TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#Amhara

በሰሜን ሸዋ ዞን ሞጃና ወደራ ወረዳ አይሱዚ በተባለው የጭነት ተሽከርካሪ ላይ ሰኞ ዕለት ተፈፅሟል በተባለ የድሮን ጥቃት ከ30 በላይ ሰዎች መገደላቸውን የሟች ቤተሰቦች ተናግረዋል።

ለደህንነቴ ስለምሰጋ ስሜን አትጥቀሱብኝ ያሉ በርካታ ሟቾች ዘመዶቼ ናቸው ያሉ ነዋሪ ለቪኦኤ በሰጡት ቃል ፤ በጭነት ተሽከርካሪ ላይ የነበሩት አብዛኞቹ ቤተክርስቲያንን ልጅ ክርስትና አስነስተው ወደ መኖሪያ ቤት እየተመለሱ የነበሩ ናቸው ብለዋል።

እኚሁ ነዋሪ ምን አሉ ?

- ጥቃቱ ከደረሰባቸው ውስጥ የኔ ዘመዶች ይገኙበታል። ሳሲት ከተማ ክርስትና ላይ ውለው ሲመለሱ ነበር።

- ከሰላ ድንጋይ ወደ ሳሲት ጦርነት እየቀረበ ሲመጣ ሙሉ ቤተሰብ የነበራቸውን የራሳቸውን ተሽከርካሪ ተጠቅመው ወደ ትውልድ ቄያቸው ሲጓዙ ነው ጥቃት የተፈፀመው።

- ከ40 በላይ ሰዎች ነበሩ ነው የተባለው ፤ መኪናው በአካባቢው የነበረውን ጦርነት በመሸሽ ላይ የነበሩ ሰዎችንም ጭምር እያሳፈረ ነው የሄደው።

- የእኔ ቤተሰቦች፦ የአክስቴ ልጆች እህትና ወንድም የነበሩ፣ በወንድምየው ወገን 7 ልጆች ነበሩ አንድ ላይ (እስከነ ሚስቱ) አቶ ምሳው ይባላል፣ እህቱ ሸዋለፋ ትባላለች እሷ እስከነልጇ ነበረች አጠቃላይ 6 ቤተሰብ ነው ያለቀው። በሌላ በኩል፤ የአባቴ ወገን፣ ዘመዶች፣ አክስቶቼ ነበሩ ፤ ቄስ ንጉሴ እስከነባለቤታቸው አጠቃላይ 8 ቤተሰብ፣ ክርስትና አንሺ የነበረው የባልየው ወንድም ዘየደ እስከነ ሹፌሩ፣ ጎረቤታቸው አቶ ማመዬ አጠቃላይ የአጎቴና የአክስቶቼ ልጆች የስጋ ዘመዶቼ አልቀዋል።

- በጥቃቱ አስከፊነት ምክንያት ማንነታቸው ሳይለዩ የተቀበሩ አሉ። ወደ ጤና ተቋማት ሄደው የሞቱም አሉ።

- ጥቃቱ በይበልጥ በግራ በኩል ነው ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰው።

- ክርስትና የተነሳው ህፃን በአያቱ እቅፍ ውስጥ የነበረ ሲሆን ከአያቱ ጋር በህይወት መትረፍ ችሏል። ወላጆቹ ግን ህይወታቸው አልፈዋል።

- ቦታው ከጦርነት ቀጠና 15 ኪ/ሜ ይርቃል። ማንም እዛ ጥቃት ይፈፀማል ብሎ አልገመተም።

- ጥቃቱ ማህበረሰቡን ያስደነገጠ ነው። ከዚህ ቀደም በአካባቢው እንደዚህ አይነት ነገር ስላልነበር።

- ስትጓዙ ተጠንቀቁ። አንዳንድ ተሽከርካሪዎች ላይ አትጓዙ። ትራንስፖርት መጠቀም ከባድ ሆኗል።

- መንግሥት ህዝብን ለማስተዳደር እስከተመረጠ ድረስ የመረጠው ህዝብ ላይ እንዲህ ያለው ጥቃት ማድረስ የማይጠበቅ ነው። ተዋጊና ተዋጊ ምንም አይነት ጉዳት ቢደርስ ሁለቱም አስቦበት ነው። ሰላማዊ ሰዎች ላይ እንዲህ ያለው ጥቃት ሲደርስ መንግሥት ኃላፊነቱን ቢወስድ።

- መንግሥት ጉዳዩን በቅርበት አይቶ የተፈፀመውን ጥቃት ቢመረምርልን የሚል መልዕክት አለኝ።

ጥቃቱ በደረሰበት ወቅት በመከላከያ እና የፋኖ ታጣቂዎች መካከል " ሰላድንጋይ " ላይ ግጭት እንደነበር አሁን ላይ ግን እንደሌለ መከላከያም በከፍተኛ ቁጥር ወደ ስፍራው ገብቶ አካባቢውን እንደተቆጠር ተነግሯል።

ይህን የሰሜን ሸዋ ጉዳይ በተመለከተ እስካሁን በመንግሥት በኩል የተሰጠ ምንም ምላሽ የለም። መገናኛ ብዙሃን ምላሽ ለማግኘት ጥረት ቢያደርጉም እንዳልተሳካ አሳውቀዋል።

