TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.3K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
ደብረ ማርቆስ‼️

በደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር #መብራት ለአንድ ወር ያክል እንደሚጠፋ በመወራቱ ወፍጮ ቤቶች በወረፋ መጨናነቃቸውን ተሰምቷል።

ስለሚወራው ወሬ አብመድ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሰሜን ምዕራብ ሪጂን የትራንስሚሽን ሰብስቴሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ውበት አቤን በስልክ አነጋግሯል፡፡

‹‹ሽብር ለመፍጠር የሚነዛ #አሉባልታ ነው፤ በባለፈው በመኪና ክሬን ዋና የኃይል መስመሩ ተነካክቶ ችግር ተፈጥሮ ኃይል ተቋርጦ ነበር፡፡ እሱንም አስተማማኝ በሆነ መልኩ ጠግነን ሥራ አስጀምረናል፡፡ አሁን ለመብራት መጥፋት የሚሆን ምክንያት የለም›› ብለዋል፡፡

የደብረ ማርቆስና አካባቢውን የኃይል አቅርቦት የበለጠ አስተማማኝ ለማድረግ ተጨማሪ ትራንስፎርመር ለማቅረብ እየተሠራ መሆኑን የገለጹት አቶ ውበት ኅብረተሰቡ #የሚወራውን ሙሉ በሙሉ ወደ ጎን በመተው መደበኛ ሕይወቱን እንዲመራ አሳስበዋል፡፡

‹‹ለአንድ ወር ቀርቶ ለአንድ ቀን የምናቋርጥበት ምክንያት የለም፡፡ የተለመዱ የደቂቃዎች መቆራረጦችም እንዳይኖሩ አቅማችንን አሟጠን እየሠራን ነው›› ብለዋል አቶ ውበት፡፡

በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የደብረ ማርቆስ አገልግሎት መስጫ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ ቸኮልም ‹‹ወሬው ሰንብቷል፤ ማን እንዳስወራው ግን አላወቅንም፡፡ ሕዝቡ መደናጥ እንደሌለበት በከተማ አስተዳደሩ በኩልም መረጃ ለማድረስ ሞክረናል፡፡ በዝናብና ዛፎች ንክኪ ምክንያት ድንገተኛ ችግር ካላጋጠመን በቀር የኃይል አቅርቦት ሥራችንን ያለመቆራረጥ እያደረስን ነው›› ብለዋል፡፡

በደብረ ማርቆስ ከተማ በጥቅምት ወር አጋማሽ ከአንድ ሳምንት በላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ተቋርጦ እንደነበር ይታወቃል።

ምንጭ፦ የአማራ ብዙሀን መገናኛ ድርጅት
@tsegabwolde @tikvahethiopia
ጅግጅጋ የሆነው ምንድነው ?

ከሰሞኑን በጅግጅጋ ከተማ እጅግ አሰቃቂ የተባለ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ተፈፅሟል።

የአስገድዶ መድፈር ወንጀሉ የተፈፀመባት የ9 ዓመት ህፃን ልጅ ስትሆን ይህ ድርጊት ከተፈፀመባት በኃላ የድርጊቱ ፈፃሚዎች የደፈሯትን ልጅ ገድለዋታል።

ከዚህ አሰቃቂ ድርጊት በኃላ ወንጀሉን የፈፀሙ 4 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ሊውሉ እንደቻሉ ተገልጿል።

ነገር ግን ከዚህ የወንጀል ድርጊት ጋር በተያያዘ ተጠርጣሪዎችን በመያዙ ሂደት ላይ ሰዎችን ለይቶ በአፈሳ የማሰር ድርጊት እንደነበር ቃላቸውን የሰጡ የጅግጅጋ ነዋሪዎች ገልጸዋል።

አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የጅግጅጋ ነዋሪ በሰጡት ቃል ፤ ከህፃኗ መደፈር ድርጊት ጋር በተያያዘ ሰኞ 4 ተጠርጣሪዎች ቢያዙም በከተማው ሰፊ አፈሳ ሲደረግ ነበር ብለዋል።

በተለይም ከደቡብ አካባቢ የመጡ ልጆች በድርጊቱ ላይ በመጠርጠራቸው ይህን መሰረት ያደረገ እስር ሲፈፀም እንደነበር ገልጸዋል። ድርጊቱ እስከ ትላንት ድረስ መቀጠሉን ጠቁመዋል።

አንድ ሌላ ነዋሪ ድርጊቱ እጅግ በጣም አሰቃቂና አስደንጋጭ እንደነበር ገልጸው ከተጠርጣሪዎች አያያዝ ጋር በተያያዘ በፀጥታ ኃይሎች የተፈፀመው ድርጊት ተገቢ አይደለም ብለዋል።

