TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#ትኩረት

በአማራ ክልል፣ ኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር በጅሌ ጥሙጋ ወረዳ በዚህ ሰዓት የፀጥታ ችግር መኖሩን በወረዳው ነዋሪ የሆኑ የቲክቫህ ቤተሰብ አባላት አሳውቀዋል።

ያለው ሁኔታ #እጅግ_በጣም ከፍተኛ የሆነ ትኩረት የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል።

ባለው የፀጥታ ስጋት " ለነፍሳችን ሰግተናል " ያሉ ነዋሪዎች የፌዴራል መንግስት ጣልቃ እንዲገባ እና ሁኔታው እንዲረጋጋ ጠይቀዋል።

ዛሬ በወረዳው ለተፈጠረው የፀጥታ ችግር ዝርዝር መረጃ ለማግኘት ጥረት እያደረግን ነው።

የጅሌ ጥሙጋ ወረዳ በተረጋገጠ የማህበራዊ ትስስር ገፁ ላይ ፤ "ሰንበቴ በአሁኑ ሰአት ጭንቅ ውስጥ ገብታለች ፤ ዱኣ ወይም ፀሎት ትፈልጋለች!! የሚመለከተው የመንግስት ባለድርሻ አካላትን ልዩ ትኩረት ትሻለች። " ሲል አንድ አጭር ፅሁፍ አሰራጭቷል።

ወረዳው ይህንን ከማለት ውጭ ስለጉዳዩ ምንም የሰጠው ዝርዝር መረጃ የለም።

በአጣዬ በኩልም ስጋት መኖሩን ቤተሰቦቻችን እየገለፁ ይገኛሉ።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ፤ በአካባቢው ካሉት የቤተሰብ አባላቱ ሁኔታውን ለመከታተል ጥረት ያደርጋል።

ይህ የሀገራችን ቀጠና ከዚህ ቀደም ተደጋጋሚ ጊዜ የፀጥታ ችግር ሲከሰትበት እና የሰዎች ህይወት ሲቀጠፍበት ፣ ንብረትም ሲወድምበት እንደነበር የሚዘነጋ አይደለም።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#ትኩረት በአማራ ክልል፣ ኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር በጅሌ ጥሙጋ ወረዳ በዚህ ሰዓት የፀጥታ ችግር መኖሩን በወረዳው ነዋሪ የሆኑ የቲክቫህ ቤተሰብ አባላት አሳውቀዋል። ያለው ሁኔታ #እጅግ_በጣም ከፍተኛ የሆነ ትኩረት የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል። ባለው የፀጥታ ስጋት " ለነፍሳችን ሰግተናል " ያሉ ነዋሪዎች የፌዴራል መንግስት ጣልቃ እንዲገባ እና ሁኔታው እንዲረጋጋ ጠይቀዋል። ዛሬ በወረዳው ለተፈጠረው…
#ትኩረት

በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን እና ኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር አዋሳኝ አካባቢዎች ያለው የፀጥታ ችግር ተባብሶ ከፍተኛ ውድመት እየደረሰ ይገኛል።

በትላንትናው ዕለት በዚሁ አካባቢ ስላለው ሁኔታ ቤተሰቦቻችን መልዕክት መላካቸው አይዘናጋም።

ዛሬ ደግሞ አጣዬና ጀውሀ እንዲሁም የኤፍራታና ግድም ወረዳ ቀበሌዎች በታጠቁ ኃይሎች ዝርፊያና ውድመት ቃጠሎ እየደረሰባቸው ሲሆን የሚመለከተው አካል ትኩረት እንዲሰጥ እየተጠየቀ ነው።

የሰሞኑን ሁኔታ በተመለከተ አል ዓይን ኒውስ ነዋሪዎችን ዋቢ አድርጎ ባወጣው ዘገባ ፤ የፀጥታ ችግሩ ከአራት ቀናት በፊት መከሰቱንና ተባብሶ መቀጠሉን አመልክቷል።

ነዋሪዎቹ ችግር የተፈጠረው ቅዳሜ ጥር 13 ቀን 2015 ዓ/ም ምሳ ሰዓት በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች በጀውሀ ከተማ ለጸጥታ ስራ በተሰማራ የአማራ ልዩ ሀይል ላይ ጥቃት በመክፈታቸው ነበር ብለዋል።

በጥቃቱ የጀውሀ አስተዳዳሪን እና የአማራ ልዩ ሀይል አባላትን ጨምሮ በድምሩ የ30 ሰዎች ህይወት ማለፉን አመልክተዋል።

ሁኔታው እሁድ ዕለት ጋብ ብሎ የነበረ ቢሆንም ትላንት በጀውሀ፣ ሰንበቴ፣ ሸዋሮቢት ከተማ እና ቀወት ወረዳ ስር ወዳሉ ቀበሌዎች መስፋፋቱ ተገልጿል።

ግጭቱን ለመቆጣጠር ተጨማሪ የአማራ ልዩ ኃይል ከአጣዬ አቅጣጫ ወደ ጀውሀ እና ሸዋሮቢት በመጓዝ ላይ እያለ ሰንበቴ ላይ ከመንገድ ዳር ባደፈጡ ታጣቂዎች ተኩስ እንደተከፈተባቸው ነዋሪዎቹ አመልክተዋል።

ይሄንን ተከትሎ ግጭቱ ከጀውሀ አልፎ ወደ ሰንበቴ እና አጣዬ ሊስፋፋ መቻሉን ተገልጿል።

ያንብቡ : https://telegra.ph/Attention-01-24-4

NB. እስካሁን የመንግስት አካላት በጉዳዩ ዙሪያ የሰጡት ዝርዝር ማብራሪያ የለም።

@tikvahethiopia
#ትኩረት

በሐመር ወረዳ በአየር መዛባት ምክንያት በተከሰተ የዝናብ እጥረት የተነሳ ድርቅ በሰው እና በእንስሳት ላይ የከፋ ጉዳት እያደረሰ በመሆኑ ልዩ ትኩረት ሊደረግበት ይገባል።

በደቡብ ኦሞ ዞን ስር በምትገኘው ሐመር ወረዳ እንደ ሶማሌ እና እንደ ቦረና ሁሉ ለወረዳው ለአርብቶ አደሮች ጊዜው ከፍቷል ተብሏል።