ነገር ግን ከወራት በፊት መንግሥት ፦
- ድሮን የታጠቀው አለኝ ለማለት ሳይሆን ልክ እንደሌለው ማሳሪያ ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሆነ ፣
- የፀጥታ ኃይሉ ድሮ በንፁሃን ላይ እንደማይጠቀም ፤
- ድሮ ጥቅም ላይ የሚውለው ለስብስብ ኢላማ እንደሆነ በዚህም ከመንግሥት ጋር የገጠመው የታጣቂው ስብስብ ዒላማ ሲገኝ እንደሚመታ
- ህዝብ ላይ ድሮን እንደማይጣል ፣ መንደር ላይ እንደማይተኮስ ፣
- የታጣቂ ኃይሎች ምርጥ ኢላማ ሲገኝ እንደሚተኮስ
- ድሮን ጥቅም ላይ ሲውል ለህዝብ ጥንቃቄ እንደሚደረግ አሳውቆ ነበር።

@tikvahethiopia
#Amhara

የአቶ ዮሐንስ ቧያለውን ያለመከሰስ መብት ማንሳቱን የአማራ ክልል ምክር ቤት አሳወቀ።

የአማራ ክልል ምክር ቤት በ6ኛ ዙር 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባዔ የክልሉ ም/ቤት አባል የነበሩት የአቶ ዮሐንስ ቧያለውን ያለመከሰስ መብት አንስቷል።

አቶ ዮሐንስ ከወራት በፊት በቁጥጥር ስር መዋላቸው ይታወሳል።

የቀድሞው የአማራ ክልል ባለልስጣን ለረጅም ጊዜ በተለያየ የስልጣን እርከን ሲሰሩ የቆዩ ሲሆን በኃላ ላይ ከመንግሥት ጋር መቃቃር ውስጥ ገብተው ነበር።

ከወራት በፊትም በአማራ ክልል ከተፈጠረው አለመረጋጋት ጋር ተያይዞ ለእስር መዳረጋቸው መነገሩ ይታወሳል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
" መስመሩ መበጠሱን ነው እንጂ ያረጋገጥነው በምን ምክንያት እንደተበጠሰ ማወቅ አልቻልንም " - አቶ ሞገስ መኮንን ከባህር ዳር - በደብረታቦር - ንፋስ መውጫ - ጋሸና - አላማጣ የተዘረጋው ባለ 230 ኪሎ ቮልት የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር እንዲሁም ከደብረ ብርሃን - ሸዋሮቢት - ኮምቦልቻ የተዘረጋው መስመር በመበጠሱ በሰመና መቐለን ጨምሮ በበርካታ ከተሞች ኃይል ተቋርጧል። ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ…
#Amhara

አብዛኛው የአማራ አካባቢዎች ኃይል በመቋረጡ በጨለማ ተውጠዋል።

ኃይል የተቋረጠው በኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር ላይ መበጠስ አጋጥሞ እንደሆነ ቲክቫህ ኢትዮጵያ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያገኘው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል እንዳሳወቀው ትላንት ከባህር ዳር - በደብረ ታቦር፣ ንፋስ መውጫ፣ ጋሸና፣ አላማጣ የተዘረጋው ባለ230 ኪሎ ቮልት የከፍተኛ የኃይል ማስተላለፊያ መስመር ተበጥሷል። በተመሳሳይ ከደብረ ብርሃን፣ ሸዋሮቢት፣ ኮምቦልቻ የተዘረጋውም ተበጥሷል።

የተቋሙ የኮሚኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሞገስ መኮንን እነዚህ ሁለት መስመሮች በምን ምክንያት ነው የተበጠሱት ተብሎ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ለቀረበላቸው ጥያቄ ፤ " መስመሩ መበጠሱን እንጂ ያረጋገጥነው በምን በምን ምክንያት እንደተበጠሰ ማወቅ አልቻልንም " ሲሉ መልሰዋል።

መቼ ነው እሺ የተበጠሱት መስመሮች ተጠግነው ህዝቡ ኃይል የሚያገኘው በሚል ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ለቀረበው ጥያቄ ፤ " በቀላል የሚገናኙ መስመሮች ይኖራሉ ፤ በቀላል ሊገናኙ የማይችሉ እና የተበጠሰበትን ቦታ ብቻ ሳይሆን መስመር መቀየር የሚያስፈልጉም ሊኖሩ ስለሚችሉ እነዚህን እርግጠኛ ባልሆንንበት በዚህ ቀን ሊባል አይችልም " የሚል ምላሽ ነው የሰጡት።

በሌላ በኩል ፤ የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ትላንት ሌሊት ባሰራጨው መግለጫ የአማራ አብዛኛው ክፍል በጨለማ የተዋጠው ንፋስ መውጫ አካባቢ የባለ 230 ኪሎ ቮልት የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊ መስመር አንደኛው ፌዝ በክልሉ በሚንቀሳቀሱት " ፅንፈኛ " ሲል በጠራቸው ታጣቂዎች በመሳሪያ በመመታቱ ነው ሲል አሳውቋል።

