TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.3K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
አ.ሳ.ቴ.ዩ. ለተወሰነ ጊዜ ተዘጋ‼️

የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እየተስተጓገለ ያለውን የትምህርት ክፍለጊዜ ለማስተካከል ለጊዜው የመማር ማስተማሩ ሂደት ተቋርጦ ተማሪዎች ወደ የቤተሰቦቻቸው #እንዲመለሱ መወሰኑን አስታወቀ።

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር #ለሚ_ጉታ ዛሬ ለኢዜአ እንደገለጹት ተማሪዎች ትምህርታቸውን ካቋረጡ 31 ቀናት ሆናቸዋል።

ይህንኑ ቀናት ሁሉ ባክኖ የመጀመሪያውን መንፈቀ ዓመት የመማር ማስተማር እቅዱን ማሳካት ስለማይቻል እንደ አዲስ ትምህርቱን የካቲት 25 ቀን እንዲጀመር በሴኔቱ ተወስኗል።

የባከነውን የትምህርት ክፍለጊዜ እንደ አዲስ አስተካክሎ ለመጀመርና ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት ለማረጋገጥ ለጊዜው ተማሪዎች ወደ ቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ መወሰኑን ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል።

ተማሪዎቹ ከአንድ ወር በላይ ትምህርታቸውን ያቋረጡት ዩኒቨርሲቲው የገባልን ቃል አልፈፀመም በሚል ሰበብ እንደነበር አስታውሰዋል።

የተማሪዎቹ ጥያቄ የሁለተኛና ሶስተኛ ዲግሪ የትምህርት እድል እንደሚመቻችላቸው እንዲሁም የሥራ እድል ትስስር ከኢንዱስትሪዎች ጋር እንደሚፈጠርላቸው ቃል ተገብቶልን ነበር የሚል ነው።

በተጨማሪም ላፕቶፕ ኮምፒዩተር እንደሚሰጣቸው የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት የነበሩት የውጭ ዜጋ ቃል ገብቶልናል የሚል ጥያቄ እንደሚያነሱም ዶክተር ለሚ አመልክተዋል።

መንግስት ሁኔታዎችን አይቶና ገምግሞ የሀገሪቷን አቅም መሰረት ያደረገ መፍትሔ እንደሚፈልግ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች፣የቦርድና የዩኒቨርስቲው አመራሮች ባሉበት በተካሄደው ውይይት ቢገልፅም ተማሪዎቹ ለመቀበል ሳይፈልጉ ቀርተዋል።

በዚህም ምክንያት ከአንድ ወር በላይ የመማር ማስተማር ሂደቱን በማስተጓጎል አንዳንድ ተማሪዎች ከጊቢ ወጥተው ለተለያዩ ሱሶችና አልባሌ ተግባራት እየተጋለጡ መሆኑን ጠቁመዋል።

”በተቋሙ ውስጥ የምግብ፣የመኝታና ተጓዳኝ አገልግሎት እያገኙና የሀገር ሀብት እየባከነ እንደፈለጉ መሆን ስለማይቻል ለጊዜው የመማር ማስተማር ሂደት በማቋርጥ ተማሪዎች ወደየ ቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ ወስነናል “ብለዋል።

ዩኒቨርሲቲው ከጥር 12/2011 ዓ.ም. ጀምሮ ተማሪዎች ቅጥር ጊቢውን ለቀው እንዲወጡና ወደ የቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ ማድረጉን ጠቅሰው የተማሪ ወላጆች ልጆቻቸው ከነሱ የተለዩበትን ዓላማ ብቻ ከዳር እንዲያደርሱ የማድረግና የመምከር ቤተሰባዊ ኃላፊነት መወጣት እንደሚጠበቅባቸውም አሳስበዋል።