" ተጠርጣሪዎችን በልዩነት ማሰር እየተቻለ ሰዎች በአፈሳ ወደ ማቆያ ሲገቡ ነበር ይህ ተገቢ ያልሆነ አካሄድ ነው " ሲሉ ገልጸዋል።

ሌላ አንድ ነዋሪ ደግሞ ፤ " እሁድ እለት አንድ ልጅ ተደፈራ ከተገደለች በኃላ ድርጊቱን የፈፀሙ ግለሰቦች ተይዘው ለህግ ቀርበዋል " ብለዋል።

" ይሄ ጥሩ ነው " ያሉት እኚሁ ነዋሪ ነገር ግን ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት የለላቸውን ሰዎች ፓሊስ በጅምላ በማፈስ ማሰረሱን ፣እና መደብደቡን ጠቁመዋል።

በነበረው ሁኔታ የሰዎች ህይወት ማለፉን እንደሰሙ ገልጸዋል።

በተለይ ከደቡብ የመጡ ወጣቶችን መታወቅያ በማየት እስር ፣ ድብደባ ሲፈፀም ነበር ይህን የሚመለከተው አካል ይወቀው ሲሉ ገልጸዋል።

የሶማሌ ክልል መንግሥት ግን ከአሰቃቂው የወንጀል ድርጊት በኃላ ተፈፅሟል የተባለው ድርጊት #አሉባልታ እና #ሀሰተኛ ነው ብሏል።

የክልሉ ኮሚኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አብድቃድር ረሽድ ፤ " በሱማሌ ክልል የሌላ ክልል ተወላጆች እየታፈሡ እየታሰሩ ፣እየተገደሉ ነው በሚል በማህበራዊ ሚዲያ የሚሰራጨው አሉባልታ ወሬ ነው " ያሉ ሲሆን የሚንገረው ሁሉ ውሸት ነው ብለዋል።

" የሶማሌ ህዝብ ሰፊ ህዝብ ነው አቃፊ ነው ፣ ከየትኛውም ህዝብ ጋር የመኖር ባህል ያለው ማህበረሰብ ነው ፤ የሌላ ኢትዮጵያዊ ተወላጅ የማሳደድ፣ የመግደል ባህል ፈፅሞ የለውም የሚነገረው ሁሉ ውሸት ነው፤ የሶማሌ ህዝብን ስም ለማንቋሸሽ የሚሰራ ፕሮፖጋንዳ ነው " ሲሉ ተናግረዋል።

" የህግ አካላት ቦታው ላይ ሳይደርሱ ሁከት ለመፍጠር ሙከራ ተደርጎ ነበር " ያሉት ኃላፊው የህግ አካላት የዜጎችን ደህንነት ለማስጠበቅ የወሰዱት እርምጃዎች ነበሩ ብለዋል።

" እነዛም መቆያ አካባቢዎች ለደህንነታቸው ስጋት የቆዩ አካላት በማጣራት ወደመደበኛ ስራቸው እንዲመለሱ ትላንት በፀጥታ አካላት መመሪያ ተሰጥቷል። " ሲሉ ተናግረዋል።

" በሶማሌ ክልል ምንም ችግር የለም ሰላም ነው ፤ የሶማሌ ህዝብ አቃፊ ነው " ያሉት ኃላፊው የፖለቲካ አጀንዳ በማድረግ ተቃውሞ በመፍጠር ብጥብጥ ለመፍጠር ፣ በክስተቶች ላይ ክስተት በማጋነን ፣ እከሌ ተገደለ፣ እከሌ ዘሩ እንዲህ ነው በማለት ለፖለቲካ የሚጠቀሙ ኃይሎች አሉ " ብለዋል።

" የሶማሌ ክልል ሰላም ነው ፤ ሁሉም ወደ መደበኛው ስራ ተመልሷል " ሲሉ አክለዋል።

#ቲክቫህኢትዮጵያ

@tikvahethiopia
#NBE

ብሔራዊ ባንክ " ሪፖርተር ጋዜጣ " ላይ ወጥቷል ባለው አሳሳች ዘገባና አሉባልታ ምክንያት በዋጋ ላይ የሚፈጠር ማንኛውም ሰው ሠራሽ #ጭማሪ ተቀባይነት የለውም፤ ጥብቅ ክትትልም ይደረጋል ብሏል።

ብሔራዊ ባንክ ምን አለ ?