" ይህም ህዝቡን በማሰቃየት የተወሳሰበ ችግር ውስጥ መክተት ፣ እና ክልሉን ወደ ጨለማ የመውሰድ እንቅስቃሴ ነው " ብሎ ይህ የሚደረገው ህዝብ እንዲማረር በማድረግ ለትግል ለማነሳሳት ነው ብሏል። " ይህ ዘዴ ያረጀ ያፈጀ ፣ ያለፈበትና የተነቃበት የትግል ስልት ነው " ሲል በመግለጫው ላይ ገልጿል።

በአማራ ክልል በመንግሥት እና በፋኖ ታጣቂ ኃይሎች መካከል የትጥቅ ግጭት መካሄድ ከጀመረ ወራት ተቆጥረዋል።

ክልሉ ገና ከሰሜኑ ጦርነት ባላገገመበት ወቅት የተቀሰቀሰ ሲሆን የትጥቅ ግጭቶቹ በተለያየ ቦታ እና ጊዜ እየተካሄዱ ናቸው። በዚህም የበርካቶች ህይወት እየጠፋ፣ ንብረት እየወደመ ፣ የክልሉ ኢኮኖሚም እያዳከመው መጥቷል።

በግጭቱ ምክንያት የዳታ ኢንተርኔት ከተዘጋ በርካታ ወራት ያለፈ ሲሆን አሁን ደግሞ በከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር መበጠስ አብዛኛው የአማራ ክፍል በጨለማ ውስጥ ገብቷል።

@tikvahethiopia
#Amhara

“ ወደ 1.8 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች የዕለት ምግብ ይፈልጋሉ ” - አማራ ክልል 

የአማራ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ማስተባበሪያ ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙት ኃላፊ ወ/ሮ ፍቅሬ ሙሉጌታ፣ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል፣ በክልሉ “ በአጠቃላይ ወደ 1.8 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች የዕለት ምግብ ይፈልጋሉ ” ብለዋል።

“ በአማራ ክልል በ2015/16 የምርት ዘመንን ተከትሎ የዝናብ መቆራረጥ ተከስቷል። በተለይ ደግሞ ተከዜ ተፋሰስ የሚያዋስናቸው ወረዳዎችና ዞኖች ድርቅ ተከስቶባቸል” ሲሉም አስረድተዋል።

* “ዘጠኝ ዞኖች
* 43 ወረዳዎች 
* 429 ቀበሌዎች ላይ ተጋላጭ ሆነዋል ለድርቅ ” ነው ያሉት ኃላፊዋ።

በገለጻው መሠረት፣ “ከተጎዱት ዘጠኝ ዞኖች ውስጥ በተለይ ደግሞ በጣም ተጋላጭ የሆኑት ከሰሜን ጎንደር 3 ወረዳዎች፣ ከዋግኽምራ ብሔረሰብ 3 ወረዳዎች በብዛት ተጋላጭ ሆነዋል በድርቁ። " ብለዋል።

“ የድርቅ መከሰትን ተከትሎ የዕለት የምግብ ምላሽ ለመስጠት የክልሉ መንግስት ከመጠባበቂያ በጀት መድቧል ” ያሉት ወ/ሮ ፍቅሬ፣ “ወደ 430 ሚሊዮን ብር የክልሉ መንግሥት ፈቅዷል የዕለት ምግብ የሚገዛበት። ከዚህ ውስጥ ወደ 300 ሚሊዮን ብር የምግብ እህል ተገዝቷል። ስርጭትም ተከናውኗል” ሲሉ ተናግረዋል።

አክለውም፣ “ከዚህ ባሻገር ደግሞ የተለያዩ በጎ አድራጊ ግለሰቦች፣ መግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ልዩ ልዩ ተቋማት እንደዚሁ ባገኙት መረጃ መሠረት በተለያየ ጊዜ የምግብ እህል እየገዙ እያጓጓዙ እያቀረቡ ነው” ብለዋል።
 
ድርቅ ከተጋረጠባቸው ወገኖች ባሻገር በክልሉ መጠለያዎች ጣቢያዎች፣ ከህብረተሰቡ ጋር የሚኖሩ ተፈናቃዮች እንዳሉ የገለጹት ኃላፊዋ፣ “ላለፉት 2 ዓመታት የሰሜኑ ጦርነት ነበረ አሁንም የፀጥታ ችግር አለ በክልሉ። እነዚህ ጉዳዩች ተደራራቢ ችግር እንዳለ ያሳያን። ይህን መሰረት በማድረግ ስራዎች እየተሰሩ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

በክልሉ ያለው የጸጥታ ችግር አለ ለስራዎች እንቅፋት እየሆነ መሆኑን አመልክተዋል።

“የፀጥታው ችግር የዕለት ምግብ ለማድረስ በትራንስፖርት ለመንቀሳቀስ ችግር ፈጥሮብን ቆይቷል። በቀጣይም ተደራራቢ ችግሮች ናቸው። እነዚህ ተደራራቢ ችግሮች ህብረተሰቡ ችግር ላይ እንዳይወድቅ የሚላኩት የድጋፍ እህሎች በወቅቱ ሊደርሱ ይገባልና በየአካባቢው የሚጓጓዙት ትራንስፖቴሽኖችን ሊተባበሯቸው ይገባል ” ሲሉ አሳስበዋል።