በአየር መዛባት ምክንያት በተከሰተዉ የዝናብ እጥረት የአርብቶ አደሩ የኑሮ መሠረት የሆኑት የቀንድ ከብቶቹ በየጫካና ጥሻዎቹ ውስጥ በተኙበት እየሞቱ ይገኛሉ።

አሁን ላይ በሐመር ድርቁ ዕለት በዕለት የአርብቶ አደሩ መተዳደሪያ የሆኑ የቁም እንስሳትን በከፍተኛ ሁኔታ እየጨረሰ ነው።

ውኃ የለም፤ ሣር የለም። አርብቶ አደሩ የእንስሳት ተዋጽዖ በመመገብ ነው የሚኖረው። ዝናብ የለም በዚህ ምክንያት ብዙ ከብቶች እየሞቱ ነው።

ሰውም በጣም በከፍተኛ ሁኔታ በረሐብ እየተሰቃየ መሆኑን ከወረዳው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በወረዳው ለተከታታይ አራት ዓመት እና በላይ በቂ ዝናብ ባለመጣሉ ነው ድርቁ በከፍተኛ ኹኔታ የተፈጠረው ተብሏል።

የእንስሳት መኖ አለመኖሩ ትልቅ ተጽዕኖ እያሳደረ ሲሆን በየትኛውም አማራጭ ውኃ ማግኘት ወደማይቻልበት ሁኔታ ተደርሷል።

ለ4 አመታትና በላይ በቂ ዝናብ ባለመዝነቡ እንስሳቱ የሚግጡት ሳር ጠፍቷል።

ወንዞች በመድረቃቸው በርካታ ቁጥር ያላቸው የቀንድ ከብቶች ለሰው ልጅ የመጠጥ ውሃ የተቆፈሩ የጉድጓድ ውሃዎችን ፖምፕ እየተደረጉ ለማጠጣት ቢሞከርም ከአቅም በላይ ሆኗል።

የከርሰምድር ውሃ እየሸሸ መሄዱና የፓምፖች ብልሽት እየተከሰተ በመሆኑ በሰው ላይ ከዚህ የከፋ ችግር ከመከሰቱ በፊት መንግስትና አጋር ድርጅቶች እንዲሁም የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።

#ሐመር_ወረዳ

@tikvahethiopia
#ትኩረት

በምስራቅ ሀረርጌ  ዞን የተከሰተው ድርቅ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን የኢትዮጵያ ህጻናት አድን ድርጅት አስታወቀ፡፡

ድርጅቱ በዞኑ ውሃ ፤ የጤናና ሌሎች መሰረታዊ አገልግሎቶች በአፋጣኝ እንደሚያስፈልጉ አሳውቋል።

የኢትዬጵያ ህጻናት አድን ድርጅት የምስራቅ ሀረርጌ ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የሚዲያ ዘርፍ ዳይሬክተር አቶ አብዱራዛቅ አህመድ  " የተከተሰው ድርቅ ከፍተኛ ችግር እያስከተለ በመሆኑ በ35 ወረዳዎች ላይ ድጋፍ ለማድረግ የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ ናቸው " ብለዋል።

ድርጅቱ ከ2 መቶ በላይ ትምህርት ቤቶች ላይ ለተማሪዎች  ምገባ እያደረገ መሆኑን አሳውቀዋል።

በድርቁ ምክንያት ለተፈናቀሉ ዜጎች የጥሬ ገንዘብ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን የገለፁት ዳይሬክተሩ በድርቁ ከ2 ሚሊየን በላይ እንስሳት እስካሁን መሞታቸውን አንስተዋል፡፡

ቦረና ላይ ከተከሰተው ድርቅ ባልተናነሰ በምስራቅ ሀረርጌም በዜጎች እና በእንስሳት ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ገልጸው በዚህ ምክንያት ግን እስካሁን የሞተ ሰው ስለመኖሩ ያገኙት መረጃ እንደሌለ ተናግረዋል፡፡

ድርቁ ነአርሶ አደሩ ላይ ከፍተኛ ጫና እንደፈጠረ የተናገሩት ዳይሬክተሩ ዝናብ ካልዘነበ አሁንም በዞኑ ያለው ችግሩ እየተባባሰ እንደሚመጣ አመልክተዋል።

በዞኑ ካለው ችግር፤ አንፃር የሚደርሰው እርዳታ ተመጣጣኝ እንዳልሆነ አመልክተዋል።

በሌላ በኩል ፤ ድርጅቱ ቦረና ላይ ለደረሰው ድርቅ እርዳታ ተደራሽ ለማድረግ ድጋፎችን እያሰባሰበ መሆኑን አሳውቀዋል።

Credit : አሀዱ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን

@tikvahethiopia
#ትኩረት

በኦሮሚያ እና በሲዳማ ክልል አዋሳኝ አከባቢዎች [ቦጬሳ ቀበሌ - ጭሬ] ካለፈው እሁድ ረፋድ ጀምሮ በተቀሰቀሰ ግጭት የሰዎች ህይወት መጥፋቱ እንዲሁም በዜጎች ንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን በአከባቢው የሚገኙ የቲክቫህ ቤተሰቦች አስታውቋል።

ግጭቱ በተቀሰቀሰባቸው ቦታዎች በርካታ ዜጎች መፈናቀላቸውን ገልጸው #መንግስት ለአከባቢው በቂ የሆነ ትኩረት እንዲሰጥ ፤ የዜጎችንም ደህንነት እንዲያስጠብቅ ጥሪ አቅርበዋል።

በአካባቢው ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ እየተከታተልን እናሳውቃለን።

@tikvahethiopia
#ትኩረት

ከአዲስ አበባ ወደ ጎጃም መስመር በሚያቀኑ የጭነት የተሽከርካሪ ሾፌሮች እና ረዳቶች ላይ " እገታ ተፈፅሟል " ሲሉ የታጋች ቤተሰቦች ገለፁ።

ድርጊቱ ዛሬ ንጋት 12 ሰዓት  " አሊዶሮ " በሚባለው አካባቢ ስለመፈፀሙ አንድ ወንድሜ ታግቷል ያለ የቲክቫህ ቤተሰብ አባል ጠቁሟል።

የታጠቁ አካላት " እስከ ሰላሳ / 30 የሚሆኑ ሰዎችን ከመኪናቸው አስወርደው አግተዋቸዋል ከነሱ ውስጥ ደግሞ አንዱ ወንድሜ ነው " ሲል አስረድቷል።