በሴኔቱ ውሳኔ ተማሪዎቹ ወደ ዩኒቨርሲቲው የሚመለሱትና በአዲስ መልክ ተመዝግበው ትምህርታቸውን የሚጀምሩበት የካቲት 25 እና 26/2011 ዓ.ም. እንደሆነ ያስታወሱት ዶክተር ለሚ “ነገር ግን የባከነውን የትምህርት ክፍለጊዜ ለማካካስ በማሰብ አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መልሰን ለመጥራት ርብርብ እያደረግን እንገኛለን“ብለዋል።

ዩኒቨርሲቲው እየተስተጓጓለ ያለውን የመማር ማስተማር ሂደት ለማስተካከል የወሰደው እርምጃ አግባብ መሆኑን የገለጸው ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የኤሌክትሮንክስና ኮሙዩኒኬሽን ትምህርት ክፍል የአምስተኛ ዓመት ተማሪና የተማሪዎች ተወካይ ፍፁም ቱጁባ ነው።

በ2007 ዓ.ም. በወቅቱ ተቋሙ ሲመሩ በነበረው የውጭ ዜጋ በአፍ ደረጃ የላፕቶፕ ኮምፒዩተሮችን ጨምሮ የሁለተኛና ሶስተኛ ዲግሪ እንደሚሰጣቸው የተገባውን ቃል አሁን ካልተፈፀመልን አንማርም ብሎ ትምህርት ማቋረጥ ትክክል እንዳልሆነ ጠቅሷል፡፡

አሁን ላይ ተማሪዎች ወደ ቤተሰቦቻቸው ተመልሰው ራሳቸውን እንዲያዩና እንዲፈትሹ የሚያደርግ የእርምት እርምጃ በመሆኑ እንደሚደግፈው ተናግሯል።

”በተቋሙ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት እንዲረጋገጥ የተማሪ ቤተሰቦች ጭምር የድርሻቸውን መወጣት አለባቸው” ብለዋል።

ተማሪዎችም ቢሆኑ ከፖለቲካ ግፊትና አስተሳሰብ ወጥተው የመማር ግዴታቸውን እየተወጡ የወጡለትን ዓላማ ሳይጎዱ መብታቸውን መጠየቅ እንደሚገባቸውም ተማሪ ፍፁም መልዕክቱን አስተላልፏል።

ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
@tsegabwolde @tikvahethiopia
አ.ሳ.ቴ.ዩ‼️

#የአዳማ_ሳይንስና_ቴክኖሎጂ_ዩኒቨርሲቲ ከጥር 12 እስከ 14 ቀን 2011ዓ.ም. ሁሉም የመደበኛ ቅድመ ምረቃ ተማሪዎች ዩኒቨርሲቲውን ለቀው እንዲወጡ መወሰኑን ተከትሎ፣ ተማሪዎቹና የዪኒቨርሲቲው አስተዳደር እየተወዛገቡ ነው። የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት #ለሚ_ጉታ (ዶ/ር)የተላለፈው ውሳኔ ትክክል ነው ሲሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ተማሪዎቹ ግቢውን ለቀው እንዲወጡ የተወሰነው ውሳኔ ሕጉን መሠረት ያደረገ መሆኑን ፕሬዚዳንቱ ያስረዱ ቢሆንም፣ ተማሪዎቹ የተወሰደው ዕርምጃ መሬት ላይ ያለውን #እውነታ ከግምት ያላስገባ ነው በማለት #ተቃውመውታል

ዩኒቨርሲቲው ከጥር 15 ቀን ጀምሮ ለቅድመ ምረቃ ተማሪዎች የሚሰጠውን ማንኛውንም አገልግሎት እንደሚያቋርጥ ጥር 12:በዩኒቨርሲቲው ሰሌዳ ባወጣው ማስታወቂያ ይፋ አድርጓል፡፡

