TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#መቐለ

በጦርነት ምክንያት ተቋርጦ የነበረው  የመቐለ ከተማ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ግንባታ ዳግም ጀመረ።

የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቱ የከተማዋ የንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅምን በ30 ከመቶ ያሳድገዋል።

ፕሮጀክቱ ከ150 ሺህ በላይ ህዝብ ተጠቃሚ ያደርጋል።

ከጦርነቱ በፊት በ830 ሚሊዮን ብር ግንባታው ጀምሮ 12 ከመቶ ሲደርስ የተቋረጠው ገረብ ሰገን የተባለው ፕሮክጀክት ፤ በክልሉ የውሃ ሃብት ቢሮና በአፍሪካ ልማት ባንክ ቅንጅት ዳግም ግንባታው ጥር 28/2016 ዓ.ም በይፋ ተጀምሯል።     

ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘው የ10 ሚሊዮን ዶላር በድር የሚገነባው ፕሮጀክቱ በ420 የስራ ቀናት እንደሚጠናቀቅ  የግንባታው አስተባባሪ ኢንጅነር ደሰታ ግደይ ገልፀዋል።

እንደ መቐለ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ምልከታ የመቐለ ከተማ የንፁህ የመጠጥ ውሃ እጥረት በእጅግ አሳሳቢ ሁኔታ ይገኛል።

በከተማዋ ለወራት የንፁህ ውሃ መጠጥ አገልግሎት የማያገኙ አከባቢዎች ከጉድጓድ ለሚቀዳ ለአንድ የ20 ሊትር ጀሪካን ውሃ በብር 20 ለመኪና ቦቴ ደግሞ አስከ 1 ሺህ ብር በመከፈል ለመግዛት ይገደዳሉ።

የከተማዋ የውሃ አጥረት ያሳሰባቸውና በስራቸው ከፍተኛ አሉታዊ ጫና የፈጠረባቸው በሆቴልና መስተንግዶ የስራ ዘርፍ የተሰማሩ ባለሃብቶች በተለይ ከሰላም ስምምነቱ በኃላ  የውሃ ቁፋሮ ማሸነሪ በመከራየት የከርሰ ምድር ውሃ ማውጣት እንደ አማራጭ በመውሰድ እየተጠቀሙበት ይገኛሉ።   

ከጊዜ ወደ ጊዜ የነዋሪዋችዋ ቁጥር እየጨመረ የሚገኘው መቐለ ከቻይና መንግስት በተገኘ በረጅም ጊዜ በድር በፌደራል መንግስትና በትግራይ ክልላዊ መንግስት ትብብር ተጀምሮ የነበረው ግዙፉ የገረብ ግባ የንፁህ ውሃ መጠጥ ፕሮጀክት በጦርነቱ ምክንያት ተቋርጦ በስራው የነበሩ በርካታ ማሽነሪዎች ለስርቆትና ብልሸት ተዳርገዋል።

ቻይናዊው የፕሮጀክቱ ተቋራጭ ከሰላም ስምምነቱ በኃላ በፕሮጀክቱ የደረሰ ውድመትና ያለበት ሁኔታ ለመታዘብ ከትግራይ ክልል ከፍተኛ ሹማምንት በመሆን በቦታው ድረሰ በመምጣት ከወራት በፊት ጉብኝት ያደረገ ቢሆንም እስከ አሁን ደረስ ወደ ስራ ተመልሶ አለመግባቱ የመቐለ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ዘግቧል።
                
@tikvahethiopia            
#መቐለ

ባለፈው የካቲት 14 ቀን 2016 ዓ/ም ሌሊት በትግራይ መቐለ ከተማ ዓይደር ከፍለ ከተማ በተለምዶ " ሓሚዳይ የኢንዱስትሪ መንደር " ተብሎ በሚጠራ ቦታ በቡድን የተደራጁ ዘራፊዎች የተጠና ስርቆት ሊፈፅሙ ሲሉ ተደርሶባቸው አምልጠዋል።

በወቅቱ ይህ መረጃ የደረሰው የመቐለ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ቦታው ድረስ በመሄድ ጉዳዩን ተከታትሏል።

ድርጊቱ እንዴት ተፈፀመ ?