" ትላንት ነበር ከአ/አ የተነሱት ፤ በለሊት ጉዞ እየተደረገ ስላልሆነ መሃል ላይ መታደር ስላለበት አድረው ዛሬ ንጋት ላይ መኪናቸው እንዳለ እነሱን ግን እንደወሰዷቸው በስልክ ለእናቴ ደውሎ ነግሯታል "  ሲል ይኸው የቤተሰባችን አባል ገልጿል።

" ከዛ በኃላም ቀን 6 ሰዓት ደውሎ ጫካ ውስጥ በእግር እየወሰዱን ነው ከእንግዲህ ከሌለውም ይቅርታ አድርጉልኝ ሲል የመሰናበቻ አይነት መልዕክት ተናግሮ ፤ እናቴን ጨምሮ መላው ቤተሰብ እያለቀሰ ፤ በጭንቀት ላይ ነው ፤ ምናልባት መፍትሄ ከተገኘ በሚል ነው ወደ ሚዲያ የወጣነው " ሲል ሁኔታውን አስረድቷል።

ወንድሙ ሲደውልበት የነበረው ስልክ አሁን ላይ መስራት እንዳቆመ ጠቁሟል።

ወንድሙ በዚህ መስመር (ከአዲስ አበባ - ቻግኒ) ለረጅም አመታት መስራቱን ከዚህ ቀደም እንዲህ ያለውን ነገር  / እገታ አጋጥሞት እነደማያቅ ገልጾ ለቤተሰብ ጭንቀት እረፍት ይሆን ዘንድ የሚመለከተው አካል መፍትሄ ይፈልግ ዘንድ ጥሪ አቅርቧል።

ሌሎች የታጋች ሾፌር ቤተሰቦች ካላችሁም መልዕክታችሁን በ @tikvah_eth_BOT ላይ ልታደርሱን ትችላላችሁ (ከማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ ኮፒ የሚደረጉ መልዕክቶችን ባትልኩ ይመረጣል) ።

በዚሁ በ" ገብረ ጉራቻ  "ቀጠና ከዚህ ቀደም ታጣቂዎች እንደሚንቀሳቀሱ፣ እገታ ፣ እንደሚፈፀም በተደጋጋሚ መነገሩ የሚዘነጋ አይደለም።

ጉዳዩ ይመለከታቸዋል የሚባሉ አካላት በጉዳዩ ዙሪያ የሚሰጡት ማብራሪያ ካለ ተከታትለን እናሳውቃለን።

@tikvahethiopia
#ትኩረት

#ከዳሎቻ ወደ #ወራቤ ያለው መንገድ በአፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጠው ነዋሪዎች ጠይቀዋል።

ከላይ በምስሉ ላይ የምትታየው እናት ምጥ ይዟት ከዳሎቻ ወደ ወራቤ ሆስፒታል ብትላክም በመንገዱ ብልሽት ምክንያት አንቡላንሷ በጭቃ ተይዛ እናትም በጭቃ መሃል እንድትወልድ ተገዳለች።

ከዚህ ባለፈ ከዳሎቻ ወደ ወራቤ ሆስፒታል ሪፈር የተፃፈላት ህፃን በመንገዱ ብልሽት ምክንያት አንቡላንሱ መሃል መንገድ ደርሶ ማለፍ ባለመቻሉ የህፃኗ ህይወት ልያልፍ ችሏል።

መንገዱ ከዳሎቻ ከተማ ጫፍ እስከ ወራቤ ከተማ ጫፍ ቡታጅራ መውጫ የተዘረጋና ርቀቱም ከአስር ኪሎ ሜትር ያነሰ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት በከፍተኛ ሁናቴ ተበላሽቶ ይገኛል። 

በተጨማሪም መንገዱ እጅግ በጣም ጠባብ ፣ በየቦታው የተቆፋፈረ፣ በክረምት ወራት ከባድ ጭቃ፣ በበጋ ጊዜያት አስቸጋሪ አቧራ ያሚበዛበት ሲሆን በተደጋጋሚ የሚጠቀሙት መንገደኞች ላይ ከፍተኛ የጤና መታወክም ሲያደርስ ቆይቷል።

ይህም መንገድ በክልል ገጠር መንገድ በኩል በጠጠር መንገድ ደረጃ ተሰርቶ እያገለገለ ቆይቶ  በየ ጊዜው የተወሰነ ጥገና እየተደረገለት እስካሁን ቢደርስም አሁን ላይ የጉዳቱ መጠን እጅግ ከፍ ያለ ደረጃ መድረሱ ከክረምቱ ወቅት ዝናብ ጋር ተዳምሮ የመስመሩን ጉዞ እጅግ ፈታኝ አድርጎታል።

ስለሆነም የሚመለከተው አካል የመንገዱን አሁናዊ ሁኔታ ተመልክቶ አፈጠኝ ምለሽ ሊሰጠን  ይገባል ሲሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ጠይቀዋል።

(ሰይፈዲን ሉንጫ ከወራቤ)

@tikvahethiopia
#ትኩረት

" #የጨረር_ሕክምና ባለመኖሩ ከ700 በላይ ሕሙማን አገልግሎት ማግኘት አልቻሉም " - ዓይደር ሆስፒታል

የዓይደር ሆስፒታል የካንሰር ሕክምና ማዕከል ኃላፊ ክብሮም ህሉፍ ( ዶ/ር ) ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በገለጹት መሠረት፣ የጨረር ሕክምና ባለመኖሩ ከ700 በላይ ሕሙማን አገልግሎት ማግኘት አልቻሉም።

" ባለፈው ሦስትና አራት ወራት ውስጥ ወደ 800 የሚሆኑ ሪፈር የተፃፈላቸው ፔሸንቶች አሉ " ያሉት ኃላፊው፣ " በመቐለ ዩኒቨርስቲ የተጀመረው የጨረር ሕክምና አግልግሎት መስጫ ህንፃ ግንባታ የፊኒሽንግ ሥራው ስላልተጠናቀቀ ታካሚዎቻችንን ወደ ጥቁር አንበሳ፣ ጅማና ሀረሚያ ሪፈር እያልናቸው ነው " ብለዋል።