በዩኒቨርሲቲው ሴኔት መመሪያ መሠረት አንድ ተማሪ በሴሚስተር መከታተል ያለበት ቢያንስ ሰማንያ በመቶ የትምህርት ክፍለ ጊዜ ሲሆን፣ ተማሪዎቹ በሴሚስተሩ ከተቀመጠው የትምህርት ክፍለ ጊዜ 34.4 በመቶ እንዳልተከታተሉ፣ በመመሪያው አንቀጽ 101.2 እና 231.3መሠረት በዩኒቨርሲቲው ሴኔት ውሳኔ ዕርምጃ መውሰድ አስፈላጊ ሆኖ በማግኘቱ ዕርምጃው መወሰዱን በዩኒቨርሲቲው የማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ ይፋ የሆነው ማስታወቂያ ይገልጻል፡፡

ይህን ያህል የትምህርት ክፍለ ጊዜ ሊከታተሉ ያልቻሉት በተደጋጋሚ ለተቃውሞ ሠልፎች በመውጣታቸው እንደነበር ተማሪዎቹ ገልጸው፣ ከወር በፊት በዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ ውስጥ ሦስት ተማሪዎች ሕይወት ማለፉ ለተቃውሞዎቹ መራዘም ምክንያት መሆኑንም አክለዋል፡፡ በዚህ ክስተት ማግሥት ዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች የአጋማሽ ፈተና እንዲወስዱ ማስታወቂያ ወጥቶ እንደነበር፣ ፈተናውን መውሰድ እንደማይችሉ ቢገልጹም ሰሚ አለማግኘታቸውን ተማሪዎቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ለተከታታይ ዘጠኝ ቀናት የመማር ማስተማር ሒደቱ ተቋርጧል በማለት የተላለፈውን ውሳኔ ተቃውመዋል፡፡

‹‹ይኼንን ፈተና መውሰድ ያልቻልነው በሦስቱ #ወንድሞቻችን ላይ የደረሰው ድንገተኛ ሞት ምክንያት በደረሰብን መሪር #ሐዘንና #ድንጋጤ እንዲሁም ሥርዓተ ቀብር ለመፈፀም ወደ የትውልድ ቦታቸው (አሰላ፣ አለታ ወንዶና ባህር ዳር) በመጓዛችን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ተገቢውን ዝግጅት አላደረግንም፤›› ሲሉ ፈተናው እንዲራዝም የጠየቁበትን ምክንያት ለሪፖርተር ያስረዱ ሲሆን ‹‹ዋናው ጥያቄያችንም የደኅንነት ጥያቄ ነው›› ብለዋል።

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የሞቱትን ተማሪዎች በሚመለከት ከአዳማ ፖሊስ መምሪያና ከቅዱስ ጳውሎስ ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የአስክሬን ምርመራ ውጤት እንደደረሳቸው ወዲያውኑ ለተማሪዎች ይፋ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱም ይህ ሁኔታ ከመፈጠሩ በፊት ተማሪዎቹ የሁለተኛና የሦስተኛ ዲግሪ ዕድል ይመቻችልን እንዲሁም የሥራ ዕድል ትስስር ከኢንዱስትሪዎች ጋር እንደሚፈጠርልን ቃል ተገብቶልን ነበር በሚል ከሦስት ሳምንት በላይ ትምህርት አቋርጠው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ እነዚህ ቀናት ሁሉ ባክነው የመጀመሪያውን መንፈቀ ዓመት ዕቅድ ማሳካት ስለማይቻል እንደ አዲስ የመማር ማስተማሩ ሒደት የካቲት 25 እና 26 ቀን 2011 ዓ.ም. እንዲጀመር በሴኔቱ ተወስኗል ብለዋል፡፡ የባከነውን የትምህርት ክፍለ ጊዜ ለማካካስም አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መልሰን ለመጥራት ርብርብ እያደረግን እንገኛለን ሲሉም አክለዋል፡፡

ምንጭ፦ ሪፖርተር
@tsegabwolde @tikvahethiopia
አ.ሳ.ቴ.ዩ‼️

የመማር ማስተማሩ ሂደት ተቋርጦ የነበረው የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ ተማሪዎች ተመልሰው ትምህርት እንዲጀምሩ በሴኔት መወሰኑን ዩኒቨርሲቲው አስታወቀ።