የካቲት 14/2016 ዓ.ም ከሌሊቱ 8:00 ሰዓት የተደራጁ ዘራፊዎች በሁለት አቅጣጫ #ጠባቂ_በመመደብ የተቀሩት በከፍታ ቦታ የተሰቀለው ባለ 400 ኪሎ ቮልት ትልቅ ትራንስፎርመር መሳልል በመጠቀም ወደ መሬት ለማውደቅ ይጥራሉ።

በዚህ መሃል በአከባቢው የነበረ ጥብቃ ማንነታቸው ሲጠይቃቸው ዘራፊዎቹ የመንግስት ስራ በመስራት ላይ መሆናቸውንና ከማደናቀፍ ተቆጥቦ ስራውን እንዲሰራ ያስጠነቅቁታል።

ብዛት ያላቸው መሆናቸው የተገነዘበው የጥበቃ ባለሞያ ትእዛዛቸው ተቀብሎ የሄደ በመምሰል ራቅ ወዳለ ቦታ በመሄድ በአካባቢው ከሚያውቃቸው ጥበቃዎች ወደ አንዱ ስልክ ይደውላል።

በዚህ መሃል ዘራፊዎቹ ትራንስፎርመሩ ከነበረበት ከፍታ ቦታ ወደ መሬት በመጣል የሚፈልጉት የውስጥ አካል ለመዝረፍ በጥድፍያ ይሰራሉ።

በዚህ ሰዓት በፀጥታ የተዋጠው አከባቢ በጥይት #ቶክስ እና በጥሩምባ ድምፅ ይረበሻል።

ዘራፊዎቹ እጅግ ከመደንገጣቸው የተነሳ የጀመሩት ሳይጨርሱ በሩጫ በትንትናቸው ይወጣል።

በአከባቢው በነበሩ የጥበቃ ሰራተኞች ጥረት ስርቆቱ ከመፈፀም ቢድንም ትራንስፎርመሩ ከከፍታ ወደ መሬት ተከስክሶ ከጥቅም ውጪ ሆኗል።

የስርቆት ሙከራው ወደ ፓሊስና የኤሌክትሪክ ሃይል አገልግሎተ ሪፓርት ተደርገዋል።

ፖሊስ ተጠርጣሪዎችን ለመያዝ እያፈላለገ ነው።

የኤሌክትሪክ ሃይል የቴክኒክ ቡድን ከስርቆት አምልጦ መሬት ላይ ወድቆ የተከሰከሰው ትራንስፎርመር ተጥግኖ መልሶ አገልግሎት መስጠት ይችል እንደሆነ እየሰራበት ነው። 


የስርቆት ሙከራው የተካሄደበት ቦታ ሓሚዳይ የተባለ የኢንዱስትሪ መንደር ፡ ቀን ሰውና ተሽከርካሪ የሚበዛበት ፤ ጨለማ ሲሆን ደግሞ በሰው እጦት ፀጥታ የሚሰፍንበት ነው።

የስርቆት ሙከራው ሲፈፀም በመቐለ በንፋስ ምክንያት በበርካታ አከባቢዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎት መቋረጥ ስለነበረ ለስርቆቱ አመቺ ሁኔታ ሳይፈጥርላቸው አልቀረም ተብሏል።

ቃላቸውን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ የሰጡ ገለሰብ ፤ የስርቆት ሙከራው ተራ ስርቆት ሳይሆን በኤሌክትሪክ ሃይል ሰራተኞች የታገዘ የባለሙያ ስርቆት ነው የሚል ጥርጣሬ እንዳላቸው ገልጸዋል።

የትራንስፎርመር ስርቆት ሙከራው ምን ያለመ ነበር ?

