TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#አማራክልል

በደብረ ብርሃን በፋኖ እና በመከላከያ መካከል ተደረገ በተባለ የተኩስ ልውውጥ ንጹሐን ሰዎች መገደላቸውን ነዋሪዎችና የከተማው ከንቲባ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገለጹ።

በአማራ ክልል ደብረ ብርሃን ከተማ ሰሞኑን በፋኖ ከታጣቂዎችና በመከላከያ ሠራዊት ተደረገ በተባለ የተኩስ ልውውጥ፣ “በርካታ ንጹሐን ተገድለዋል። ባለሥልጣናትም ታግተው ተወስደዋል” ሲሉ አንድ የከተማው ነዋሪ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ተናግረዋል።

ሌላኛው ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ ነዋሪ፣ “እኔ ባለኝ መረጃ 5 ንጹሐን ተገድለዋል” ብለው፣ ከንጹሐን ሰዎች በተጨማሪ የብልጽግና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የአቶ ሰለሞን ጌታቸው ሹፌርም እንደተገደሉ፣ የፋኖ ታጣቂዎች ኃላፊውን ጨምሮ በርካታ ሠራተኞችን አግተው እንደወሰዱ አስረድተዋል።

የደብረ ብርሃን ከተማ ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት ምን ያህል ሰዎች እንደተገደሉ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ለቀረባለቸው ጥያቄ በሰጡት ማብራሪያ፣ የተወሰኑ ሰዎች ላይ ጉዳት እንደደረሰ፣ የሟቾችን ብዛት እያጣሩ መሆኑን፣ እስካሁን (ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ) ድረስ ከአራት ሰዎች በላይ መገደላቸውን ተናግረዋል።

አክለውም፣ የብልጽግና ጽሕፈት ኃላፊው ሹፌር ተገድሏል መባሉ እውነት መሆኑን፣ ይሁን እንጂ ኃላፊውና ሌሎች ሠራተኞች ታግተው #እንዳልተወሰዱ አስረድተው፣ የጸጥታውን ሁኔታ በተመለከተም፣ “ወደ መደበኛ ሥራው ተመልሷል። መደበኛ እንቅስቃሴ ላይ ነው” ብለዋል።

ከደብርሃን ከተማ በተጨማሪ በሰሜን ወሎ የተለያዩ አካባቢዎች፣ በጎንደርና በጎጃም መስመሮች በተለያዩ አካባቢዎች በየወቅቱ የተኩስ ልውውጥ እንደሚደረግ ነዋሪዎች ይናገራሉ።

ሰሞንኛውን የደብረ ብርሃን የጸጥታ መደፍረስ ተከትሎ ወደ ሸዋ ሮቢት፣ ደሴ፣ ወልዲያና ሌሎች አካባቢዎች መጓዝ አለመቻላቸውን፣ አሁንም ለገና በዓል ወደ ቤተሰብ ለመሄድ የመንገዱ ደህንነት ሥጋት እንደደቀነባቸው ተጓዦች ሲያማርሩ ተስተውለዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ከላም በረት መናኸሪያ ስምሪት ባደረገው ቅኝት ከአዲስ አበባ ወደ ደሴ መስመር ስምሪት እንደሌለ፣ ለዚሁ መስመር የጉዞ ትኬት የሚጠይቁ ሰዎችም የለም እየተባሉ መሆኑን ተመልክቷል።

በሌላ በኩል በሰሜን ወሎ ዞን ራያ ቆቦ ከተማ ወጣ ብሎ በስተምዕራብ በኩል ጠበለት ተራራ ተብሎ በሚጠራው ቦታ ሰሞኑን ከፍተኛ የተኩስ ልውውጥ እንደነበር፣ ከቆቦ ወደ ተኩለሽ ታዳጊ ከተማ በጸጥታው ችግር ምክንያት የትራንስፖርት አገልግሎት ከቆመ ዓመታት ማስቆጠሩን ነዋሪዎቹን አማሯል።

ከዚህም ባሻገር በክልሉ በተለይ ድርቅ በተከሰተባቸው ዋግኽምራ አስተዳደር ዞን፣ በሰሜን ጎንደር አካባቢዎች እርዳታ ለማድረስ የጸጥታው ችግር ፈተና እንደሆነ የአካባቢዎቹ ባለሥልጣናት በተደጋጋሚ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ መግለጻቸው፣ ነዋሪዎች በበኩላቸው የጸጥታው ችግር የኑሮ ውድነቱን እንዳባባሰው ተናግረዋል።

በፋኖ ታጣቂዎችና መከላከያ ሠራዊት መካከልበአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች በየወቅቱ የተኩስ ልውውጥ ሲደረግ ይስተዋላል።

ዘገባውን የላከው የአ/አ ቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ነው።

@tikvahethiopia