TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
TIKVAH-ETHIOPIA
መምህራን ምን አሉ ? • " የመምህራን ደመወዝ ይቆረጣል የሚሰጠው ምክንያት ደግሞ አሳማኝ አይደለም " • " የፌዴራል መንግሥት የዓመቱን በጀት ወደ ክልሎች ቢልክም፣ ክልሎች ለወረዳዎች አይልኩም " • " አንዳንዴ ደመወዝ ለበርካታ ወራት ሳይከፈላቸው ይጠብቃሉ፤ ግማሽ ደመወዝ ብቻ የሚከፈልበት ጊዜም አለ " የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር በጅግጅጋ ከተማ ባካሄደው 36ኛው ጉባዔ ላይ፣ በክልሎች የበርካታ…
#የኢትዮጵያ_መምህራን_ማህበር #ቲክቫህኢትዮጵያ

የመማሪያ መፅሀፍት ጉዳይ

" ቅሬታችንን መንግሥት ይወቅልን " ያሉ #ተማሪዎች ፣ የመማሪያ መፅሀፍት ሶፍት ኮፒ እንኳን ማግኘት ቢቻል ማንበቢያ ስልክ ያስፈልጋል ፣ ስማርት ስልክ ደግሞ የቤተሰቦቻችን ገቢ  ዝቅተኛ በመሆኑ ሊገዛልን አይችልም ሲሉ ቅሬታቸውን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ተናግረዋል።

አክለውም፣ በዚህ ሁኔታ እንዴት መማርና ውጤታማ መሆን እንችላለን ? ነው ወይስ ትምህርት መማር ያለባቸው የባለሃብት ልጆች ብቻ ናቸው ? ሲሉ ጠይቀዋል።

36ኛውን የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር ምክር ቤት ስብሰባ ምክንያት በማድረግ ሰሞኑን በጅግጅጋ በነበረ ውይይት የተማሪዎችን የመጽሐፍ እና የሶፍት ኮፒ አለምግኘት ጨምሮ ሌሎች መምህራን የሚያነሷቸውን ቅሬታዎች በተመለከ ምን የመፍትሄ ሀሳብ እንደተቀመጠ ቲክቫህ ኢትዮጵያ ለኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር ጥያቄ አቅርቧል።

የማኅበሩ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ማብራሪያ፣ " አንድ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት (ሳውላ ጎፋ አካባቢ) ፕሪንተርም፣ ፎቶ ኮፒም የለውም " ብለዋል።

" አንዳንድ ትምህርት ቤቶች የማባዣ ቁሳቁስ እንኳን የሌላቸው አሉና ሶፍት ኮፒ ብቻ ልኮ ተማሪዎች መፅሐፍ አግኝተዋል ማለት አይቻልም " ያሉት የማኅበሩ ፕሬዝዳንት፣ " ሶፍት ኮፒ ደግሞ በሞባይል ነው የሚታየው፣ ሁሉም ተማሪ ደግሞ ለዛ የሚመጥን ስማርት ስልክ ላይኖረው ይችላል፣ አስቸኳይ መፍትሄ መስጠት ያስፈልጋል " ነው ያሉት።

" ተማሪዎች ሀርድ በእጃቸው ይዘው የሚያነቡት ሀርድ ኮፒ ያስፈልጋቸዋል " ያሉት ዮሐንስ (ዶ/ር)፣ ይህንን በተመለከተም በጅግጅጋ በነበረው የማኅበሩ ምክር ቤት ክልሎች የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መፅሐፍ እጥረት እንዳለ፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መፅሐፍ እንዳልደረሰ ተነግሯል ብለዋል።

የተነሱ ቅሬታዎችን በተመለከተ የትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) " ወደ 40 ኮንቴነር ጂቡቲ ደርሷል፣ እንደውም ወደ መሀል አገርም እየተጓጓዘ ነው፣ በቅርቡ ወደ ትምህርት ቤቶች ይደርሳል " ማለታቸውን ይሐንስ (ዶ/ር) ገልጸዋል።

የመምህራን ዝውውር ጉዳይ

ከዝውውር ጋር በተያያዘ መምህራን በተደጋጋሚ ቅሬታ ሲያነሱ የሚደመጥ ሲሆን፣ ችግሩን ለመቅረፍ ምን ውይይት እንደተደረገ ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ጥያቄ የቀረበላቸው የማኅበሩ ፕሬዚዳንት፣  መምህራን የሚዘዋውሩበት የዝውውር ስርዓት እንዳለ ገልጸው ተከታዩን አክለዋል።