የመቐለ የቲክቫህ ቤተሰብ አባል ስርቆቱ ለምን አላማ እንደተፈፀመ ለአንድ የኤሌክትሪክ ሃይል የቴክኒክ ባለሞያ ጥያቄ አቅርቦ ነበር።

ባለሞያው ፦

- ይህ መሰል ሰርቆት በተለይ በጦርነቱ ጊዜ እጅግ የተባባሰ እንደነበረ ፤ ሰርቆቱ በትራንስፎርመሩ ውስጥ የሚገኘው ፈሳሽ ዘይትና ኬብል ለመውሰድ ያለመ መሆኑን፤

- ከትራንስፎርመሩ የሚቀዳ ዘይት ከነዳጅ ጋር ተቀላቅሎ ጥቅም ላይ እንደሚውል ፣ ኬብሉ ደግሞ ቀልጦ ከወርቅ ተደባልቆ እንደሚሰራና በተጨማሪ ለብየዳ ስራ እንደሚውል ፤

- አሁን ስርቆቱ በተፈፀመበት ቦታ በጦርነቱ ጊዜ 800 ኪሎ ቮልት ያለው በአከባቢው የሚገኙ ኢንዱስትሪዎችና ፋብሪካዎች የሚጠቀሙበት ትልቅ ትራስፎርመር በመፍታት በወስጡ ያለው ዘይት በመዘረፉ ምክንያት ተቃጥሎ ከጥቅም ውጭ በመሆኑ በመንግስት ላይ ከፍተኛ ኪሳራ መደረሱን ገልጸዋል።

#TikvahFamilyMekelle

@tikvahethiopia
#መቐለ
 
" ባለ ውለታ ይከበራል እንጂ ፤  በረሃብና በሽታ አይቀጣም " - የትግራይ ጡረተኞች

የትግራይ ጡረተኞች ዛሬ የካቲት 21/2016 ዓ.ም በመቐለ ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ አካሄዱ።

ሰልፎኞቹ በመቐለ ከተማ ባካሂዱት ሰልፍ :- 
- የትግራይ ጡረተኞች ድምፅ ይሰማ !!
- የ18 ወራት ውዙፍ አበል በአስቸኳይ ይከፈለን !
- የፕሪቶሪያ ውል በአስቸኳይ ይተግበር !
- የትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር የጡረተኞች መብት ያክብር ያስከብር !!
- መንግስት የጡረተኞች አዋጅና ደንብ ያክብር ! 
- ባለ ውለታ ይከበራል እንጂ ፤ በረሃብና በሽታ አይቀጣም !!
- የዓለም አቀፍ ተቋማት የት ናችሁ ? !

የሚሉ መፈክሮች እያሰሙ በከተማዋ በዋና ዋና መንገዶች ተዘዋውረዋል። 

የጡረተኞቹን ሰላማዊ ጥያቄ ያዳመጠውና የተቀበለው በኢፌዲሪ የመንግስት ሰራተኞች ማህበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ የሰሜን ሪጅን ቅርንጫፍ ፤ የታህሳስ 2015 ዓ.ም የውል አበል በተያዘው ሳምንት ለመከፈል መዘጋጀቱን ፤ ቀሪ የ18 ወራት የጡረታ አበል እንዲከፈል ከክልሉ ጊዚያዊ አስተዳደርና ከፌደራል መንግስት በመነጋገር ላይ መሆኑ አስታውቋል።

መረጃው በመቐለው የቲክቫህ ቤተሰብ አባል የተዘጋጀ ነው።

@tikvahethiopia            
#መቐለ

በመቐለ ቀዳማይ ወያነ ክፍለ ከተማ ፥ ዘስላሴ ቀበሌ ቀጠና 14 በሚገኘ " እየሩሳሌም " በተባለ ሆቴል እፍሬም ፍትዊ ገ/ክርስቶስ የተባሉ ግለሰብ በመኝታ ክፍል ውስጥ ሞተው መገኘታቸውን የክ/ከተማው ፖሊስ ገልጿል።

ግለሰቡ መጋቢት 20/2016 ዓ.ም ከቀኑ 6:30 ነው በያዙት የመኝታ ክፍል ውስጥ ሞተው የተገኙት።

የአሟሟታቸው ሁኔታ ለማወቅ የሚያስችል የአስክሬን ምርምራ በዓይደር ሆስፒታል በመካሄድ ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል።