መረጃው ተዘጋጅቶ የተላከው በአ/አ ቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ነው።

@tikvahethiopia
#Amhara

በአማራ ክልል ከመንግሥት የፀጥታ ኃይል ጋር የትጥቅ ትግል እያደረጉ የሚገኙት እና ታጥቀው የሚንቀሳቀሱት እነ ምሬ ወዳጆን ጨምሮ 27 ተከሳሾች #የጋዜጣ_ጥሪ እንዲደረግላቸው እና እንዲቀርቡ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መስጠቱ ተሰማ።

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 2ኛ የህገ መንግስትና በህገ መንግስት ስርዓት ላይ የሚፈጸሙ የወንጀል ጉዳዮችን የሚመለከተው ችሎት ፤ በሽብር ወንጀል በተከሰሱት እነ ዶክተር ወንደሰን አሰፋ መዝገብ ተካተው ያልቀረቡ ተከሳሾች የጋዜጣ ጥሪ እንዲደረግላቸውና ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ማዘዙን ኤፍ ቢ ሲ ዘግቧል።

የጋዜጣ ጥሪ ይደረግላቸውና ይምጡ የተባሉት በአሁን ሰዓት ነፍጥ አንግበው በአማራ ክልል እየተንቀሳቀሱ የሚገኙት ምሬ ወዳጆን ጨምሮ 27 ተከሳሾች ናቸው።

እነ ዶክተር ወንደሰን አሰፋ እና መስከረም አበራን ጨምሮ 23 ተከሳሾች በአማራ ክልል ካለው ሁኔታ ጋር በተያያዘ ታስረውና " በሽብር ወንጀል " ተከሰው የፍርድ ሂደታቸው እየታየ እንደሆነ ይወቃል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
“ ከ4,000 በላይ ሴቶች ተደፍረዋል ” - የአማራ ክልል ሴቶች ማኀበር የኢትዮጵያ ሴቶች ማኀበር ሴቶች ላይ እየደረሱ ናቸው የተባሉ ፈርጀ ብዙ ችግሮችን በተመለከተ በየክልሉ በዘርፉ የተሰማሩ ተቋማትን በመጋበዝ ትላንት ረቡዕ በአዲስ አበባ ኢሊሊ ሆቴል የውይይት መድረክ አዘጋጅቶ ነበር። በዚህም ላይ ከተገኙት ባለድርሻ አካላት መካከል የአማራ ክልል ሴቶች ማኀበር አንዱ ነው። በአማራ ክልል በ “ፋኖ”…
#Amhara

“ ' 4 ሺህ ሴቶች ተደፍረዋል ' በሚል ያልተረጋገጠ ሀሳብ አንስተዋል ” - ወ/ሮ ሁሉአየሽ አወቀ

የኢትዮጵያ ሴቶች ማኀበር ፤ ሴቶች ላይ እየደረሱ ናቸው የተባሉ ፈርጀ ብዙ ችግሮችን በተመለከተ በየክልሉ በዘርፉ የተሰማሩ ተቋማትን በመጋበዝ ባለፈው የካቲት 20 ቀን 2016 ዓ/ም በአዲስ አበባ የውይይት መድረክ አዘጋጅቶ እንደነበርና ቲክቫህ ኢትዮጵያም መረጃ ማጋራቱ ይታወሳል።

በወቅቱ የአማራ ሴቶች ማኀበርን የወከሉት ወ/ሮ በላይነሽ ሽባባው ስለሴቶች በአማራ ክልል ያለውን ሁኔታ ለተሳታፊዎችና ኃላፊዎች ገለጻ ሲያደርጉ፣ “ አማራ ክልል ራሱ የበፊቱን እንኳን ትተነው አሁን በሚስተዋለው ግጭት ብቻ ከ4,000 በላይ ሴቶች #ተደፍረዋል ” ሲሉ ገልጻ አድርገው ነበር።

ይህንንም ቲክቫህ ኢትዮጵያ ዘግቦት እንደነበር ይታወሳል።

ሆኖም የአማራ ክልል ሴቶች ማኀበር ምክትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ሁሉአየሽ አወቀ፣ ዘገባው ከተሰራ በኋላ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል፣ የወ/ሮ በላይነሽን ገለጻ መሠረት በማድረግ የተዘገበውን ዜና ጠቅሰው፣ “ የእናንተ ስህተት አይደለም በእርግጥ የልጆቷ ስህተት ነው ” ብለው ዘገባው #ማስተካከያ እንዲደረግበት ጠይቀዋል።

ወ/ሮ በላይነሽ በስብሰባው ላይ ያደረጉት ገለጻ የድምጽ ቅጅ እንደገና ሲረጋገጥ፣ “ 4 ሺህ ሴቶች ተደፍረዋል ” የሚል ሆኖ እያለ፣ መረጃውን የት እንዳገኙት እንዲገልጹ የአማራ ሴቶች ማኀበር ሲጠይቃቸው፣ “ ‘4 ሺህ የተባለው እንደ ኢትዮጵያ የቀረበ እንጂ እኔ አላልኩም፣ 400 ነው ያልኩት " ሲሉ ለመካድ እንደሞከሩ ያስረዱት ም/ዳይሬክተሯ፣ “ 400 ከየት አመጣሽ ? ሲባል ‘ከሴቶች ሕጻናት ጉዳይ ቢሮ ሲባል ሰምቼ ነው’ የሚል ሀሳብ ነው ያመጣች ግን 400ም የእኛ መረጃ አይደለም ” ብለዋል።