አክለውም፣ " ከጦርነት ጋር ተያይዞ፣ የትራንስፖርት መወደድ፣ ከኑሮ ውድነቱ ጋር በተያያዘ ሪፈር ከተባሉት ታካሚዎች መካከል እዚያ የሚደርሱት 10 በመቶ ብቻ የሚሆኑት ብቻ ናቸው። 90 በመቶዎቹ ሕክምና እያስፈለጋቸው አይሄዱም። ምናልባት 80 ወይም 100 የሚሆኑ ታካሚዎች ናቸው የሚሄዱት፣ ቀሪዎቹ ወደ 700 ታካሚዎች ግን እየተጠባበቁ ያሉት ምናልባት እኛ ህንጻውን ከጨረስነው ነው፣ ካልሆነ ግን ሕመሙ ምን እንደሚያደርጋቸው እየጠበቁ ነው " ሲሉ አስረድተዋል።

ክብሮም (ዶ/ር) ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ማብራሪያ ፣ " የጨረር ሕክምና ኢትዮጵያ ውስጥ ስድስት ነበር ለመትከል የታሰበው የዛሬ ስድስት፣ ሰባት ዓመታት። ጥቁር አንበሳ፣ ጅማና ሀረማያ ጀምረዋል። የሀዋሳው ተተክሎ አልቋል፣ የጎንደሩም እንደዚሁ ተቃርቧል" ሲሉ ተናግረው፣ " የእኛ የመቐሌው ግን በዚህ በነበረው ጦርነት ምክንያት፣ ከኮሮና ጋር ተያይዞ፣ መቐሌ ዩኒቨርሲቲ በገጠመው የበጀት እጥረት ሕንፃው ማለቅ አልቻለም " ብለዋል።

የጨረር ሕክምና አገልግሎት መስጫ ሕንፃ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ምን ያህል ገንዘብ እንደሚያስፈልግ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽም፣ የሕንፃውን የፊንሺንግ ሥራዎች በማጠናቀቅ፣ ተገዝቶ የተቀመጠውን ማሽን በመገጣጠም አግልግሎቱን ለመጀመር ቢያንስ ከ60 እስከ 80 ሚሊዮን ብር ወጪ እንደሚጠይቅ ኮንትራክተሮች ተናግረዋል ብለዋል።

አክለውም፣ "በዶ/ር ሊያ የተመራ ልዑክ መቀሌ መጥቶ ነበር ከዚህ በፊት፣ በመጡበት ጊዜ ሕንፃውን ለመጨረስ ቃል ገብተው ነበር የሄዱት" ሲሉ አስታውሰው፣ " የፊኒሽንግ ሥራዎችን ለመጨረስ ብር ሊያግዙን ነበር አሁን ግን ሌሎች ቅድሚያ የሚያስፈልጋቸው የጤና ተቋማት አሉ በሚል እነርሱም እንደማይችሉ ነግረውናል። ትልቁ ችግራችን የጨረር ሕክምና ነው " ሲሉ ተናግረዋል።

በሌላ በኩል ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ በመድኃኒት እጥረት ምክንያት ከ100 በላይ የካንሰር ሕሙማን መሞታቸውን ሆስፒታሉ ከአምስት ወራት በፊት ገልፆ ነበር። አሁን የመድኃኒት እጥረቱ እንደተቀረፈና እንዳልተቀረፈ እንዲያብራሩ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ጥያቄ ቀርቦላቸው በሰጡት ምላሽ፣ "አሁን አዲስ አበባ ያሉት መድኃኒቶች እየመጡልን ነው። ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በተወሰነ መልኩ ከእስከዛሬው አንፃር መሻሻሎች አሉ። ብለዋል።

"አሁንም የተወሰኑ የመድኃኒት እጥረቶች አሉ ያሉት ክብሮም (ዶ/ር) ፣ ምን ያህል ተመላላሽ የካንሰር ታካሚዎች እንዳሉ ሲያስረዱም፣ እስክ 1,500 ተመላላሽ የካንሰር ሕሙማን እንዳሉም ገልጸው፣ "አሁን ትልቁ ያለው ችግራችን የጨረር ሕክምና ነው" ሲሉ አስረድተዋል።

ያንብቡ ፦ https://telegra.ph/TikvahEthiopia-10-19

@tikvahethiopia
#ደራ_ወረዳ #ትኩረት

በደራ ወረዳ ያለው የፀጥታ ችግር አሁንም #አሳሳቢ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ፣ የሰዎች ህይወት እያለፈ ፣ ንብረትም እየወደመ መሆኑን ነዋሪዎች ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገልጸዋል።

የደራ ወረዳ ነዋሪዎች በሰጡት ጥቆማ አንድ የቀድሞ የኦሮሚያ ፖሊስ አባል የልጆቻቸው እናት የሆነች ሚስታቸውን ከ " ኦነግ ሸኔ " ታጣቂዎች ጋር በመወገን ገድለዋል ብለዋል።

አንድ ቃላቸውን ለ ' ቲክቫህ ኢትዮጵያ ' የሰጡ የሟች የቅርብ ቤተሰብ ነኝ ያሉ ግለሰብ ፤ " በደራ ጁሩ የተባለ አካባቢ አንድ የቀድሞ የኦሮሚያ ክልል የፓሊስ አባል ከኦነግ ሸኔ ጋር በመወገን የአራት ልጆቹን እናትና የ5 ወር ነፍሰጡር ሚስቱን ገድሏል " ሲሉ ተናግረዋል።

ሌላኛው የሟች የቅርብ ቤተሰብ ይህ ግድያ በጥቅምት 6 ቀን 2016 ዓ.ም ፤ " ጁሩ " የተባለ አካባቢ ላይ እንደትፈጸመ አስረድተው፣ " የሟቿን እናት ጨምሮ ሌሎች የቤተሰቡ አባላት ጉዳት ደርሶባቸዋል። እኛም ልባችን ተሰብሮ አለን " ብለዋል።

በሌላ በኩል ፤ ሌላኛው የዓይን እማኝ #ጥቅምት_9 በገለጹት መሠረት፣ በደራ ወረዳ " ቆሮ ግንደ በርበሬ " ቀበሌ የኦነግ ሸኔ ጦር አካባቢውን እና መንደሩን ካቃጠለ 2 ሴቶችን እና አንድ ወንድ ገድሏል ሲሉ ከሰዋል።

