TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
ከ60 በላይ የጤና ባለሙያዎች ፤ " ጤና ሚኒስቴር በሕግ የተወሰነልንን ልዩ አበል አልከፈለንም " አሉ።

የጤና ባለሙያዎቹ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ እንደገለፁት፤ የኮቪድ - 19 ወረርሽኝ መጋቢት 8 ቀን 2012 ዓ / ም መከሰቱን ተከትሎ የጤና ማኒስቴር ባወጣው ጥሪ መሠረት የኢፌደሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት ግንቦት 18 ቀን 2012 ዓ / ም ባወጣው መመሪያ የሕክምና አገልግሎት ለሚሰጡ ለመላው ሀኪሞች በቀን 1,050 ብር፣ ለየመጀመሪያ ድግሪ ባለሙያዎች 900 ብር ልዩ አበል እንዲከፈላቸው ተወስኖ ነበር።

በዚህ መሠረት ጤና ሚኒስቴር በኮቪድ - 19 ወቅት የአገልግሎት ሥራ ለሰሩት የተወሰኑ ወራት አበል እንደከፈላቸው ፣ ይሁን እንጂ ከዚያ በኃላ ክፍያውን እንዳቆመ ፣ ይህን ተከትሎም ቀሪው ልዩ አበል እንዲከፈላቸው በቃልና በደብዳቤ ቢጠይቁም ምላሽ እንዳላገኙ ፣ በመጨረሻም ክስ እንደመሰረቱ፣ በክሱ  መሠረትም ገንዘቡ እንዲከፈላቸው ቢወሰንም ጤና ሚኒስቴር ግን ከውሳኔው በኋላም ለመክፈል ፈቃደኛ እንዳሆነ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ አስረድተዋል።

በአጠቃላይ ቅሬታ አቅራቢዎቹ  በቁጥር 71 ሲሆኑ አንድ ሥማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ ባለጉዳይ እና የጤና ባለሙያዎቹ ተወካይ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል ፦ " ጤና ሚኒስቴር ከተሰጠው ኃላፊነት አንፃር የጤና ሥርዓቱን ማዘመን፣ የጤና ባለሙያውን መብቶች፣ ጥቅሞች ማክበር፣ ለጤና ባለሙያዎች ምቹ ከባቢና የሥራ ዋስትና መፍጠር ነበር። ነገር ግን  መንግሥት ነኝ በማለት በማን አለብኝነት  በጤና ባለሙያዎች ላይ ከማሾፉም በላይ ጤና ባለሙያዎች ከአቅም በላይ ሲሆንባቸው መብታቸውን በፍትህ አካል ጠይቀው ተወስኖላቸው 'እንደውሳኔው ክፈል' ተብሎ ሲታዘዝ  'ያለውሳኔ ነው' በማለት ነገሮችን ማጣመም ተገቢና ከአንድ ሥሙ ትልቅ ከሆነ ተቋም የማይጠበቅ ነው " ሲሉ ሚኒስቴር መ/ቤቱ ላይ ወቀሳ አቅርበዋል።

ጤና ባለሙያዎቹ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ የላኩት ማስረጃ ጤና ሚኒስቴር ፦
▪️ከ1ኛ - 14ኛ ተራ ቁጥር ላሉት የጤና ባለሙያዎች ከኅዳር 1 ቀን  2013 ዓ.ም እስከ ኅዳር 21 ቀን 2014 ዓ.ም ለእያንዳንዳቸው 400 ሺሕ 050 ብር፣

▪️15ኛ ተራ ቁጥር ላይ ላሉ የጤና ባለሙያ ከሚያዚያ 1 ቀን 2013 ዓ.ም እስከ ኅዳር 21 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ 242 ሺሕ 550 ብር፣

▪️ከ16ኛ - 66ኛ ተራ ቁጥር ላሉ የጤና ባለሙያዎች ደግሞ ከመስከረም 1 ቀን 2013 ዓ.ም ኅዳር 21 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ ለእያንዳንዳቸው 396, 900 ብር በአጠቃላይ ከ1ኛ እስክ 66ኛ የጤና ባለሙያዎች የተጠቀሰው የኮቪድ - 19 ልዩ  አበል እንዲከፈላቸው አቤቱታ ማቅረባቸውን ያትታል።

ይህ የገንዘብ መጠን የጤና ባለሙያዎቹ ክስ ሲመሰርቱ ያካተቱት ሲሆን፣ በውሳኔ ግልባጩ ጤና ሚኒስቴር ለከሳሾች የልዩ አበሉን ከኀዳር 1 ቀን 2013 እስከ ሰኔ 30 ቀን 2014 ዓ.ም እንዲከፈል ተብሎ ቢወሰንም የተጠቀሰ የልዩ አበል መጠን ግን የለም።