የሟች ቤተሰቦች እስከ መጋቢት 22 /2016 ዓ.ም ባለው ጊዜ ወደ ፖሊስ ሪፓርት ካላደረጉ ህጉ በሚፈቅደው መሰረት ከአስከሬን ምርመራ በኃላ የቀብር ስነ-ሰርአት ለመፈፀም እንደሚገደድ ፖሊስ አመልክቷል። (104.4 የመቐለ ኤፍኤም ሬድዮ)

#TikvahFamilyMekelle
        
@tikvahethiopia            
#መቐለ

ዛሬ በመቐለ #ሰላማዊ_ሰልፍ የወጡ የመቐለ ዩኒቨርሰቲ ተማሪዎች በፖሊስ ድብደባና እስራት እንደተፈፀመባቸው ዶቼ ቨለ ሬድዮ ተማሪዎቹን ዋቢ በማድረግ ዘግቧል።

ተማሪዎቹ ተራዝሟል ያሉትን የመመረቂያ ግዜን በመቃወም ሰልፍ የወጡ ሲሆን የትግራይ ክልል የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ ድብደባ እና እንግልት እንደፈፀሙባቸው ተናግረዋል።

10 ተማሪዎች መታሰራቸውም ተገልጿል።

ተማሪዎቹ ዛሬ ረፋድ 4 ሰዓት ከመቐለ ዩኒቨርሲቲ አሪድ ግቢ ተነስተው ያሏቸውን ቅሬታዎች ለማሰማት ወደ መቐለ ከተማ ጎዳናዎች ሰላማዊ ሰልፍ ባደረጉበት ወቅት ነው ድብደባና እስራቱ የገጠማቸው።

ተማሪዎቹ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ለምን #ተገደዱ ?

በተለያዩ ችግሮች #ለዓመታት ትምህርታቸው ሲስተጓገል ቆይቶ ዘንድሮ 2016 ለመመረቅ እየተጠባበቁ የነበረ ቢሆንም ፤ ዩኒቨርሲቲው ሌላ ተጨማሪ ዓመት መማር እንደሚጠበቅባቸው ከገለፀላቸው በኃላ ነው ሰልፍ የወጡት።

ከሰላማዊ ሰልፉ በፊት ግን ለዩኒቨርሲቲው በተደጋጋሚ ቅሬታቸውን ማቅረባቸውን እና ከዩኒቨርሲቲው ምላሽ አለማግኘታቸውን ለሬድዮ ጣቢያው በሰጡት ቃል ገልጸዋል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
#መቐለ

" ዲግሪ ለመያዝ 8 ዓመታትን መማር #ፍትሃዊ አይደለም " - ተማሪዎች

ዛሬ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ አደባባይ የወጡ የመቐለ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በፖሊስ በኃይል እንዲበተኑ ተደርገዋል።

ተማሪዎቹ ምንድነው ጥያቄያቸው ?

" አንድ ዲግሪ ለመያዝ 8 (#ስምንት) ዓመታትን መማር  #ፍትሃዊ አይደለም " ያሉት ተማሪዎቹ " ከሌሎች ዩኒቨርስቲዎች የምንለይበት ምክንያት የለም ፤ የመውጫ ፈተና መፈተን አለብን " ብለዋል።

" ተመርቀን ወጥተን ስራ መስራት ፤ ህይወትን ማሸነፍ ባለብን በዚህ እድሜያችን የመጀመሪያ ዲግሪ ለማግኘት 8 ዓመታት መጠበቅ የለብንም ፣ የወጣትነት እድሜያችን ያሳስበናል ፤ ብንጮህ ብንጮህ ሰሚ አላገኘንም " ሲሉ ገልጸዋል።

" በዚህ ዓመት መመረቅ ሲገባን ሌላ ተጨማሪ ጊዜ ትማራላችሁ እያሉን ነው ይሄ በፍፁም የማንቀበለው ነው " ብለዋል።

ዛሬ ተማሪዎቹ ከመቐለ ዩኒቨርስቲ ዋናው ግቢ በመነሳት የተለያዩ መፈክሮች በመያዝ ወደ ከተማ ለማምራት ሲሞክሩ በፓሊስ እንግልትና ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል።