እንደ ነዋሪው ገለፃ ን በታጣቂ ቡድኑ የተገደሉት ፀጋ እምነት፣ ጌታው አቤቱ እና ለግዜው ስሟን ያላወቁት ሴት ናቸው።

እኚሁ እማኝ ፤ " በመንግሥት ይሁንታ #የደራ_ህዝብ ከፍተኛ የዘር የፍጅት እየደረሰበት ነው " ብለዋል።

ይኸው ዘገባ እየተዘጋጀበት እስከነበረበት ጊዜ ድረስ ታጣቂ ቡድኑ ያለበትን ሁኔታ ሲያስሩዱም፣ " አሁንም በተለያዩ ቀበሌዎች እንደቀጠለ ነው። መንግሥት ምንም እርምጃ አልወሰደም። አድማሱን እያሰፋ ይገኛል " ነው ያሉት።

እኚሁን ምንጭ ጨምሮ ሌሎች የኦሮሚያ እና የአማራ ተወላጅ የደራ ወረዳ ነዋሪዎች ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በገለጹት መሠረት ፣  አሙማ ገንዶ፣ ኢሉ ጎደ ጨፌ ፣ ሀርቡ ደሶ ፣ ዴኙ ወቤንሶ ፣ ጁሩ ዳዳ፣ ሀቼ ኩሳዬ፣ ካራ፣ ጎዲማ ሶስት ዋርካ፣ ጊሊ ወዲሳ፣  ቆሮ ግንደ በርበሬ፣ በዮ ኖኖ፣ ደንቢ ብርጄ፣ ባቡ ድሬ፣ ወሬ ገበሮ፣ መንቃታ፣ የተባሉና ላሎችም ቀበሌዎች እስካሁን (ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ) በታጣቂ ቡድኑ ስር ናቸው ይላሉ።

በሌላ በኩል ደግሞ ፤ በጉዳዩ ዙሪያ ቃላቸውን በስልክ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ የሰጡ የኦሮሚያ ክልል ተወላጅ፣ መከላከያ በአካባቢው እንዳለ፣ እንደ አጠቃላይ ግን ነዋሪው የጸጥታ ችግር ውስጥ እንደሆነ አስረድተው ስማቸው እንዳይጠቀስ ጠይቀዋል።

ሌላኛው ነዋሪ በበኩላቸው ፤ " ፋኖ ታጣቂዎችም አልፎ አልፎ ጥቃት እያደረሱ  ነው። በመካከል እየተጎዳ ያለው ንጹሐኑ ነው። መንግሥት እርምጃ ቢወስድ ምን አለ ? " ሲሉ ተይቀው ተጨማሪ ሀሳብ ለመስጠት ተቆጥበዋል።

የደራ ወረዳ ነዋሪዎች ባለፉት ሳምንታት በርካታ ሰዎች በታጣቂ ቡድኑ እንደታገቱ ፣ ከእገታ ለመለቀቅም ከ500 እስከ አንድ ሚሊዮን ብር እየተጠየቀባቸው እንደነበር፣ በጥቃቱ ከ200 በላይ ሰዎች እንደተገደሉ ፣ በርካታ ቤቶች እንዲሁም አብያተ ክርስቲያናት እንደተቃጠሉ መግለፃቸው ይታወሳል።

የኦሮሚያ ተወላጆችም ፤ " የፋኖ ታጣቂዎች በርካታ ቁጥራቸው ገና በትክክል ያልታወቀ ሰዎችን ገድለዋል " ማለታቸው አይዘነጋም።

መንግሥት " ኦነግ ሸኔ " እያለ በሚጠራው የታጣቂ ቡድን ታገቱ የተባሉ ሰዎች ከምን እንደደረሱ፣ የሟቾች ቁጥር ስንት እንደሆነ፣ የቤት ቃጠሎ ጥቃቱ እንደቆመና እንዳልቆመ ቲክቫህ ኢትዮጵያ ላቀረበው ጥያቄ ፣ " ከ500 ሺህ እስከ 1 ሚሊየን ብር የከፈሉ ተለቀዋል፣ ያልከፈሉትን ገድሏል " ብለዋል ሁኔታውን ሲከታተሉ የነበሩ ታማኝ ምንጭ።

ሌሎች ነዋሪዎች በበኩላቸው፣ የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች የሚሰነዝሩትን ግድያ፣ ቃጠሎ፣ እገታ እንዳላቆሙ የሟቾችን ቁጥር ማወቅ እንዳልተቻለ ግን በመቶዎች የሚቆጠሩ እንደተገደሉ አስረድተው፣ ይህን ልጓም ያጣ ጥቃት መንግሥት ቸል ብሎታል የዓለም መንግሥታት፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ይወቁልን ብለዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ፤ ደረሰ እና አልቆምመ የተባለውን ጥቃት በተመለከተ ምን ምላሽ እንዳላቸው በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን የደራ ወረዳ አስተዳዳሪ ለአቶ ሺበሺን በስልክና በአጭር ጽሑፍ እንዲያብራሩ ጥያቄ ቢያቀርብም #ምላሽ_ለመስጠት_ፈቃደኛ_አልሆኑም

አቶ ሺበሺ ከዚህ በፊት ጉዳዩን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ ችግሩን ለመቅረፍ የጸጥታ ኃይል እጥረት እንዳለ አስረድተው ነበር።

በተጨማሪ ከዞኑ አስተዳደር፣ ከክልሉ የጸጥታ ቢሮ የተደረገው ተመሳሳይ ሙከራ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሳይሳካ ቀርቷል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ፤ በደራ ስላለው ሁኔታ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንን ያነጋገረ ሲሆን " ክትትል ተጀምሯል ግን ገና አላለቀም " የሚል አጭር ምላሽ አግኝቷል።

መረጃው በአ/አ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ተጠናቅሮ የቀረበ ነው።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
" እርዳታው ከተላከ ከአንድ ሳምንት በላይ ሆኖታል እስካሁን ግን ቦታው ላይ አልደረሰም " - ቀይ መስቀል የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ላጋጠመው ድርቅ እርዳታ ቢልክም እስካሁን ቦታው ላይ አልደረሰም። እርዳታው ቦታው ላይ ያልደረሰው በፀጥታ ችግር ነው ብሏል። የማህበሩ የፕሮግራም ኃላፊ አቶ ድረስ ደስይበለው ለሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬድዮ ጣቢያ በሰጡት ቃል ፤ እርዳታው…
#ትኩረት

" ተጨማሪ ሁለት ሰዎች በረሃብ ህይወታቸው አልፏል። ... አካባቢው ረሃብ ብቻ ነው፤ እርዳታም አልመጣም ፤ ሰው እያለቀሰ ነው ያለው " - የቢላዛ ቀበሌ አስተደደር

በዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ፤ ሳህላ ሰየምት ወረዳ ቀበሌ 10 አካባቢ ከረሃብ ጋር በተያያዘ ባለፉት አስር ቀናት ውስጥ የሁለት ሰዎች ህይወት ማለፉ ተሰምቷል።

የቢላዛ ቀበሌ አስተዳደር ሁለት ሰዎች በረብ እንደሞቱ ማረጋገጡን ገልጾ ወደ ሟቾች ቤት ሲኬድ የሚበላም ሆነ የሚጠጣ አንዳች ነገር እንዳልተገኘ አመልክቷል።

ወደ አካባቢው እርዳታ ሊገባ እንዳልቻለ ያመለከተው የቢላዛ አስተዳደር ነዋሪው በከፍተኛ ችግር እና ረሃብ ላይ ነው፤ አካባቢው ረሃብ ብቻ ነው ብሏል።

ከዚህ ቀደም በዚሁ ቀበሌ የመኸር ወቅቱ ድርቅ ባስከተለው ረሃብ 6 ሰዎች የሞቱ ሲሆን በቅርቡ የሞቱትን አንድ አዛውንትና አንዲት ሴትን ጨምሮ የሟቾች ቁጥር 8 መድረሱ ተነግሯል።

ከ4 ሺህ በላይ ህዝብ በሚኖርበት በዚህ ቀበሌ እስካሁን 15 ኪሎ ግራም ፉርኖ ዱቄት የእርዳታ እህል ማግኘት የቻሉት 800 ሰዎች ብቻ ናቸው።

አስተዳደሩ በቂ የእርዳታ እህል እየቀረበ አይደለም ብሏል። አሁንም ቢሆን እርዳታ በአፋጣኝ ካልደረሰ የከፋ ችግር ይከሰታል ሲል አሳስቧል።

አካባቢው ለተሽከርካሪ የማያመች ሲሆን ከፍተኛ የመንገድ ችግርም አለበት። አሁን እየከፋ በመጣው ረሃብ ቀደም ሲል የገባውን እርዳታ ለማጓጓዝ ጥቅም ላይ የዋሉ አህያዎች በመኖ እጥረት ምክንያት አቅማቸው በመዳከሙ እርዳታ ቢገኝ እንኳን ማጓጓዝ አይቻልም ተብሏል።

ከመንገድ በተጨማሪ የክልሉ ወቅታዊ የፀጥታ ሁኔታ የእርዳታ እህል ለተጎጂዎች ለማድረስ አስቸጋሪ እንዳደረገው ተገልጿል።

በሌላ በኩል ፤ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ሰሞኑን ወደ ዋግኽምራ ሳህላሰየትም ወረዳ ሊላክ የነበረው የእርዳታ እህል በፀጥታና ደህንነት ምክንያት ባህር ዳር ላይ ለቀናት እንደቆመ መግለፁ ይታወሳል።

የእርዳታ እህል የጫኑ ተሽከርካሪዎች ወደ ዋግኽምራ እንዳይሄዱ ብቸኛው መንገድ (በማክሰኚት - ምስራቅ በለሳ -አርባያ-ጉአላ) ምቹና አስተማማኝ ስላልነበር እርዳታውን ወደ ሌላኛው ከፍተኛ የድርቅ ተጎጂዎች ወዳሉበት ሰሜን ጎንደር ወረዳዎች እንዲሰጥ መደረጉን ቀይ መስቀል አሳውቋል።

ቀይ መስቀል እርዳታው ወደ ዋግኽምራ እንዳይሄድ የመንገድ ደህንነት ችግር በመሆኑ ከአዲስ አበባም ከወጣ 20 ቀን አካባቢ ባህርዳር ላይ በመቆሙ ከመበላሸቱ በፊት በድርቅ እኩል ለተጎዱ የሰሜን ጎንደር ወረዳዎች እንዲከፋፈል ተደርጓል ብሏል።

አስተማማኝና ምቹ ሁኔታ እስከሚፈጠር ድረስ እርዳታው ወደ ሰሜን ጎንደር መላከው ያስረዳው ቀይ መስቀል ለሳሃላሰየምት ሌላ ድጋፍ ይፈለጋል ሲል አሳውቋል።

የዋግኽምራ አስተዳደር ዞን አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ማስተባበሪያ ወደ ቢላዛ ቀበሌም ሆነ ወደሌሎች አካባቢዎች እርዳታ እንዳይደርስ የመንገድ እና የፀጥታ ችግር ፈተና እንደሆነበት ገልጿል።

ከፌዴራል እና ከክልል መንግስት የተላከ እርዳታ ቢኖርም በቂ እንዳልሆነም ገልጾ በቀጣይ ወር ለተጎጂዎች የተዘጋጀ ምንም ሰብዓዊ ድጋፍ የለም ብሏል።
ስለሆነም፦
- መንግሥት
- መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት
- በጎ አድራጊዎች ሁሉ የእርዳታ እጃቸውን እንዲዘረጉ ተማጽናል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ መረጃውን ያገኘው ቪኦኤ አማርኛው አገልግሎት ነው።

@tikvahethiopia
#ትኩረት

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሃዲያ ዞን፤ ባድዋቾ ወረዳ እና በሾኔ ከተማ በተቀሰቀሰ የኩፍኝ ወረሽኝ የ4 ህጻናትን ጨምሮ የ8 ሰዎችን ህይወት መቅጠፉን የሾኔ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገልጿል።

ከሰሞኑ የተቀሰቀሰው የኩፍኝ ወረርሽኝ በአስደንጋጭ ሁኔታ መዛመቱንና ህይወት መቅጠፉን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ የገልጹት በሾኔ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የኩፍኝ ወረሽኝ ቁጥጥር አስተባባሪው ዶክተር ፋብዬ ግርማ  " ችግሩ ከዚህ በላይ ጉዳት ከማስከተሉ በፊት የሚመለከተዉ አካል ሁሉ አስፈላጊዉን ትብብር ማድረግ ይኖርበታል  " ሲሉ አሳስበዋል።

አሁን ላይ ከሰላሳ በላይ ተጠቂዎች በሆስፒታል ዉስጥ ተለይተዉ ክትትል ላይ የሚገኙ መሆኑን ገልጸው የተወሰኑ ሰዎች በተሰጣቸዉ ህክምና ድነዉ ወደቤታቸዉ መሸኘታቸውን አስረድተዋል።