ቲክቫህ - ኢትዮጵያ የተመለከተው #የውሳኔ_ግልባጭ ፣ ጤና ሚኒስቴር (መልስ ሰጭ ተቋም) ለይግባኝ ባዮች ያቀረቧቸው ሁሉንም የመቃወሚያ ሀሳቦች ውድቅ አድርጎ ከኅዳር 1 ቀን 2013 ዓ.ም እስከ ሰኔ 30 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ ባሉት ወራት ውስጥ (የሚከፈልባቸው ወራት ከፋፍሎ አስቀምጦ) ፣ ጤና ሚኒስቴር ለ66ቱ የጤና ባለሙያዎች የጠየቁትን የኮቪድ - 19 ልዩ አበል እንዲከፍል ውሳኔ ማሳለፉን ያስረዳል።

የውሳኔ ግልባጩ " 15ኛ ይግባኝ ባይ አቶ ክንዳለም መኳንንት በኮቪድ - 19 ሥራ ላይ ያገለገሉበት ክፍያ አቤቱታቸውን ካቀረቡ በኋላ የተከፈላቸው መሆኑን የይግባኝ ባዮች ተወካይ በችሎት በማስረዳታቸው 15ኛ ይግባኝ ባይ ከክርክሩ ውጭ ሆኗል " ይላል።

ቲክቫህ የጤና ባለሙያዎቹ በሕግ የተወሰነላቸውን ልዩ አበል ያልከፈለበትን ምክንያት እንዲያስረዳ ጤና ሚኒስቴርን ጠይቋል።

በተቋሙ ኃላፊነት ተሰጥቷቸው የሚያገለግሉት አቶ ዮርዳኖስ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት የፅሑፍ ምላሽ ፣ " ክልሎች ናቸው ጤና ባለሙያዎችን የሚቀጥሩት ስለሆነም የቀጠራቸው ክልል ጤና ቢሮ ማናገሩ ጥሩ ነው " ብለዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ስራ የሰሩበት አበል ሊከፍላቸው የሚገባው " የቀጠራቸው ክልል ነው " ስለተባለ የቀጠራቸው ተቋም ማን እንደሆነ ቅሬታ አቅራቢዎቹን ጠይቋል።

ይሁን እንጂ አንድ ቅሬታ አቅራቢ ለቲክቫህ በሰጡት ምላሽ ፣ "ጤና ባለሙያዎች የከሰስነው የቀጠረንን ተቋም ነው። ክልሎች ቀጥረውን እንዴት ጤና ሚኒስቴርን እንከሳለን ? ይህን እኮ እነሱም ያውቃሉ ውልም አለን። አሁን ከእነሱ ተቋም የለቀቅን ብዙዎች ነን እንጂ ከለቀቅን በኋላ ያለውን ደግሞ አልከሰስንም " ብለዋል።

እኚሁ ታማኝ ምንጭ በተጨማሪ ልዩ አበሉ ይከፈለን የሚሉች የጤና ባለሙያዎች የጤና ሚኒስቴር ሠራተኞች እንደነበሩ የሚያረጋግጥ ማስረጃ ልከዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ይበልጥ ይህንን ጉዳይ ለማጣራት የተመለከተው የውሳኔ ግልባጭ ፤ " መልስ ሰጭ መ/ቤት ይግባኝ ባዮች የልዩ አበል ክፍያ መጠየቅ ያለባቸው ተመድበው እየሰሩ ያሉበትን ተቋም ነው እንጂ ጤና ሚኒስቴርን አይደለም በማለት ያቀረበው መከራከሪያ ተቀባይነት የለውም " ሲል ውድቅ እንዳደረገው በግልጽ ያሳያል።

በመሆኑም አቶ ዮርዳኖስ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ለምን " ክልሎች ናቸው ጤና ባለሙያዎችን የሚቀጥሩት ስለሆነም የቀጠራቸው ክልል ጤና ቢሮ ማናገሩ ጥሩ ነው " የሚል ምላሽ እንደሰጡ በድጋሚ ለመጠየቅ በፅሑፍና መልዕክትና በስልክ ጥሪ ቢሞክርም ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆኑም።

በመጨረሻም ለጉዳዩ ምን አይነት ምላሽ እንዳላቸው ለመጠየቅ ለጤና  ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) ስልክ ቢደወልም ባለማንሳታቸው ሀሳባቸውን ማካተት አልተቻለም።

የክሱን ሂደት በተመለከተም ቲክቫህ ኢትዮጵያ ከሁነኛ አካላት ባደረገው ማጣራት የጤና ባለሙያዎቹ ልዩ አበሉ እንዲከፈላቸው መወሰኑን፣ አፈጻጸሙ ግን ገና እንዳልተቋጨ ለማወቅ ችሏል።

ይህ መረጃ በቲክቫህ ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባል ኢዮብ ትኩዬ ተዘጋጅቶ የቀረበ ነው።

@tikvahethiopia