TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#ዓለምአቀፍ

የጣሊያኗ " ላምፔዱሳ " ደሴት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አወጀች።

አዋጁን ያወጀችው ባለፉት ሁለት ቀናት ከአፍሪካ የተነሱ ወደ 8,000 የሚጠጉ ስደተኞች ወደ ደሴቷ መድረሳቸውን ተከትሎ ነው።

ስድተኞች ከተለያዩ አፍሪካ ሀገራት ወደ ጣልያን እየገቡ የሚገኙት በጀልባ ለህይወታቸው እጅግ አስጊ በሆነ መንገድ ተጉዘው ነው ተብሏል።

አንድ ከጊኒ ተነስቶ ጣልያን የገባ ስደተኛ ፤ በሕይወት ተርፎ ጣልያን በመግባቱ ዕድለኛ እንደሆነ ተናግሯል።

ሀገሪቱ አሁን እየገቡ ያሉትን ስደተኞች ወደ ሌሎች የመቀበያ ቦታዎች ለማዘዋወር እየሰራች ነው ተብሏል።

የጣልያን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የትራንስፖርት ሚኒስትር ማትዮ ሳልቪኒ ፤  በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ስደተኞች ጣልያን መድረሳቸውን " የጦርነት አነይት ድርጊትን " ይወክላል ብለዋል።

ሚኒስትሩ " ጣሊያንን ለማተራመስ ሆን ተብሎ የተነደፈ ስልት መሆኑን እርግጠኛ ነኝ " ያሉ ሲሆን ከዚህ ሴራ ጀርባ ማን እንዳለ ለመግለፅ አልወደዱም።

" ከዚህ በስተጀርባ አንድ እቅድ እንዳለ እርግጠኛ ነኝ " ያሉት ሚኒስትሩ " ከ100 በላይ ጀልባዎች በጥቂት ሰአታት ውስጥ መድረሳቸው ድንገተኛ ሳይሆን የተደራጀ የጦርነት አይነት ድርጊት ነው። " ብለዋል።

" ይህ የሚያመጣው ተፅእኖ በላምፔዱሳ ላይ  ብቻ የሚያበቃ አይደለም ፤ ወደ ሮም፣ ሚላን፣ ቱሪን፣ ኔፕልስ፣ ፓሌርሞ ስለሚሄዱ አሳዛኝ መዘዞችን ያስከትላል። " ሲሉ ተናግረዋል።

ጣልያን ከፍተኛ የስደተኞችን ቁጥር የምታስተናግድ አውሮፓዊት ሀገር ስትሆን በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየታየው ያለው ነገር ውጥረት መፍጠሩ ተገልጿል።

በላምፔዱሳ ያለው ከመደበኛ በላይ ሁኔታ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ አስገድዷል።

ባለፉት 2 ቀናት ብቻ 8,000 ከአፍሪካ የተነሱ ስደተኞችን የቀበለችው የጣልያኗ ደሴት ላምፔዱሳ አጠቃላይ የነዋሪዎቿ ብዛት 6000 ብቻ እንደሆነ መረጃዎች ያሳያሉ።

በሌላ በኩል ፤ የጀርመን የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር በጣሊያን በኩል ወደ #አውሮፓ የገቡ አዲስ ስደተኞችን ለጊዜው መቀበል እንዳቆመ አስታውቋል።

ጀርመን እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰችው ጣልያን ባአውሮፓ ህብረት በኩል በስደተኞች ላይ የተደረሰውን ስምምነት ለማክበር ፈቃደኛ ባለመሆኗ ነው ተብሏል።

የጀርመን መገናኛ ብዙሀን እንደዘገቡት " ከፍተኛ የስደተኞች ጫና አለ " በሚል ምክንያት ጀርመን ከጣሊያን የሚገቡ አዲስ ስደተኞችን ላልተወሰነ ጊዜ መቀበል አቋርጣለች።

ፈረንሳይ በበኩሏ ወደ ግዛቷ ለመሻገር የሚሞክሩ ስደተኞች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመምጣቱ ከጣሊያን ጋር በሚያዋስናት ድንበር ላይ የሚገኙ የፖሊስ እና የጦር ሃይሎች ጥበቃን በከፍተኛ ሁኔታ እንደምታጠናክር ይፋ አድርጋለች።

ቪድዮ ፦ ከማህበራዊ ሚዲያዎች የተገኘ

@tikvahethiopia
#ዓለምአቀፍ #ፖላንድ

በፖላንድ ፤ እ.አ.አ. ከ2011 ጀምሮ ለቪዛ ያመለከቱ ሰዎች ዝርዝር ላይ #ኦዲት ሊደረግ ነው ተባለ።

በፖላንድ ለአፍሪካውያን በክፍያ ቪዛ እየተሰጠ ነው በሚል መንግሥት ላይ ጥያቄ ማስነሳቱን ቢቢሲ በድረገፁ አስነብቧል።

የፖላንድ የላይኛው ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ቶማዝ ግሮዲዚ በአገሪቱ ገንዘብ እየተቀበሉ ቪዛ የመስጠት አካሄድ ተባብሷል ብለዋል።