የትራፊክ ፖሊስ አባላት ሰልፉን ለማደናቀፍ መንገድ ሲዘጉ ፤ ታጣቂዎች ሰልፈኛ ተማሪዎች ሲደበድቡ ታይተዋል።

ጥያቄ  ካነሱ ሰላማዊ ሰልፈኞች መካከል ሶስት ሴት ተማሪዎች በፓሊስ #ሲደበደቡ መመልከቱን ህሉፍ በርሀ የተባለ የአይን እማኝ ገልጿል።

ከዛሬው ሰልፍ ጋር በተያያዘም አንድ የፖሊስ አባል አንዲት #ሴትን እያንገላታ #ገፍትሮ መሬት ላይ ሲጥላት የሚያሳይ ቪድዮ ብዙዎችን አስቆጥቷል።

የመቐለ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ሰላማዊ ስልፍ በማስመልከት የዩቨርስቲው አስተዳደር እና የትምህርት ሚንስቴር እንዲሁም የከተማው ፖሊስ እስከ አሁን ያሉት ነገር የለም።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ተቋማቱ የሚሉት ካለ ተከታትሎ ያቀርባል።

መረጃው በመቐለ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል የተዘጋጀ ነው።

@tikvahethiopia
#መቐለ

በትግራይ ክልል፣ መቐለ ዓይደር ኮምፕሬሄንሲቭ ሪፈራል ሆስፒታል የላፕራቶሪ ማሽኖች ላይ ወድመት ደርሷል።

ከሰሞኑን አንድ በጭንቅላቱ ላይ ካርቶን ያደረገ ማንነቱ የማይታይ ግለሰብ በሆስፒታሉ የህክምና ቁሶች ላይ ጉዳት ሲያደርስ የሚያሳይ የCCTV ቅጂ ተሰራጭቷል።

ግለሰቡ ለምን እንዲህ ያለውን ተግባር እንደፈጸመ የሚታወቅ ነገር የለም።

ሆስፒታሉ ለቢቢሲ ትግርኛ ክፍል በሰጠው ቃል ፥ በትክክል ድርጊቱ የተፈፀመው ዓይደር ውስጥ እንደሆነ አረጋግጧል።

ድርጊቱ የተፈፀመው በራሱ ሰራተኛ እንደሆነ አመልክቷል።

ድርጊቱ የተፈፀመው ቅዳሜ መጋቢት 21 ለሊት ሲሆን በሚሊዮኖች የሚገመት ዋጋ ያላቸው በርካታ የህክምና መሳርያዎች ላይ ጉዳት ደርሷል ብሏል።

የጉበት፣
የኩላሊት እጥበት፣
የሰውነት ሆርሞን መለኪያ
የካንሰር አመላካቾች እንዲሁም በተለያዩ እንደ የልብ ህመም ያሉ ድንገተኛ ሁኔታዎች መመርመሪያዎች፣ የሆርሞኖች፣ የሰውነት ስብን መለኪያ መሳሪያዎች ከተጎዱት የሆስፒታሉ መገልገያዎች መካከል ናቸው።

ጉዳት ከደረሰባቸው የህክምና መሳሪያዎች አንዱ ለተለያዩ ምርመራዎች የሚውለው " ኮባስ 6000 " የሚል መጠሪያ ያለው ሲሆን፣ በትግራይ ያለው ብቸኛው እና ትልቁ የሆስፒታሉ መሳሪያ ነው።

አሁን ከአገልግሎት ውጪ ሆኗል።

መሳሪያው ቀደም ብሎ በ20 ሚሊዮን ብር የተገዛ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ዋጋው 30 ሚሊዮን ብር እንደደረሰ ሆስፒታሉ ገልጿል።

የመቐለ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባልም ጉዳዩ ዓይደር ኮምፕሬሄንሲቭ ሪፈራል ሆስፒታል ድረስ በመጓዝ ጉዳዩ ሲከታተለው ነበር።