አክለው “ የ6 ወራት ሪፓርታችንም ‘ፆታዊ ጥቃት ደረሰብን’ ብለው ተቋማችን ድረስ የመጡ 4 ሴቶች ናቸው። እነዚያን ሴቶችም ሁለቱን ሰጥተናል። ሁለቱን ከፓሊስ ጋ ሁነን ገና በሂደት ላይ ያለ ጉዳይ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ በበኩሉ አንድ ሰው ከአንድ ተቋም ሲላክ ታምኖበት፣ ዘርፉን ያውቀዋል ተብሎ ነውና የሚላከው ባለሙያዋ የተናገረችው ስህተት መሆኑን እንዴት ነው የምታረጋግጡልኝ ? የሚል ጥያቄ ለም/ዳይሬክተሯ ወ/ሮ ሁሉአየሽ አቅርቧል።

“ እውነት የምነግርህ እኔ ምክትል ዳይሬክተር ነኝ ፤ ልጅቷ ፕላንድ የሚባል ፕሮጀክት አለ የእርሱ አስተባባሪ ነች ” ያሉት ም/ ዳይሬክተሯ፣ “ ዙሮ ዙሮ ግን እርግጠኛ ሆኘ የምነግርህ ክልሉ ያለበት ሁኔታ ይታወቃል። ቁጥሩ ከዚህ በላይ ሊሆንም ይችላል፣ ሊያንስም ይችላል፣ ስትሰበስበው ነው የምታገኘው ” ሲሉ አስረድተዋል።

ተቋማቸው መልዕክቱን በሰነድ መልኩ እንዲልክ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ተጠይቀው ምክትል ዳይሬኮተሯ ፈርመው የላኩት ደብዳቤ ፦

- " ወ/ሮ በላይነሽ ሽባባው ' በክልሉ በተፈጠረው ግጭት ምክንያት 4,000 ሴቶች ተደፍረዋል ' የሚል ያልተረጋገጠ ሀሳብ አንስተዋል " ይላል።

- ክልሉ በዚህ ወቅት በግጭት ላይ በመሆኑ በሴቶች ላይ የተለያዩ ጥቃቶች እንደሚፈጸሙ ቢገመትም ተቋሙ ግን ታች ድረስ ወርዶ መረጃ ለመሰብሰብ ባለው ግጭት ምክንያት ምቹ ሁኔታ ስለሌለና ኢንተርኔት በመዘጋቱ ምክንያት መረጃዎችን ሰብስቦ ማረጋገጥ እንዳልተቻለ ይገልጻል።

* የተባለው መረጃው በተቋሙ ውስጥ እንደሌለ፤ ምቹ ሁኔታን ሲገኝ ታች ወርዶ ያረጋገጥነውን መረጃ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ እንደሚያሳውቅ ያመለክታል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ያደረጉት ገለጻ ስህተት እንደሆነ የተነገረላቸው ወ/ሮ በላይነሽን በድጋሚ ማብራሪያ እንዲሰጡ ያደረገው ሙከራ ስልክ ለማንሳት ፈቃደኛ አልሆኑም።

#AATikvahFamily

@tikvahethiopia
#Amhara

➡️ “ በአጠቃላይ 7 ሰዎች ሞተዋል። በተለይ ሕፃናት ተርበዋል ” - ደባርቅ የሚገኙ የትግራይ ተፈናቃዮች 

➡️ “ በድርቁም ችግር አለ፤ ተፈናቃዮች ላይም ችግር አለ ” - የሰሜን ጎንደር ዞን

በ2013 ዓ/ም ከትግራይ ክልል ተፈናቅለው በአማራ ክልል ፤ በሰሜን ጎንደር ዞን ፤ ደባርቅ ወረዳ ውስጥ የሚገኙ ተፈናቃዮች እርዳታ እየተደረገላቸው ባለመሆኑ የምግብ እጥረት እንደተጋረጠባቸው፣ በዚህም የሞቱ ሰዎች እንዳሉ ገልጸዋል።

ተፈናቃዮቹ ሁኔታውን በተመለከተ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል “ ኬንዳውን (መጠለያውን) አፈረሱብን። በየመስሪያ ቤቱ ብንገባም ተቀባይነት አጣን ” ብለዋል።

“ የትግራይ ተፈናቃዮች በየመስሪያ ቤቱ፣ በየመስጂዱ (በተለይ ሕፃናት፣ ሕሙማን፣ እናት አባት የሞቱባቸው) ናቸው ” ያሉ ሲሆን “ ባይሆን ለእነርሱ እንኳን እርዷቸው ብለን እንኳ ብንለምን ‘ ምንም የለም፤ ለእናንተ አይሰጥም ’ አሉን ” ሲሉ አማረዋል።

“ ሕዝቡ ግን ረሃብ ሞተ። በተለይ ሕፃናት ፣ መድኃኒት ተጠቃሚዎች። ከ2016 ዓ/ም መስከረም ወር ወዲህ 4 ሰዎች ሞተዋል። ከዚያ በፊት ደግሞ 3 ሰዎቸ ሞተዋል። በአጠቃላይ 7 ሰዎች ሞተዋል ” ነው ያሉት።