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር #ለሚ_ጉታ ለfbc እንደተናገሩት የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር እና መምህራን ትናንት ከተማሪ ወላጆች ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ ሴኔቱ ተማሪዎች ወደ ትምህርት እንዲመለሱ ወስኗል ብለዋል።

ከተማሪ ወላጆች ጋር በተደረገ ውይይትም ወላጆች ተማሪዎች ጥያቄ ቢኖራቸውም ትምህርት #ማቋረጣቸው ተቀባይነት የሌለው መሆኑንና የተፈጠረው ችግርም #እንዳሳዘናቸው መናገራቸውን አንስተዋል።

ወላጆች ለተማሪዎቹ ድርጊት #ይቅርታ እንዲደረግ መጠየቃቸውን ተከትሎም ሴኔቱ ያስተላለፈውን የአንድ ሴሚስተር ቅጣት ማንሳቱን ገልጿል።

በዚህ መሰረትም ከፊታችን ሰኞ የካቲት አራት ጀምሮ ተማሪዎች ወደ ተቋሙ የሚገቡ መሆኑ ነው የተገለፀው።

የተቋሙን የመማር ማስተማር ሂደት ሆነ ብለው ሲያውኩ የነበሩ ተማሪዎች ግን የስነ ምግባር ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ዩኒቨርሲቲው አስታውቋል።

የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ትምህርት ማቆማቸውን ተከትሎ  ከጥር 12 ቀን  እስከ 14 ቀን 2011 ዓ.ም  ጊቢውን ለቀው እንዲወጡ መደረጋቸው ይታወሳል ።

ምንጭ፦ fbc
@tsegabwolde @tikvahethiopia
አ.ሳ.ቴ.ዩ‼️

• በ25 ተማሪዎች ላይ የዲስፕሊን እርምጃ ወስዷል፤

• 14 የስታፍ አባላትንም ለይቶ ለዲስፕሊን የማቅረብ ሂደት ጀምሯል፤
.
.
የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በዳግም ቅበላ ተማሪዎቹን ማስተማር መጀመሩን ገለጸ፡፡ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እንዳይማሩ በማድረጉ ሂደት ተሳትፎ ባላቸው 25 ተማሪዎች ላይ የዲስፕሊን እርምጃ መውሰዱን እና 14  የስታፍ አባላትንም ለይቶ #ለዲስፕሊን የማቅረብ ሂደት መጀመሩን ገልጿል፡፡

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር #ለሚ_ጉታ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደተናገሩት፤ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው ጊቢ ውስጥ እየኖሩ ነገር ግን ለረዥም ጊዜ ክፍል ሳይገቡ መቆየታቸውን ተከትሎ ለአንድ ሴሚስተር እንዲቀጡ ሴኔቱ በወሰነው መሰረት ከጊቢ እንዲወጡ ተደርጎ ነበር፡፡ ሆኖም ተማሪዎች ከሄዱ በኋላ የዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንትና ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ጨምሮ ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ተማሪዎች ከጊቢ በወጡበት ጊዜ ውስጥ መሰራት በሚገባቸው ዘጠኝ ያህል ነጥቦችን ለይቶ ቀንና ሌሊት ሲሰራ በመቆየቱ ለአንድ ወር ከ15 ቀን የነበረውን ከጊቢ ውጪ ቆይታቸውን ወደ ሦስት ሳምንት እንዲያጥር ተደርጓል፡፡ አብዛኛው ተማሪም ፒቲሺን ፈርሞ ይቅርታ ጠይቋል፡፡