ከሆስፒታሉና ስለ ጉዳዩ እውቀትና ቅርበት ካላቸው ወገኖች የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ማንነቱ ያልታወቀው ግለሰብ በስለት በመጠቀም ሲቆርጠው የሚታየው (ከላይ ቪድዮ አለ) ከ30 ሚሊዮን ብር ዋጋ እንዳለው የተነገረለት የላቦራቶሪ ማሽን የኤሌክትሪክ ማስተላለፍያ ክፍል ነው።

በመቐለ ከተማ የዓይደር ክፍለ ከተማ ፓሊስ በዓይደር ኮምፕሬሄንሲቭ ሪፈረሰል ሆስፒታል የላብራቶሪ ማሽኖች ወድመት በተያያዘ ቪድዮው ላይ ያለው ግለሰብ ጨምሩ 4 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር አውሏል። 

@tikvahethiopia
አምባሳደር ማይክ ሐመር ከነማን ጋር ተገናኙ ?

በአፍሪካ ቀንድ #የአሜሪካ_ልዩ_መልዕክተኛ የሆኑት ማይክ ሐመር ከሰመኑን በኢትዮጵያ ቆይታ አድርገዋል።

ኢትዮጵያ የመጡት ፦
° የፕሪቶሪያን ስምምነት አፈጻጸም ለመገምገም፤
° በአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች ያሉ ግጭቶች በድርድር እልባት እንዲያገኙ ለማድረግ፤
° የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መመርመር አስፈላጊነት ላይ ለመወያየት ነው።

በዚህም ወቅት ፦

- ከፌዴራይል ባለስልጣናት ጋር መክረዋል።

- ከአሜሪካው አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ጋር ወደ #መቐለ አምርተው ከትግራይ ክልል አመራሮች ጋር መክረዋል።

- ከአፍሪካ ህብረት ተወካዮች ጋር ተወያይተዋል።

- ከኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ጋር መክረዋል።

- ከኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ሊቀመንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ እና ከኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ጋር  ተወያይተዋል።

አምባሳደር ማይክ ሐመር የፕሪቶሪያው ግጭትን በዘላቂነት የማስቆም ስምምነት እንዲፈረም ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል የሚባልላቸው የአሜሪካ ባለስልጣን ናቸው።

@tikvahethiopia
#መቐለ

ከሳምንት በፊት " በአፈልጉን ማስታወቅያ "  ስትፈለግ የሰነበተች ተማሪ በውሃ ጉድጓድ ውስጥ ሞታ ተገኘች።

ተማሪ ቤቴልሄም ገብረሚካኤል ነጋሽ ግንቦት 11 ቀን 2016 ዓ/ም ከጠዋቱ 2:00 ሰዓት ላይ ነው በመቐለ ከተማ ፤ ዓዲ ሓቂ ክፍለ ከተማ ዓዲ ሓውሲ ቀበሌ ከሚገኝ ቤትዋ እንደወጣች የቀረችው።

ዛሬ ግንቦት 19 ቀን 2016 ዓ/ም ግን አስክሬኗ ደብሪ ቀበሌ ጨለዓንቋ ተብሎ በሚታወቅ ኩሬ ተጥሎ መገኘቱ ተገልጿል።

የ17 ዓመትዋ ተማሪ ቤቴልሄም በመቐለ የቀላሚኖ ልዩ ትምህርት ቤት የ10ኛ ክፍል ተማሪ የነበረች ስትሆን ከአንድ ሳምንት የአፋልጉን ጥሪ በኋላ በውሃ ጉድጓድ አስክሬኗ ተጥሎ መገኘቱ ብዙዎችን አስደንግጧል፤ አሳስዝኗል።

የተማሪዋ አስክሬን በፓሊስ ትእዛዝ ወደ ዓይደር ሪፈራል ኮምፕሬሄንሲቭ ሆስፒታል ተወስዶ ከተመረመረ በኋላ አመሻሽ በመቐለ አቡነ አረጋዊ ቤተክርስትያን በክብር እንዲያርፍ ተደርጓል።

በቀብር ስነሰርዓቱ ላይ ቤተሰቦች፣ የቀላሚኖ ትምህርት ቤት ኮሙዩኒቲ ፣ ወዳጆች እና አብሮ አደጎችን ጨምሮ በርካታ ህዝብ በመገኘት የተሰማው ጥልቅ ሃዘን በእንባ በመታጀብ ገልጿል።