ዶ/ር ፋብዬ ፤ " አሁን ባለን መረጃ መሰረት በሽታዉ እየተስፋፋ ነው " ያሉ ሲሆን " ማህበረሰቡ ለበሽታዉ ባለዉ ዝቅተኛ አመለካከትና ከጤና ባለሙያዎች የሚሰጠዉን ምክር በአግባቡ ባለመረዳቱ ምክኒያት ጉዳዩ አሳሳቢ ሆኗል " ብለዋል።

" በሽታው በዚህ ሰአት 4 ህጻናትን ጨምሮ 8 ሰዎች ለህልፈት ሲዳረግ በዚህ ምክኒያትም የአካባቢዉን ማህበረሰብ ለከፍተኛ ጭንቀትና ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር እያጋለጠ ነው " ብለዋል።

ከዚህ በተጨማሪ ማህበረሰቡ የህክምና ወጪዉን ራሱ እንዲሸፍን መደረጉ ወደሆስፒታል የመምጣቱን ሁኔታ ዝቅ ማድረጉን የሚገልጹት ዶክተር ፋብዬ አሁን ላይ ሆስፒታሉ በነጻ የሚሰጠዉ አልጋና ኦክስጅን ብቻ ሲሆን የፌደራል መንግስቱ ድጋፍ ሲጀምር መድሀኒቶች በነጻ የመታደል ተስፋ ይኖራቸዋል ብለዋል።

ዘገባዉን ያደረሰን የሀዋሳዉ የቲኪቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ነዉ።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#አማራ #ጎንደር🕯 በአማራ፣ ሰሜን ጎንደር ዞን 3 ወረዳዎች በመሬት መንሸራተት አደጋ የሞቱ እና የተጎዱ ሰዎች ቁጥር በዛሬው ዕለት ጨምሯል። ሟች ወገኖቻችን 23 ደርሰዋል። የአካል ጉዳት የደረሰባቸው ወገኖቻችን ደግሞ  8 መድረሳቸው ተነግሯል። ከቄያቸው የተፈናቀሉ ወገኖቻችን አጠቃላይ ከ2 ሺህ 700 በላይ ናቸው። አደጋው የደረሰው በዞኑ በጠለምት፣ በጃናሞራ፣ በአዲአርቃይና በየዳ ወረዳዎች በሚገኙ…
#ትኩረት🚨

" የመሬት መንሸራተቱ እየጨመረ ነው፡፡ በዞኑ ከ50 ሺሕ በላይ ሰዎች ተፈናቅለዋል " - ዞኑ


በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን በተለያዩ ወረዳዎች በተከሰተው የመሬት መንሸራተት ከ50 ሺሕ በላይ ሰዎች መፈናቀላቸውንና እስካሁን የ5 ሰዎች አስከሬን እንዳልተገኘ ዞኑ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገልጿል።

የዞኑ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሰላምይሁን ሙላት በሰጡት ቃል፤ " የመሬት መንሸራተቱ እየጨመረ ነው፡፡ በዞኑ ከ50 ሺሕ በላይ ሰዎች ተፈናቅላዋል " ብለዋል።

የመሬት መንሸራተቱ ከዚህ ቀደም ካደረሰው ውጪ በሰዎች ሕይወት ላይ ተጨማሪ ጉዳት ባያደርስም በተለይ ጠለምት ወረዳ ላይ እንደቀጠለ መሆኑን አሰድተዋል።

ችግሩ የከፋ ከመሆኑ በሻገር ሊቆም ባለመቻሉ ለአደጋው ተጋላጭ የሆኑ አካባቢዎችን በዘላቂነት ከችግሩ ለማውጣት፣ አደጋው የደረሰባቸውን ወገኖች ለመርዳት የሌሎች ድጋፍ እንደሚያሻው ዞኑ በቲክቫህ ኢትዮጵያ በኩል ጥሪ አቅርቧል፡፡

" ከመንግስት ውጪ ያሉ አካውንቶች ተገቢ አይደሉም፡፡ ግልጽነት የጎደላቸው ናቸው፡፡ የጣምራ አካውንት የተከፈተ አለ " ያሉት ኃላፊው፣ ተከታዩን አካውንት ልከዋል፡።

ድጋፍ ማድረግ የሚሹ በውጪም በውስጥም ያሉ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በንግድ ባንክ አካውንት ቁጥር 1000647478453 ወይም በአማራ ባንክ አካውንት ቁጥር 9900028121157 ድጋፍ እንዲያደርጉ ነው ጥሪ ያቀረቡት።

በመሬት መንሸራተት አደጋው 23 ሰዎች እንደሞቱ፣ 8 ሰዎች የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው፣ 318 የቤት እንስሳት የጉዳቱ ሰለባ እንደሆኑ፣ 1,775 ሄክታር ማሳና 48 ቤቶቾ እንደወደሙ ዞኑ አስረድቷል፡፡

#TikvahEthiopiaFamilyAA

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#Alert🚨 ኦሞ ወንዝ በከፍተኛ ሁኔታ በመሙላቱ የወንዙ ውሃ እና የቱርካና ሀይቅ ይዞታውን እያሰፋ በመሆኑ በኦሞራቴ ከተማ በ1.9 ኪ/ሜ ርቀት አከባቢ በተለያዩ ቦታዎች የመሬት መሰንጠቅ እዲሁም ውሃው ውስጥ ለውስጥ እየሄደ በመሆኑ ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲደረግ የዳሰነች ወረዳ አስተዳደር ጥሪ አቅርቧል። @tikvahethiopia
#ትኩረት🚨

ኦሞራቴ ዙሪያ 500 ሜትር እርዝመትና ሁለት ሜትር ጥልቀት ያለዉ የመሬት መሰንጠቅ ተከስቷል።

የከተማዉ ነዋሪዎች " የመሬት መሰንጠቁ ውሀዉ መድረሱን ያሳያልና ድረሱልን " እያሉ ነው።

ከሰሞኑን የኦሞ ወንዝ መሙላቱን ተከትሎ በርካታ አርብቶ አደሮች መፈናቀላቸውንና አካባቢው በውሀው ከመጥለቅለቁ ባለፈ የወረዳው ዋና ከተማ ኦሞራቴ መቅረቡ የከተማውን ማህበረሰብ ስጋት ውስጥ እንዳስገባው ነግረናችሁ ነበር።