-  በጋዜጣዊ በህዳር 23/2016 እትም ብሔራዊ ባንክ ባለፈው ሳምንት የ2016 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለፓርላማ የፕላን፤ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ባቀረበበት ወቅት ከአንድ የፓርላማ አባል ቀረበ ከተባለ አስተያየት ላይ ተነሥቶ ብሔራዊ ባንክ በውጭ ምንዛሪ ተመን ላይ በቅርብ ጊዜና በከፍተኛ ደረጃ ለውጥ ለማድረግ ማቀዱን በማስመልከት የወጣው ዘገባ ፈጽሞ ሐሰተኛና አሳሳች፣ ከጋዜጠኝነት ሥነ ምግባር ያፈነገጠ ድርጊት ነው ብሏል።

- " ለፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ ጉዳዮን በተመለከተ የቀረበ ዕቅድ የለም " ሲል ገልጿል።

- እስከ 4 ስዓት በፈጀው ውይይት ወቅት በብሔራዊ ባንክ የተነገረ ነገር እንደሌለ ህብራተሰቡ መረዳት አለበት ብሏል።

- በዚህ አሳሳች ዘገባና አሉባልታ ምክንያት በዋጋ ላይ የሚፈጠር ማንኛውም ሰው ሠራሽ ጭማሪ ተቀባይነት የለውም ጥብቅ ክትትልም ይደረጋል ብሏል።

በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ የወጣው ዘገባ ምን ይላል ?

- ብሔራዊ ባንክ በሕጋዊውና በጥቁር ገበያው መካከል ያለውን ሰፊ የውጭ ምንዛሪ ተመን ልዩነት #በ95_በመቶ ለማጥበብ ዕቅድ መያዙ መታወቁ ፤ ይህ ዕቅድ ግን መቼና እንዴት እንደሚፈጸም የታወቀ ነገር እንደሌለ ያስረዳል።

- ይህ ባንኩ ዕቅድ የተሰማውም ኅዳር 19 ቀን 2016 ዓ/ም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የበጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የብሔራዊ ባንክን የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድና የመጀመርያ ሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸም በገመገመበት ወቅት ነው ብሏል።

- ብሔራዊ ባንክ ይህንን ዕቅዱን በቋሚ ኮሚቴው የግምገማ መድረክ ላይ #በይፋ_ባያቀርብም፣ ለቋሚ ኮሚቴው የቀረበን #ሰነድ የተመለከቱ አንድ የም/ ቤት አባል፤ ዕቅዱን ከሪፖርቱ ላይ እንደተመለከቱ ጠቅሰው ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

የም/ቤቱ አባሉ ምን አሉ ?

" ብሔራዊ ባንክ በሕጋዊው የውጭ ምንዛሪ ተመንና በጥቁር ገበያው መካከል ያለውን ልዩነት በ95 በመቶ የማቀራረብ ዕቅድ ይዟል።

ነገር ግን በአሁኑ ወቅት በሕጋዊው የምንዛሪ ተመንና በጥቁር ገበያው መካከል ያለው ልዩነት እጥፍ ነው።

ስለዚህ ልዩነቱን በ95% ለማጥበብ የተያዘው ዕቅድ በተጨባጭ የሚቻል ነው ወይ ? ወይስ ዲቫሉዌሽን ለማድረግ (የብርን የመግዛት አቅም ለማዳከም) አስባችኋል? " ሲሉ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

- የብሔራዊ ባንክ ዋና ገዥ አቶ ማሞ ምሕረቱ፤ "እንደየ ሁኔታው እየተመዘኑ የሚወሰዱ ዕርምጃዎች ይኖራሉ እንጂ በዚህ ወቅት ይህ ዕርምጃ ይወሰዳል ብሎ ብሔራዊ ባንክ ሊናገር አይችልም "  የሚል ምላሽ መስጠታቸው በጋዜጣው ላይ ሰፍሯል።

- አቶ ማሞ " የውጭ ምንዛሪ ጉዳይን በተመለከተ ሁሉን ነገር እዚህ መናገር አልችልም። ብሔራዊ ባንክን በሚመለከቱ አንዳንድ ጉዳዮች ላይ የምናደርገው ውይይት ተገቢ ላልሆነ ስፔኩሌሽን (ግምት) የሚያጋልጥ መሆን የለበትም። ገና ጥናት ያልተደረገበት ጉዳይ ላይ ብንወያይም ትርጉም የለውም። ዋናው ቁልፍ ነገር ዓላማችን ላይ መወያየት ሊሆን ይገባል። የባንኩ ዋና ዓላማ የተረጋጋ የዋጋ ሁኔታና የተረጋጋ የውጭ ምንዛሪ ሥርዓት እንዲኖር ማስቻል ነው " ማለታቸውንም ጋዜጣው አስፍሯል።

ብሔራዊ ባንክ ይህን ዘገባ ነው #አሳሳችና #አሉባልታ ነው ያለው።

$ በአሁኑ ወቅት የዶላር ሕጋዊው የውጭ ምንዛሪ ተመን 55.5 ብር የደረሰ ሲሆን፣ በጥቁር ገበያው ግን አንድ ዶላር እስከ 110 ብር እየተመነዘረ ይገኛል።

@tikvahethiopia