መጠለያውን ያፈረሱት ግንባታ ሊገነቡበት እንደሆነ ፣ የተፈናቃዮቹ ብዛት 403 አባውራ፣ በአጠቃላይ ደግሞ 1,244 መሆናቸውን፣ የተፈናቀሉት በ2013 ዓ/ም እንደሆነ ፣ የተፈናቀሉት ከመቐለ ፣ ከዓዲግራት ፣ ሽረና ሌሎች የተለያዩ ቦታዎች እንደሆነም አስረድተዋል።

“ እኛ እዚህ ተቀባይነትን ካጣን ሌላ ቦታ ተቀባይነት ካገኘን ዜግነታችንንም ቢሆን ቀይረን ፈርመን አብረን እንሄዳለን ተረካቢ ድርጅት ካገኘን ” እስከማለት የደረሱት እኚህ ተፈናቃዮች ይህን የወሰኑት የሚረዳቸው ስላጡ መሆኑን ገልጸዋል።

የእለት ደራሽ ምግብ እርዳታ እንዲሰጣቸውም አጥብቀው ጠይቀዋል።

በተፈናቃዮች በኩል ለቀረበው ቅሬታ ምላሽ እንዲሰጡ የጠየቅናቸው አንድ የሰሜን ጎንደር ዞን ባለስልጣን፣ “ የክልሉ አደጋ መከላከል ኮሚሽን ‘ከእኔ ውጪ መረጃ እንዳይሰጥ’ ብሎ በክልሉ መንግስት አሳውጇል። እኔማ እንዴት ብዬ ልስጥህ። ‘መረጃ በአንድ ማዕከል ይሁን’ ብለው አቅጣጫ ስለሰጡ ” ብለዋል።

እኝሁ አካል “ በድርቁም ችግር አለ። ተፈናቃዮች ላይም ችግር አለ። የሰላም ተመላሽ ላይም ችግር አለ። ይህን ለማለት ግን እቸገራለሁ። መረጃ ሰጥተናል ለክልሉ መንግስት ” ከማለት ውጪ ተጨማሪ ማብራሪያ ለመስጠት ተቆጥበዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ፦
° ለተናቃዮቹ ለምን እርዳታ አልተደገላቸውም ?
° መጠለያውስ ለምን ፈረሰ ? በማለት የአማራ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ማስተቢበሪያ ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ የሆኑት ወ/ሮ ፍቅሬ ሙሉጌታን ጠይቋል።

ጉዳዩን #ከፍተኛ_የመንግስት_አካላት እንደያዙት እና እሳቸው ማብራሪያ መስጠት እንደማችሉ ከመግለጽ ውጪ ዝርዝር ማብራሪያ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆኑም።

#TikvahEthopiaFamilyAA

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
#Amhara

ኢሰመኮ፦

- ከየካቲት 15 እስከ 28 ቀን 2016 ዓ/ም በምዕራብ ጎጃም ዞን፣ ደጋ ዳሞት ወረዳ (ዝቋላ ወገም፣ ፈረስ ቤት01፣ ገሳግስና ጉድባ ሰቀላ ቀበሌዎች) እና ሰከላ (አጉት፣ ጉንድልና አምቢሲ ቀበሌዎች እና ግሼ ዓባይ ከተማ) በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎችና በታጣቂዎች መካከል የተካሄዱ የትጥቅ ግጭቶችን ተከትሎ በሲቪል ሰዎች ላይ ሞት፣ አካል ጉዳትና የንብረት ውድመት ደርሷል።

- የካቲት 20/2016 በሰሜን ጎጃም ዞን ሜጫ ወረዳ ብራቃት ቀበሌ በሚገኘው የጋፊት ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን የአብነት ተማሪዎች የዕለቱን ትምህርትና ጉባኤ ከምሽቱ 5፡00 ሰዓት አካባቢ አጠናቀው ወደ ማደሪያ ጎጇቸው ከገቡ በኋላ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አባላት ከሌሊቱ 6፡30 ሰዓት ገደማ ላይ ወደ ቦታው ደርሰው ተማሪዎችን “ #ውጡ ” እያሉ ተኩስ በመክፈት ቀድመው በወጡ #በ11_ተማሪዎች ላይ ግድያ እንደፈጸሙ፤ ሌሎች 8 ተማሪዎችንም ደግሞ በቁጥጥር ሥር አውለው ካሳደሩ በኋላ በማግስቱ ምንም ጥፋት የለባችሁም ብለው እንደለቀቋቸው ኢሰመኮ ለመረዳት ችሏል። በወቅቱ በአቅራቢያው የሚንቀሳቀስ የታጠቀ ኃይል እንዳልነበር ምስክሮች አስረድተዋል።

- መጋቢት 2 ቀን 2016 ዓ/ም በኦሮሞ ብሔረሰብ ልዩ ዞን የተነሱ ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች በሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደር #በኤፍራታና_ግድም እና #ቀወት ወረዳዎች በሚገኙ የተወሰኑ ቀበሌዎች ላይ በፈጸሙት ጥቃት በሲቪል ሰዎች ላይ ግድያ መፈጸሙን፣ የአካል ጉዳት መድረሱን፣ ንብረት መውደሙን፣ መኖሪያ ቤቶች መቃጠላቸውን እና የቀንድ ከብቶችና ባለ ሶስት እግር ተሽከርካሪዎች መዘረፋቸውን ኢሰመኮ ተረድቷል።