አሁን ደግሞ የተፈጠረዉ የመሬት መሰንጠቅ ሌላ የድንጋጤ ምክኒያት ሆኗል።

ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ቃላቸውን የሰጡ ነዋሪዎች " ውሀው ከመቅረቡ ባለፈ በአካባቢው የመሬት መሰንጠቅ መፈጠሩ በነዋሪው ላይ ከፍተኛ ድንጋጤ ፈጥሯል " ብለዋል።

ውሀው ወደ ከተማው መጠጋቱን ለመከላከል እና አቅጣጫውን ለማስቀየር በሰው ሀይል ጥረት ቢደረግም ውሀው ውስጥ ለውስጥ መጠጋቱን የፈጠረዉ የመሬት መሰንጠቅ ይጠቁማል ብለዋል።

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸዉን የሰጡን የወረዳዉ አስተዳዳሪ አሁን ላይ ህዝቡን ያሰጋዉ አምስት መቶ ሜትር ርዝመትና ሁለት ሜትር ጥልቀት ያለው የመሬት መሰንጠቅ በመፈጠሩ ነው ብለዋል።

አንድ ዶዘር መድረሱንና ስካቫተር እየመጣ መሆኑን ጠቁመው ይህም የውሀዉን አቅጣጫ ለመቀየርና ለማፍሰስ ይረዳል በማለት ይህም እየተከሰተ ያለውን የመሬት መሰንጠቅ አስቁሞ ማህበረሰቡን ያረጋጋል ብለዋል።

አሁን ላይ ምንም እንኳን ዶዘር መድረሱና ስካቫተር እየመጣ መሆኑ ተስፋ ቢሰጠንም የነዳጅ የሰዉ ሀይልና አጠቃላይ ኦፕሬሽን ኮስት ስለሚያስፈልገን የክልሉና የፌደራሉ መንግስት ሊያግዘን ይገባል ብለዋል።

#TikvahEthiopiaFamilyHW

@tikvahethiopia
#ትኩረት🚨

ዛሬም ድረስ የሰው ህይወት የሚቀጠፍባቸው የመስቃን እና ማረቆ ልዩ ወረዳዎች ነዋሪዎች " በፈጣሪ ስም መፍትሄ ይፈለግልን ፤ ተሰቃየን ህይወታችን በሰቀቀን መግፋት ደከመን " ሲሉ በቲክቫህ ኢትዮጵያ በኩል ጥሪ አቅርበዋል።

" ተደጋጋሚ እርቅ ይፈጸማል ግን ሳይቆይ ያገረሽና ደም ይፈሳል፣ ሰው ይገደላል የምንገባበት አጣን ድምጻችን ይሰማ " ብለዋል።

ከሰሞኑን በመስቃን እና ማረቆ ልዩ ወረዳዎች የ9 ሰዎች ህይወት ማለፉን ተከትሎ የአካባቢዉ ባለስልጣናት መታሰራቸውን ቲክቫህ ኢትዮጵያ ሰምቷል።

ባለፉት ጊዜያት የነበረዉ የንጹሀን ግድያ  ለተወሰነ ጊዜ ረገብ ቢልም ከሰሞኑ እንደገና ባገረሸ ግጭት የ9 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ 4 ሰዎች ደግም ቆስለዋል።

ይህን ተከትሎ አካባቢዉ ውጥረት ዉስጥ በመግባቱ አሁን ላይ በአካባቢዉ የሚኖሩ ንጹሀን በፍርሀት ውስጥ ናቸው።

" ኢንሴኖ ከተማና አካባቢው በየጊዜው በሚነሳው ግጭት ገጠራማው ቀበሌ የሚኖረው ምስኪን ግድያ ሲፈጸምበት ቆይቷል " የሚሉት ነዋሪዎቹ " በአካባቢው ሲስተዋል የነበረዉ የበቀል መጠፋፋት አሁንም በከፋ ሁኔታ ተመልሶ ይመጣል በሚል ተጨንቀናል " ሲሉ ገልጸዋል።

ከሰሞኑ በማረቆ ልዩ ወረዳ በሌሊት በተፈጸመ ጥቃት የ7 ሰዎች ህይወት (4ቱ የአንድ ቤተሰብ አባላት) እንዲሁም በመስቃን ደግሞ 2 ሰዎች ህይወታቸው መቀጠፉን የሚናገሩት ነዋሪዎቹ ሁኔታውን የመንግስት አካላት ቶሎ ካልተቆጣጠሩት ግጭቱ ከፍ ሊል ይችላል ሲሉ ፍርሀታቸውን አስረድተዋል።

ስለሁኔታዉ የጠየቅናቸዉ የምስራቅ ጉራጌ ዞን ሰላምና ጸጥታ ኃላፊዉ አቶ ተካልኝ ንጉሴ ስለሁኔታው መረጃ ከመስጠት ተቆጥበዋል።

ይሁንና በልዩ ወረዳዎቹ ግድያ መፈጸሙን ተከትሎ አካባቢውን ለማረጋጋት ወደቦታው ያቀናው የጸጥታ ኃይል ጥቂት የአካባቢው ግለሰቦችን ጨምሮ ግጭት በተፈጠረባቸዉ አካባቢዎች ለጊዜዉ ስማቸዉ አይጠቀስ የተባሉ የወረዳ ከፍተኛ ባለስልጣናትን በህግ ቁጥጥር ስር ማዋሉን ለማወቅ ተችሏል።

አሁን ላይ ኢንሴኖን ጨምሮ በሌሎች አካባቢዎች የፌደራልና የክልል የጸጥታ አካላት ተሰማርተው ህዝቡን እያረጋጉ ሲሆን የህዝቡ እንቅስቃሴ ግን በጅጉ መቀዛቀዝ ይስተዋልበታል።

ይህ አካባቢ በተደጋጋሚ የሰዎች ህይወት የሚቀጠፍበት ፣ ዜጎች የሚፈናቀሉበት ሲሆን ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄ ሳይገኘ ዛሬም በዛው ቀጥሏል።

#Update : ከመሸ ስልክ ያነሱልን የምስራቅ ጉራጌ ወንጀል መከላከል ዲቪዥን ኃላፊ ኮማንደር መሀመድ ሀሰን " አሁን ላይ ሁሉም አካባቢ ሰላም " መሆኑን ጠቅሰው ስለሁኔታው አሁን ላይ መረጃ መስጠት ከባድ መሆኑን ገልጸዋል።

#TikvahEthiopiaFamilyHW

@tikvahethiopia