በቀብር ስርዓቱ ላይ የተገኘው ህዝብ ፍትህ ጠይቋል።

የአሟሟትዋ ጉዳይ እጅግ በጣም ያሳዘናቸው የተለያዩ የህብረተሰብ አካላት ወንጀሉ ተጣርቶ ወንጀለኞች ወደ ህግ እንደዲቀርቡ ጠይቀዋል።

ፖሊስ በጉዳዩ ላይ የሚሰጠው ዝርዝር ማብራሪያ ካለ ተከታትሎ እንደሚልክ የመቐለው የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ገልጿል።

#TikvahEthiopiaFamilyMekelle

@tikvahethiopia
#Tigray
 
ወደ 26 የትግራይ ወረዳዎች ለእርዳታ በመጓጓዝ ላይ ያለ #የተበላሸ የማሽላ እህል ለህዝብ እንዳይከፋፈል ታገደ።

እግዳውን ያስተላለፈው የትግራይ ክልል ምግብና የመድሃኒት ቁጥጥርና ክትትል መ/ቤት ነው።

ከማሽላ እህሉ በተወሰደ የናሙና ምርመራ ውጤት መሰረት ፦
- መጥፎ ሽታ ያለው መሆኑ፤
- በነቀዝ የተበላና ወደ ዱቄትነት የመቀየር ደረጃ የደረሰ በመሆኑ ፤
- በአጠቃላይ የበሰበሰና የተበላሸ በመሆኑ፡
ለምግብነት ቢውል የሚያስከትለው የጤና ጠንቅ እጅግ ከባድ ስለሆነ እህሉ በያለበት መጋዘን እንዲታገድ ተወስኗል።

በመጓጓዝ ላይ ያለውም እንዲቋረጥ ሲል መ/ቤቱ ሰነ 6/2016 ዓ.ም ለወረዳዎቹ በፃፈው የእግድ ደብዳቤ አስታውቀዋል።

እግድ የተጣለበት የማሽላ እህል ' አስቸኳይ ምላሽ ለትግራይ ግብረ ሃይል ' በሚል በክልሉ የተቋቋመው በድርቅ እና በሰብአዊ ቀውስ ለተጎዱ ወገኖች ለማገዝ ከአገር ውስጥና ከውጭ ለጋሾች ባሰባሰው ብር የተገዛ ነው።

ግብረ ሃይሉ ሰነ 5 ቀን 2016 ዓ/ም ለሚድያዎች በሰጠው መግለጫ  እህሉ በግዢ ጊዜ በናሙና ከቀረበው ውጭ የሆነና የተበላሸ ለጤና ጠንቅ መሆኑ ስለተደረሰበት እንዳይከፋፈል ሲል ገልጿል።

መግለጫው ተከትሎ በማሽላ እህሉ ምርመራ ያካሄደው የምግብና የመድሃኒት ቁጥጥርና ክትትል መ/ቤት ፤ እህሉ የተበላሸና ለምግብነት ውሎ የሚያስከትለው አደጋ ከግምት ውስጥ በማስገባት  በ90 ሚሊዮን ብር በጨረታ የተገዛው የማሽላ እህል #እንዲታገድ ወስኗል።

እግዱን ተከትሎ ' አስቸኳይ ምላሽ ለትግራይ ግብረ ሃይል ' ሰነ 6/2016 ዓ.ም ለሁለተኛ ጊዜ በሰጠው መግለጫ " እህሉ ከጥቅም ውጭ እንዲሆን ፤ ለመግዣ የተመደበው 90 ሚሊዮን ብር በ26 ወረዳዎች ለሚገኙ ተረጂዎች በጥሬ ገንዘብ እንዲከፋፈል ፤ የጨረታ ሂደቱ ተሰርዞ አህል አቅራቢው ለጨረታ ማስከበርያ ያስያዘው 9 ሚሊዮን ብር እንዲወረስ ወስኛለሁ " ብሏል። 

#TikvahEthiopiaFamilyMekelle
#መቐለ

@tikvahethiopia