" ዝውውር ለመምህራን እንደ #ትልቅ_የመብት_ጉዳይ የሚታይ ነው። " የተለያዩ የአፈፃፀም ጉድለቶች እንዳሉ ምክር ቤቱ በጅግጅጋ በነበረው ስብሰባ ገምግሟል። በየደረጃው ተስተካክሎ በመመሪያው መሠረት እንዲፈጸም ሰፊ ውይይት አድርገንበታል። "

ተፈናቃዮችን ያስጠለሉ ትምህርት ቤቶች ጉዳይ

" የተፈናቀሉ ዜጎች መጠለያ የሆኑ ትምህርት ቤቶች እንዳሉ አይተናል። በዛ አካባቢ በተለይ ትምህርት ለመስጠት አስቸጋሪ ይሆናል " ሲሉ ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) አስረድተዋል።

ኢሰመኮ ጥቅምት 19 ቀን 2016 ዓ.ም ይፋ ባድረገው ሪፓርት በመንግሥት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቃዎች መካከል የተኩስ ልውውጥ በሚያገረሽበት አማራ ክልል ውስጥ ትምህርት ቤቶች የተፈናቃይ መጠለያ ካምፖች እንደሆኑ መረዳቱን ማስገንዘቡ ይታወሳል።

የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር በበኩሉ የተፈናቃይ መጠለያ በሆኑ ትምህርት ቤቶች ውስጥ መምህራን ማስተማር እንዳልቻሉ ፣ የትምህርት ተቋማትም ውድመት እንደሚደርስባቸው ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገልጸዋል።

የመምህራን ደመወዝ አለመከፈልና መቆረጥ ጉዳይ

መምህራን የሰሩበት ደመወዛቸው #ስለማይከፈላቸው እና የሚከፈላቸውም ስለሚቆረጥባቸው በተለይም ደቡብ ክልል ላይ የሥራ ማቆም አድማ እስከማድረግ የደረሱበትን ሁኔታ በተመለከተ ምን እንደታሰበም ቲክቫህ ኢትዮጵያ ለመምህራን ማኅበሩ ፕሬዝዳንት ጥያቄ አቅርቧል።

ፕሬዝዳንቱ ለቲክቫህ በሰጡት ማብራሪያ ፤ " ቀደም ብሎ እዚያ አካባቢ ባጋጠመው ሁኔታ እኛም ለክልሉ መንግሥት ደብዳቤ ፅፈን ነበር፣ በዚያ መነሻ በወቅቱ ተከፍሎ ነበር። አሁን ኋላ ላይ ደግሞ ተመልሶ እንዳገረሸ ሰምተናል" ብለዋል።

" ምክንያቶቹ የተለያዩ ይሆናሉ። መምህራን የሰሩበትን በጊዜው ማግኘት አለባቸው " ያሉ ሲሆን " ደመወዙ የመምህራኑ ብቻ ሳይሆን የቤተሰቦቻቸውም፣ የልጆቻቸውም ጭምር ስለሆነ በየደረጃው ያለው መዋቅር ይህን ተከትሎ መፈጸም እንዳለበት ሁሌም እናሳስባለን " ሲሉ ገልጸዋል።

የደመወዝ አለመከፈልን በተመለከተ ለማኅበሩ ምን ያህል መምህራን ቅሬታ እንዳቀረቡ፣ ለስንቶቹ መፍትሄ እንደተሰጠ ማብራሪያ እንዲሰጡ ሲጠየቁም፣ በአብዛኛው ቅሬታ ያለው በአዲሱ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ በጋምቤላ ክልል በተወሰነ መልኩ እንዲሁም በአፋርና በሌሎች አካባቢዎች እንድሆነ፣ ቅሬታው ከተለያዩ ወረዳዎች ስለሚመጣ ቁጥሩን ለመግለጽ እንደሚያስቸግር አስረድተዋል።

የማኅበሩ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዮሐንስ በንቲ ፤ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በገለጹት መሠረት ፣ የ36ኛው የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር ምክር ቤት ምክንያት በማድረግ ሰሞኑን በጅግጅጋ በነበረው ፕሮግራም ውይይት ተደርጎባቸው የመፍትሄ ሀሳብ የተቀመጠላቸው ዋና ዋና አጀንዳዎች፡-
- የመምህራን ዝውውር
- የመምህራን ጥቅማጥቅም
- የመምህራን የትምህርት ዕድል
- የመኖሪያ ቤት አቅርቦት
- መልካም አስተዳደር
- የትምህርት ጥራት
- የተማሪዎችን የውጤት ቀውስ
-  የጸጥታ ችግር በትምህርት ላይ ያስከተለው ያለውን አሉታዊ ተጽዕኖ በተመለከተ ነው ብለዋል።

መረጃው በአዲስ አበባ የቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ተጠናቅሮ የቀረበ ነው።

@tikvahethiopia