እንደ ዶክተር ለሚ ገለጻ፤ ተማሪዎች ከጊቢ ውጭ በነበሩበት ጊዜ ከዩኒቨርሲቲው በቅርብ ርቀት ያሉ ወላጆችን በማወያየት ቤተሰብም ያላቸውን ጥያቄዎች አንስተው መልስ ተሰጥቶ መግባባት ላይ ተደርሷል፡፡ በዚህም ተማሪዎቹ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እድል እንዲሰጣቸውና የሴሚስተር ቅጣቱ ቀርቶላቸው፤ አጥፊ ተማሪዎች ግን ተለይተው እርምጃ እንዲወሰድና ሌሎች ተማሪዎች በይቅርታ እንዲመለሱ መስማማት ተችሏል፡፡ ቤተሰብም ልጆቻቸውን እንደሚመክሩ ቃል ገብተው በሄዱት መሰረት የሴሚስተሩ ቅጣት በሴኔቱ ውሳኔ መሰረት እንደገና ተነስቶላቸው ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ ተደርጓል፡፡

እንደ ዶክተር ለሚ ገለጻ፤ ከወላጆች ጋር በነበረው ውይይት ልጆቻችን ትምህርት እንዳይገቡ የሚያስፈራሩ አካላት አሉ፤ በጥቂት ተማሪዎች ተጽዕኖ ስር ወድቀዋልናም እርምጃ ሊወሰድ ይገባል የሚል ጥያቄ ከወላጆች ቀርቦ ነበር፡፡ ይሄንና ሌሎች መረጃዎችን መነሻ በማድረግም እርምጃ መውሰድ የተጀመረ ሲሆን፤ አጥፊና አስተባባሪ የሚባሉ ተማሪዎችን ለይቶ ለዲስፕሊን የማቅረብ ስራ እንዲከናወን፤ ከአካዳሚክ ስታፉም ሆነ ከአስተዳደር አካሉ በዚህ ላይ የተሳተፈ ፤ ተማሪዎች ወደክፍል እንዳይሄዱ የሚመክርና የሚያስተባብር ካለ፤ እነዚህን ለይቶ እርምጃ እንዲወሰድ አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ ይህ የእርምጃና የልየታ ስራ ተጠናቅቆ 25 ተማሪዎች የዲሲፕሊን ቅጣት ተጥሎባቸዋል፡፡ 5 የአካዳሚክ ስታፍና 9 የአስተዳደር ስታፍ አባላትም ተለይተው ለዲስፕሊን እንዲቀርቡ እየተደረገ ሲሆን፤ ተጨማሪ መረጃዎችን የማሰባሰብ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛል፡፡

ከዚህ በኋላ ሰኞ እና ማክሰኞን ዳግም ምዝገባው ተካሂዶ ዕረቡ ዕለት ትምህርት መጀመሩን የገለጹት ዶክተር ለሚ፤ መመዝገብ ከሚገባቸው ተማሪዎች ውስጥ 93ነጥብ5 በመቶዎቹ ተመዝግበው ትምህርታቸውን መከታተል እንደቻሉና፣ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደቱም ጥሩ በሚባል ደረጃ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ ቀሪዎቹም በተመሳሳይ ተመዝግበው ትምህርታቸውን እንደሚጀምሩ ያላቸውን እምነት በመጠቆምም፤ ተማሪዎች ባለው ጊዜ ውስጥ የሁለቱንም ሴሚስተር ትምህርት እንዲከታተሉ በሚያስችል መልኩ የትምህርት መርሃ ግብሩ እንደሚከለስም ገልጸዋል፡፡

ይሁን እንጂ አሁንም የዲስፕሊን እርምጃ የተወሰደባቸው ተማሪዎች ካልተመለሱ ክፍል አንገባም የሚሉ ጥቂት ተማሪዎች መኖራቸውን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርሲቲ ሲመጡ ዓላማቸው መማር እንደመሆነና ወክለው የመጡትም ራሳቸውን መሆኑን ተገንዝበው ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ መክረዋል፤ ይሄን የሚያራምዱ ጥቂት ተማሪዎችም ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ አሳስበዋል፡፡ ሆኖም ይሄን በመዘንጋት ዳግም ወደሌላ ችግር ለመግባት የሚታትሩ ተማሪዎች ካሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እርምጃ የሚወሰድ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡ ወላጆችም ይሄን ተገንዝበው ልጆቻቸውን ሊመክሩና መስመር ሊያሲይዙ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡

እንደ ዶክተር ለሚ ገለጻ፤ ተማሪዎች ጥያቄ ማንሳትና ጥያቄዎቻቸውን በሕግና በስርዓት ለሚመለከታቸው አካላት አቅርበው መልስ የማግኘት መብታቸው ነው፡፡ ይሄን ሲያደርጉ ግን እየተማሩና የመጡበትን ዓላማ እየከወኑ መሆን እንዳለበት መረዳት አለባቸው፡፡ በዚህ ላይም ሁሉም አካል የድርሻውን መወጣት ያለበት ሲሆን፤ በተለይ ቤተሰብ ከፍተኛ ሚና ይጠበቅበታል፡፡ ምክንያቱም ወላጅ ልጁን ልኮ መቀመጥ ብቻ ሳይሆን የልጁን የትምህርት አቅምና ባህሪ በተለያየ አግባብ መከታተል ይኖርበታል፡፡ ዩኒቨርሲቲውም የመማር ማስተማር ሂደቱን ሰላማዊ ለማድረግ እና የተማሪዎችን ባህሪና ስነምግባር ለመከታተል የሚያስችሉ የተለያዩ ሰነዶች የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎችን ልምድ በመውሰድ ተዘጋጅተዋል፤ አሰራሮችም ተዘርግተዋል፡፡

ከዚህ ባለፈም አስካሁን ከመልካም አስተዳደር ችግር ጋር የተገናኙ ጥያቄዎች ባይኖሩም፤ ለወደፊት መልኩን ቀይሮ ችግሩ እንዳይመጣ በዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ከአገልግሎት አሰጣጥ፣ ከጸጥታም ሆነ ሌሎች የመልካም አስተዳደር ችግሮች ካሉም እየተፈተሹ ክፍተቶች እንዳይኖሩ እየተሰራ ነው፡፡ ለአብነት ከጊቢ ጸጥታ ጋር በተያያዘ የጊቢውን ደህንነት ከማስጠበቅ አኳያ ወደ 200 የሚሆኑ የጸጥታ ሰራተኞቹን ከኦሮሚያ ፖሊስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ጠንካራ ስልጠና እንዲሰጥ ተደርጓል፡፡ በመሆኑም በዩኒቨርሲቲው ከመምህራን ባሻገር ከተማሪዎች ጋር በቅርበት የሚሰሩ ፕሮክተሮች፣ የሕክምና ባለሙያዎች፣ የላይበራሪ አገልግሎት የሚሰጡና ሌሎችም አካላት ጋርም ሰፊ ውይይትና ግምገማ ተደርጎ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣት እንዳለባቸውም ተቀምጧል፡፡

ተማሪዎችን ለማነጽ ዋናው ጉዳይም በጭንቅላት ላይ መስራት እንደመሆኑ አነቃቂ ንግግሮችና ስልጠናዎችን እንዲያገኙ እየተደረገ ሲሆን፤ ባለፈው ሳምንት ወደ 600 ለሚሆኑ መምህራንና የአስተዳደር ሰራተኞች የቦርድ ሰብሳቢው አነቃቂ ንግግር አቅርበውላቸዋል፡፡ ለቀጣይ ቅዳሜም ዶክተር ምህረት ደበበ ተጋብዘዋል፡፡ ይሄን መሰል ሥራ ቀጣይነት ባለው መልኩ የሚሰራ ሲሆን፤ ተማሪውና ማህበረሰቡ እንዲዋሃድ፣ አንዱም አንዱን እንዲረዳ የሚደረግ ይሆናል፡፡

ምንጭ፦ አዲስ ዘመን ጋዜጣ
@tsegabwolde @tikvahethiopia