስት ወር ጊዜው ሳይጠናቀቅ ጊዜውን የማሳጠር ስልጣን ያለው በመሆኑ የአዋጁን ተፈጻሚነት ቀሪ እንዲያደርገው የሚጠይቅ የውሳኔ ሃሳብ ቀርቦ በውሳኔ ሃሳቡ ላይ የሚኒስትሮች ምክር ቤት በጥልቀት ተወያይቶ በማጽደቅ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት እንዲተላለፍ ወስኗል፡፡ "

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
#State_of_Emergency

ለ6 ወራት የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የተፈፃሚነት ጊዜ እንዲያጥር የሚኒስትሮች ምክር ቤት ዛሬ ውሳኔ አሳልፋል።

ም/ቤቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማውጣት የግድ አስፈላጊ እንዲሆን አድርጎ የነበረው ሁኔታ የተቀየረ መሆኑን ገልጿል።

አክሎም ስጋቱን በመደበኛ የሕግ ማስከበር ስራ መከላከልና መቆጣጠር የሚቻልበት ደረጃ ላይ መደረሱን በመግለፅ ለ6 ወራት የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የተፈፃሚነት ጊዜ ማሳጠር አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን አሳውቋል።

በዚህም አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የ6 ወር ጊዜው ሳይጠናቀቅ ጊዜውን የማሳጠር ስልጣን ያለው ህ/ተ/ም/ቤት የአዋጁን ተፈጻሚነት ቀሪ እንዲያደርገው የሚጠይቅ የውሳኔ ሃሳብ ለምክር ቤቱ እንዲተላለፍ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ውሳኔ አሳልፏል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
ጋዜጠኛ ክብሮም ወርቁ ከእስር ተለቀቀ። ላለፉት 3 ወራት ከሶስት ቀን በእስር ላይ የነበረው የአሐዱ ሬዲዮ የዜና ክፍል ሀላፊ ክብሮም ወርቁ ዛሬ ከሰአት በኃላ ከእስር ተፈትቶ ከቤተሰቦቹ ጋር መቀላቀሉን ጠበቃው አቶ ጥጋቡ ደሳለኝ መናገራቸውን አሀዱ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን አሳውቋል። @tikvahethiopia
ፎቶ : ጋዜጠኛ ክብሮም ወርቁ ከእስር ተፈቶ ከቤተሰቦቹ ጋር ተቀላቅሏል።

ጋዜጠኛው ከእስር መፈታቱን በተመለከተ በተረጋገጠ ፌስቡክ ገፁ ላይ " ከጥቅምት 18 እስከ ጥር 18 ... በእግዚአብሔር ምህረት ተፈትቻለሁ ፤ አመሰግናለሁ " ብሏል።

ጋዜጠኛ ክብሮ ወርቁ ላለፉት 3 ወራት በእስር ቆይቷል። ዛሬ ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ዋናው መስሪያ ቤት በመታወቂያ ዋስትና ነው ከእስር የተፈታው።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ተነስቷል ?

" የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ተነስቷል " እየተባለ በማህበራዊ ሚዲያ የሚሰራጨው መረጃ ሀሰተኛ መረጃ ነው።

ለ6 ወራት የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የተፈፃሚነት ጊዜ እንዲያጥር የሚኒስትሮች ምክር ቤት ዛሬ ውሳኔ አሳልፋል።

በዚህም አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የ6 ወር ጊዜው ሳይጠናቀቅ ጊዜውን የማሳጠር ስልጣን ያለው ህ/ተ/ም/ቤት የአዋጁን ተፈጻሚነት ቀሪ እንዲያደርገው #የሚጠይቅ የውሳኔ ሃሳብ በማፅደቅ ለምክር ቤቱ እንዲተላለፍ ተወስኗል።

ጉዳዩ ይህ ሆኖ ሳለ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንደተነሳ ተደርጎ የሚሰራጨው መረጃ ሀሰተኛ ነው።

ኢትዮጵያ አሁንም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር ናት።

@tikvahethiopia
#Safricom_Ethiopia

ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ከመሬት ባንክ ልማት ኮርፖሬሽን ጋር በመሆን ትላንት የውይይት መድረክ አዘጋጅቶ ነበር።