- መጋቢት 6 ቀን 2016 በአማራ ክልል፣ በባሕር ዳር ከተማ ዘንዘልማ አካባቢ አቶ ብርሃኑ ሽባባው አካል ፣ አቶ በላይ አካል እና አቶ ተሾመ ይበልጣል የተባሉ ነዋሪዎች አንዱ በሚሠራበት ሱቅ እና ሁለቱ በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ " ኑ ለጥያቄ ትፈለጋላችሁ " በሚል በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ መጋቢት 7 ቀን 2016 በባሕር ዳር ቀበሌ 14 በተለምዶ ጉዶ ባሕር አካባቢ #የፊጥኝ_እንደታሰሩ በጥይት ተገድለው ተገኝተዋል።

- በባሕር ዳር ዳግማዊ ምኒልክ ክ/ከተማ ጋጃ መስክ ተብሎ በሚጠራ ስፍራ መጋቢት 29 ቀን 2016 ዓ.ም. ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት አካባቢ ማንነታቸው ባልታወቁ አካላት በተፈጸመ ጥቃት ሶላት ስግደት አከናውነው ወደ ቤታቸው እየተመለሱ የነበሩ የእስልምና ተከታይ 5 ሰዎች (4ቱ የአንድ ቤተሰብ አባላት የሆኑ) ተገድለዋል።

- ሚያዝያ 7/2016 ከጧቱ 3፡00 ሰዓት ላይ በደቡብ ጎንደር ዞን እስቴ ወረዳ አጎና ቀበሌ ላይ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች ከእስቴ ወረዳ ወደ ላይ ጋይንት ወረዳ በመጓዝ ላይ እያሉ በአካባቢው ላይ በሚንቀሳቀሱ የታጠቁ ኃይሎች (#ፋኖ ) ድንገተኛ የደፈጣ ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ ታጣቂዎቹ አካባቢውን ጥለው እንደሸሹ #የመንግሥት_የጸጥታ_ኃይሎች ወደ ቦታው በመግባት 7 (1 ሴትና 6 ወንዶች) ሲቪል ሰዎች ላይ ከሕግ ውጪ ግድያ ፈጽመዋል። ከ15 በላይ የሚሆኑ የቆርቆሮ ክዳን ያላቸው መኖሪያ ቤቶች እና 3 የገለባ ቤቶችና ንብረት መቃጠላቸውን እንዲሁም ከ100 በላይ የሚሆኑ የቀበሌው ነዋሪዎች ወደ ሌላ አካባቢ የተፈናቀሉ መሆኑን የቀበሌው ነዋሪዎች እና ተጎጂዎች ገልጸዋል።

- ግንቦት 4/2016 ዓ/ም ከቀኑ ከ7፡00 ሰዓት አካባቢ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ቀወት ወረዳ ተሬ ቀበሌ ውስጥ በተፈጸመ የድሮን ጥቃት በጉሎ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ግቢ ውስጥ 2 ሲቪል ሰዎች ሲገደሉ አንድ ሴት መምህርትን ጨምሮ ሌሎች 9 ሲቪል ሰዎች የቆሰሉ መሆኑን ኢሰመኮ ተረድቷል።

#Amhara #EHRC

@tikvahethiopia
#Amhara

የኤፍራታ ግድም ወረዳ አስተዳዳሪ ተገደሉ።

በወረዳው የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች የወረዳውን አስተዳዳሪ አቶ አልብስ አደፍራሽን ትለንትና በምሽት በመግባት እንደገደሏቸው ተሰምቷል።

ወረዳው ባወጣው የሀዘን መግለጫው ፥ " አቶ አልብስ ለዓመታት በቀውስ ነጋዴዎች ለችግር ተጋልጦ የሴራ ፖለቲካ መሸቀጫ የተደረገውን የጀውሃና አካባቢው ማህበረሰብ ቀርቦ በማወያየት መተማመን ፈጥሮና አደራጅቶ ወደ ቀደመ አካባቢውና ኑሮው እንዲመለስ በማድረግ ላይ ነበሩ " ሲል ገልጿል።

አክሎ " የወደሙትን የጤናና ሌሎች ተቋማትንም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት በመስራት መልሶ እያቋቋመ የነበረ ደከመኝን የማያውቅ፣ ለእውነት የቆመ ንፁህ የሕዝብ ልጅና አገልጋይ፤ እውነተኛ የአማራ ጀግና ነበር " ብሏል።

አቶ አልብስ አደፍራሽ ትላንትና ምሽት ቤታቸው በገቡ ታጣቂዎች ተገድለዋል።

@tikvahethiopia
#Amhara

በአማራ ክልል ፤ በሰሜን ጎንደር ዞን በአድርቃይ ወረዳ በተፈጸመ ጥቃት 15 የሚሆኑ ሰዎች መገደላቸውን እና በርካታ ቤቶች መቃጠላቸውን ነዋሪዎች እና የአካባቢው አስተዳደር አሳውቀዋል።

ይህ አካባቢ የትግራይ እና አማራ ክልሎች አዋሳኝ ነው።

ነዋሪዎች ምን አሉ ?

