#ትኩረት

" #የጨረር_ሕክምና ባለመኖሩ ከ700 በላይ ሕሙማን አገልግሎት ማግኘት አልቻሉም " - ዓይደር ሆስፒታል

የዓይደር ሆስፒታል የካንሰር ሕክምና ማዕከል ኃላፊ ክብሮም ህሉፍ ( ዶ/ር ) ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በገለጹት መሠረት፣ የጨረር ሕክምና ባለመኖሩ ከ700 በላይ ሕሙማን አገልግሎት ማግኘት አልቻሉም።

" ባለፈው ሦስትና አራት ወራት ውስጥ ወደ 800 የሚሆኑ ሪፈር የተፃፈላቸው ፔሸንቶች አሉ " ያሉት ኃላፊው፣ " በመቐለ ዩኒቨርስቲ የተጀመረው የጨረር ሕክምና አግልግሎት መስጫ ህንፃ ግንባታ የፊኒሽንግ ሥራው ስላልተጠናቀቀ ታካሚዎቻችንን ወደ ጥቁር አንበሳ፣ ጅማና ሀረሚያ ሪፈር እያልናቸው ነው " ብለዋል።

አክለውም፣ " ከጦርነት ጋር ተያይዞ፣ የትራንስፖርት መወደድ፣ ከኑሮ ውድነቱ ጋር በተያያዘ ሪፈር ከተባሉት ታካሚዎች መካከል እዚያ የሚደርሱት 10 በመቶ ብቻ የሚሆኑት ብቻ ናቸው። 90 በመቶዎቹ ሕክምና እያስፈለጋቸው አይሄዱም። ምናልባት 80 ወይም 100 የሚሆኑ ታካሚዎች ናቸው የሚሄዱት፣ ቀሪዎቹ ወደ 700 ታካሚዎች ግን እየተጠባበቁ ያሉት ምናልባት እኛ ህንጻውን ከጨረስነው ነው፣ ካልሆነ ግን ሕመሙ ምን እንደሚያደርጋቸው እየጠበቁ ነው " ሲሉ አስረድተዋል።

ክብሮም (ዶ/ር) ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ማብራሪያ ፣ " የጨረር ሕክምና ኢትዮጵያ ውስጥ ስድስት ነበር ለመትከል የታሰበው የዛሬ ስድስት፣ ሰባት ዓመታት። ጥቁር አንበሳ፣ ጅማና ሀረማያ ጀምረዋል። የሀዋሳው ተተክሎ አልቋል፣ የጎንደሩም እንደዚሁ ተቃርቧል" ሲሉ ተናግረው፣ " የእኛ የመቐሌው ግን በዚህ በነበረው ጦርነት ምክንያት፣ ከኮሮና ጋር ተያይዞ፣ መቐሌ ዩኒቨርሲቲ በገጠመው የበጀት እጥረት ሕንፃው ማለቅ አልቻለም " ብለዋል።

የጨረር ሕክምና አገልግሎት መስጫ ሕንፃ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ምን ያህል ገንዘብ እንደሚያስፈልግ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽም፣ የሕንፃውን የፊንሺንግ ሥራዎች በማጠናቀቅ፣ ተገዝቶ የተቀመጠውን ማሽን በመገጣጠም አግልግሎቱን ለመጀመር ቢያንስ ከ60 እስከ 80 ሚሊዮን ብር ወጪ እንደሚጠይቅ ኮንትራክተሮች ተናግረዋል ብለዋል።

አክለውም፣ "በዶ/ር ሊያ የተመራ ልዑክ መቀሌ መጥቶ ነበር ከዚህ በፊት፣ በመጡበት ጊዜ ሕንፃውን ለመጨረስ ቃል ገብተው ነበር የሄዱት" ሲሉ አስታውሰው፣ " የፊኒሽንግ ሥራዎችን ለመጨረስ ብር ሊያግዙን ነበር አሁን ግን ሌሎች ቅድሚያ የሚያስፈልጋቸው የጤና ተቋማት አሉ በሚል እነርሱም እንደማይችሉ ነግረውናል። ትልቁ ችግራችን የጨረር ሕክምና ነው " ሲሉ ተናግረዋል።

በሌላ በኩል ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ በመድኃኒት እጥረት ምክንያት ከ100 በላይ የካንሰር ሕሙማን መሞታቸውን ሆስፒታሉ ከአምስት ወራት በፊት ገልፆ ነበር። አሁን የመድኃኒት እጥረቱ እንደተቀረፈና እንዳልተቀረፈ እንዲያብራሩ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ጥያቄ ቀርቦላቸው በሰጡት ምላሽ፣ "አሁን አዲስ አበባ ያሉት መድኃኒቶች እየመጡልን ነው። ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በተወሰነ መልኩ ከእስከዛሬው አንፃር መሻሻሎች አሉ። ብለዋል።

"አሁንም የተወሰኑ የመድኃኒት እጥረቶች አሉ ያሉት ክብሮም (ዶ/ር) ፣ ምን ያህል ተመላላሽ የካንሰር ታካሚዎች እንዳሉ ሲያስረዱም፣ እስክ 1,500 ተመላላሽ የካንሰር ሕሙማን እንዳሉም ገልጸው፣ "አሁን ትልቁ ያለው ችግራችን የጨረር ሕክምና ነው" ሲሉ አስረድተዋል።

ያንብቡ ፦ https://telegra.ph/TikvahEthiopia-10-19

@tikvahethiopia