በዚሁ የውይይት መድረክ ሳፋሪኮም በኢትዮጵያ ለሚያካሂደው የኔትወርክ ግንባታ ቀጥተኛ አስተዋጽዖ ካላቸው ልዩ ልዩ ሚኒስቴትር መስሪያ ቤቶችና የመንግስት ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች ጋር ትብብሩን በማጠናከር በቀጣይ ስለሚያስፈልጉን ድጋፎች መምከሩን ገልጿል።

ሳፋሪኮም ፥ " የኢትዮጵያ መንግስት የሚያደርግልን ያልተቋረጠ ድጋፍ ለደንበኞቻችን ምርጥ የሆነውን አገልግሎት ለማቅረብ እንዲሁም የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን አጀንዳ በብቃት እንድንደግፍ የሚያስችለን ነው " ብሏል።

አገልግሎቱን ለመጀመር እየተጋ መሆኑንም ገልጿል።

ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ውስጥ አገልግሎቱን በይፋ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል።

@tikvahethiopia
#Tigray , #Mekelle📍

በዛሬው ዕለት የዓለም አቀፍ ቀይ መስቀል ኮሚቴ (ICRC) ከባለፈው መስከረም ወር ወዲህ በትግራይ ክልል መቐለ ከተማ የመጀመሪያውን የህክምና ቁሳቁስ ድጋፎችን ማድረስ መቻሉን አሳውቋል።

አስፈላጊ መድሃኒቶችን ያካተተው የአስቸኳይ ህክምና ቁሳቁሶች አቅርቦት በክልሉ በጣም ለተጎዱ የጤና ተቋማት ይደርሳል ተብሏል።

ዓለም አቀፍ ቀይ መስቀል ኮሚቴ ተጨማሪ በረራዎችን በማዘጋጀት በያዝነው እና በቀጣይ ሳምንታት የህክምና ቁሳቁስ ድጋፉን ለመቀጠል አቅዷል፡፡

በተመሳሳይ ድርጅቱ በአማራ እና አፋር ክልሎች በግጭቱ ምክንያት አገልግሎት መስጠት አስቸጋሪ ለሆነባቸው የጤና ተቋማት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አሳውቋል።

ምንጭ : https://www.icrc.org/en/document/ethiopia-icrc-aid-flight-delivers-lifesaving-medical-supplies-tigray

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
ኮሎኔል ማማዲ ዱምበያ ስለብሄራዊ ቡድኑ ምን አሉ ?

የጊኒ ብሄራዊ ቡድን በካሜሮን የ2021 አፍሪካ ዋንጫ በጊዜ ከተሰናበቱት ሀገራት መካከል እንደምትገኝበት ይታወቃል።

ቡድኑ ወደ ካሜሮን በተሸኘበት ምሽት አሁን ጊኒን እያስተዳደር ያለው የጁንታ መሪ ኮሎኔል ማማዲ ዱምበያ ለቡድኑ አባላት ያስተላለፉት መልዕክት መነጋገሪያ ሆኖ እንደነበር የሁላችንም ትውስታ ነው።

ኮሎኔል ማማዲ ዱምበያ የሀገሪቱን ባንዲራ 🇬🇳 ለቡድኑ ካስረከቡ በኃላ ባስተላለፉት መልዕክት የቡድኑ አባላት ዋንጫውን ይዘው እንዲመጡ ካልሆነ ግን በእነሱ ላይ ኢንቨስት የተደረገውን እያንዳንዱን ገንዘብ እንዲመልሱ /እንዲተኩ ነበር ያሉት።

ቡድኑም በአፍሪካ ዋንጫው ሳይሳካለት ቀርቶ በጊዜ ተሰናብቷል ፤ ይህን ተከትሎ የጁንታውን መሪ ኮሎኔል ማማዲ ዱምበያ አስተያየት ብዙዎች ሲጠብቁት ነበር።

ኮሎኔል ማማዲ ዱምበያም ዝም አላሉም።

ኮሌኔሉ ብሄራዊ ቡድኑን 'ይቅር' እንዳሉ ገልፀው ፤ በወቅቱ ያን ንግግር የተናገሩት ቡድኑን ለማበረታታ ብቻ መሆኑ አሳውቀዋል። " የቡድን ግንባታ ጊዜ እንደሚወስድ እገነዘባለሁም " ብለዋል።