- ባለፈው ማክሰኞ ግንቦት 27 ከንጋቱ በ11፡00 ሰዓት አሊጣራ ቀበሌ አንካቶ በተባለ ጎጥ የቡድን መሳሪያ #ከትግራይ_በኩል በመጡ የታጠቁ ኃይሎች ከባድ ጥቃት ተከፍቶ ነበር።

- ጥቃቱ ከንጋቱ 11፡00 ጀምሮ እስከ ጠዋት 2፡30 ገደማ ነበር የዘለቀው።

- አንድ የአካባቢው ነዋሪ ፥ " #በአንድ_ቤት 5 ነበርን፣ ከአምስታችን እኔ ነኝ በአጋጣሚ የተረፍኩት፤ ሌሎቹ ሞቱ። አሰልፈው ነው የተኮሱብን።...እኔንም ሞቷል ብለው ነው ትተውኝ የሄዱት። በፈጣሪ ፈቃድ ነው የተረፍኩት ፤ ጀርባዬን በጥይት ተመትቼ ሆስፒታል ነው ያለሁት " ብለዋል።

- ሌላ ነዋሪ ፤ " በጥቃቱ 15 ሠዎች መገደላቸውን በዐይኔ ተመልክቻለሁ። ሁለት የ16 እና የ19 ዓመት የእህት ልጆቼም ተገድለዋል። " ሲሉ ተናግረዋል።

- ሌላኛው ነዋሪ ፥ " በእሳት እና በጥይት 3 ታዳጊዎችን ጨምሮ የበርካታ ሰዎች ሕይወት አልፏል። ህጻናትን ጨምሮ 15 ሠዎች መገደላቸውን አይቻለሁ " ብለዋል።

- የአካባቢው #የሚሊሻ አባል ፤ " ከጥቃት ፈጻሚዎች ጋር የተኩስ ልውውጥ ነበር። አብሮኝ የነበረው ታናሽ ወንድሜ በጥቃቱ ተገድሏል። ቦምብ ጉዳት አድርሷል፤ ጥይቱ፤ መሳሪያውም ብዙ ስለሆነ፤ ድሽቃ፣ ስናይፐር፣ ብሬን አላቸው። በእርቀት እየተኮሱ ነው ጉዳት ያደረሱት " ብለዋል።

-  ታጣቂዎቹ አካባቢውን ለቀው ሲወጡ 3 ሰዎችን ወስደዋል። 500 ከብቶችን ዘርፈወል። ቤቶችም ተቃጥለዋል።

ወረዳው ምን አለ ?

ዋና አስታዳዳሪ አቶ ሚሊዮን ታደሰ ጥቃቱን የፈጸሙት በዋልድባ ገዳም በኩል አድርገው የገቡ የትግራይ ኃይሎች ናቸው ብለዋል።

ቀብራቸው መፈጸሙን #ማረጋገጥ የቻሉት የስምንት ሰዎች መሆናቸውን ተናግረዋል።

ከ8ቱ ሟቾች መካከል 6ቱ #ንጹሃን_ነዋሪዎች እንደሆኑ 2ቱ የአካባቢው ሚሊሻ አባላት እንደነበሩ ገልጸዋል።

ጥቃተ የፈጸሙት የትግራይ ኃይሎች ስለመሆናቸው በምን እንዳወቁ ተጠይቀው ፥ ነዋሪዎች በሚናገሩት ቋንቋ እንደለይዋቸውና በተለያዩ ጊዜያትም ትንኮሳዎችን ይፈጽሙ እንደነበር ገልጸዋል።

" የትግራይ ታጣቂዎች ናቸው። ከእነሱ ውጪ የሚመጣብን ሌላ እንደሌለ ነው የተረዳነው " ብለዋል።

" ቡድኑን የሚመራውን ግለሰብ ጭምር እናውቃለን ፤ የህወሓት ታጣቂዎች ናቸው " ሲሉ ተናግረዋል።

ቦታው ይገባኛል የሚነሳባቸውን አካባቢዎችን ለመያዝ " ስልታዊ " መሆኑን ተንተርሶ ጥቃቱ ሳይፈጸም አልቀረም ብለዋል።

" የማንነት ጉዳይ ሚነሳባቸውን አካባቢዎች በቁጥጥራቸው ስር ለማድረግ የግድ የእኛን አካባቢ ማጥቃት አለባቸው። በ2013ም የተመለከትነው ይህን ነው። ስለዚህ ይህን አካባቢ የመቁረጥ፤ ቆርጦ መሀል ላይ ያለን የመንግሥትን መዋቅር የማጥቃት ፍላጎት አለ " ሲሉ ተናግረዋል።

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ምን ምላሽ ሰጠ ?

የትግራይ ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ባልደረባ አቶ አማረ ኃይሌ ፤ የትግራይ ኃይሎች ጥቃት አልፈጸሙም ብለዋል።

" እስካሁን ድረስ ወደዚያ አካባቢ ያደረግነው ምንም እንቅስቃሴ የለም " ብለዋል።

" እኛ ያለንበት ቦታና አሁን እየተባለ ባለው ቦታ በጣም ሰፊ ርቀት ነው ያለው። በቀጥታ የሚዋሰን ቦታም አይደለም " በማለት ጥቃቱን እንዳላደረሱ ገልጸዋል።

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር " ያሉ ችግሮችን ግጭት አልባ በሆነ መንገድ ለመፍታት ነው የሚያስበው ወደ ግጭት የመግባት ሁኔታ የለንም " ብለዋል።

Credit - BBC AMHARIC

@tikvahethiopia