ነገር ግን ለቡድኑ የተሰጠው ገንዘብ ሩብ ፍፃሜ ፣ ግማሽ ፍፃሜ እና የፍፃሜ ጨዋታዎችን የሚሸፍን ሲሆን ያ ገንዘብ ወደ መንግስት ካዝና ይመለሳል ተብሏል።

@tikvahethiopia
#NewsAlert

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፕሬዚዳንት ሣህለ ወርቅ ዘውዴ ለተለያዩ ግለሰቦች የሙሉ አምባሳደርነት እና የአምባሳደርነት ሹመት ሰጡ።

በዚህም መሠረትም፡-

1/ አቶ ተፈራ ደርበው
2/ አቶ ደሴ ዳልኬ
3/ ዶክተር ስለሺ በቀለ
4/ ጄኔራል ባጫ ደበሌ
5/ ጄኔራል ሀሰን ኢበራሂም
6/ ወ/ሮ ሽትዬ ምናለ
7/ ፕሮፌሰር ፍቃዱ በየነ
8/ አቶ ረሻድ መሀመድ
9/ አምባሳደር ጀማል በከር
10/ አቶ ፈይሰል ኦሊይ
11/ አቶ ኢሳያስ ጎታ
12/ አቶ ፀጋአብ ክበበው
13/ አቶ ጣፋ ቱሉ
14/ ዶክተር ገነት ተሾመ
15/ አቶ ዳባ ደበሌ
16/ አቶ ፍቃዱ በየነ የባሉሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሆነው ሲሾሙ።

1/ አቶ አሳየ አለማየሁ
2/ አቶ ኃይላይ ብርሃነ
3/ አቶ አወል ወግሪስ
4/ ወ/ሮ ብዙነሽ መሠረት
5/ አቶ አንተነህ ታሪኩ
6/ አቶ አክሊሉ ከበደ
7/ አቶ ሰይድ መሐመድ
8/ አቶ ዮሴፍ ካሳዬ
9/ አቶ ዘላለም ብርሃን
1ዐ/ ወ/ሮ ፍርቱና ዲባኮ
11/ አቶ ወርቃለማሁ ደሰታ በአምባሳደርነት የተሾሙ መሆኑን ከፕሬዝዳንት ፅሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

@tikvahethiopia
#ETHIOPIA

የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ለሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነርነት ከቀረቡት ዕጩዎች መካከል 42ቱን መለየቱን የም/ቤቱ አፈ-ጉባኤ የተከበሩ አቶ ታገሰ ጫፎ ዛሬ አሳውቀዋል።

አቶ ታገሰ ፥ ከመላው የሀገሪቱ ክፍሎች 632 የእጩ ኮሚሽነሮች ጥቆማ መቅረባቸውንና አብዛኛዎቹ ስራውን ለመስራት የሚያስችል ልምድና ዕውቀት ያላቸው መሆኑን መገንዘብ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡

አዋጁ ለአፈ-ጉባኤውና ለአፈ-ጉባኤው ጽ/ቤት በሰጠው ስልጣን እንዲሁም በአዋጁ በተቀመጠው መስፈርት መሰረት ከቀረቡት 632 ዕጩዎች መካከል 42ቱ መለየታቸውን ተናግረዋል፡፡

በቀረቡ 42 ዕጩ ኮሚሽነሮች ላይ ከአማካሪዎች ጋር ምክክር እየተደረገበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በቀጣይ ሳምንት ደግሞ የሲቪክ ማህበራት ተወካዮች ፣ የሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ አመራሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት አመራር አካላት በሚገኙበት በዕጩዎች የትምህርት ዝግጅትና የስራ ልምድ ላይ ምክክር ተደርጎ ግብአት የሚሰበሰብ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

በማስከተልም በም/ቤቱ ድረ-ገጽና በማህበራዊ ሚዲያ የእጩዎችን ማንነት በመግለጽ በቂ ግብአት ከተሰበሰበ በኋላ ሰብሳቢና ም/ሰብሳቢን ጨምሮ 11ዱ ዕጩ ኮሚሽነሮች ለም/ቤቱ ቀርቦ ከፀደቀና ዕጩዎች ከተሰየሙ በኋላ ወደ ስራ እንደሚገባም ገልጸዋል።

@tikvahethiopia