መንግሥት ስለ ጉዳዩ ምን መረጃ እንዳለው ይፋ እንዲያደርግም ጠይቀዋል። ነገሩ የአገሪቱን ስም እያጠለሸ ነው ብለዋል።

መንግሥት የተወሰነ መረጃ ይፋ ያደረገ ሲሆን ፤ እንደ መገናኛ ብዙኃን ዘገባ ግን ስደተኞች እስከ 5,000 ዶላር እየከፈሉ የሥራ ቪዛ የማግኘት ሂደቱን ያፋጥናሉ ተብሏል።

እስካሁን ሰባት ሰዎች ላይ ክስ ቢመሠረትም ከመካከላቸው የመንግሥት ባለሥልጣን እንደሌለ ታውቋል።

የአገሪቱ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፒዮር ዋውዚክ ፤ ባለፈው ሳምንት ክሶችን ተከትሎ ከሥራ ተነስተዋል። የፖላንድ ፀረ ሙስና ኮሚሽን መሥሪያ ቤቱ ላይ ምርመራ ካደረገ በኋላ ነው የተባረሩት።

የሕግ ክፍሉ ዳይሬክተርም ተባረዋል።

እ.አ.አ. ከ2011 ጀምሮ ለቪዛ ያመለከቱ ሰዎች ዝርዝር ላይ ኦዲት እንደሚደረግ ተገልጿል።

ተቃዋሚ የምክር ቤት አባል ፤ እስከ 250,000 ቪዛዎች ሕግ ሳይከተሉ ለእስያ እና አፍሪካ አመልካቾች ተሰጥተዋል ሲሉ ገልጸዋል።

መንግሥት ግን ቁጥሩ በጥቂት መቶዎች ብቻ የሚቆጠር ነው ሲል አስተባብሏል።

የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ዶናልድ ተስክ ፤ " ከአፍሪካ ፖላንድ መምጣት የፈለገ ሁላ ከኤምባሲያችን ቪዛ ገዝቶ አገራችን በቀላሉ ይገባል " ብለዋል።

የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ግን ይህ ንግግር ቀውስ እንደሚያስከትል ገልጸው ችግሩ የተባለውን ያህል እንዳልሆነ ተናግረዋል።

" አገራችን ኃላፊነት የሚሰማት ዴሞክራሲያዊ አገር ሆና ሳለ የነጻውን ዓለም ደኅንነት አደጋ ውስጥ የምትከት ሆና እንድትታይ የሚያደርግ አካሄድ ስለሆነ በጥልቀት ሊብራራ ይገባል። ይህ የ21ኛው ክፍለ ዘመን ትልቁ ቅሌት ነው። ሙስና በመንግሥታችን ተንሰራፍቷል " ሲሉ የላይኛው ምክር ቤት አባል አሳስበዋል።

የፍትሕ ሚኒስተሩ ዚግኒው ዚዎብሮ ፤ ይህ አባባል የተጋነነ ነው ሲሉ ለብሔራዊ ቴሌቭዥን ጣቢያ ተናግረዋል።

ይህ ጉዳይ ከስደተኞች ጉዳይ ጋር በተያያ በቀጣዩ የፓርላማ ምርጫ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር መገለፁን ቢቢሲ ዘግቧል።

@tikvahethiopia

#ዓለምአቀፍ

ሃማስ እስራኤል ላይ ድንገተኛ የተባለ ጥቃት መክፈቱ ተሰማ።

የፍልስጤሙ ሃማስ በዓመታት ውስጥ ከፍተኛው ነው የተባለ ድንገተኛ ጥቃት መክፈቱን ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን እየዘገቡ ይገኛሉ።

ሃማስ ከጋዛ ሰርጥ ወደ እስራኤል 5000 ሮኬቶችን ያስወነጨፈ ሲሆን የሰው ህይወት መጥፋቱም ተነግሯል።

እየሩሳሌምን ጨምሮ በደቡባዊ እና መካከለኛው እስራኤል የማስጠንቀቂያ ድምፅ እየተሰማ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የጸጥታ ባለስልጣናትን ለአስቸኳይ ስብሰባ ጠርተዋል ተብሏል።

የሃማስ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ መሐመድ ዴይፍ በሃማስ ሚዲያ ቀርበው " የአልአቅሳ ማዕበል ኦፕሬሽን " በሚል ወታደራዊ ዘመቻ መጀመራቸውን ገልጸዋል።

" በየቦታው ያሉ ፍልስጤማውያን እንዲዋጉ " ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።

ዲፍ " በቃ ልንል ወስነናል " ያሉ ሲሆን ሁሉም ፍልስጤማውያን እስራኤልን እንዲጋፈጡ አሳስበዋል።

" ይህ በምድር ላይ የመጨረሻውን ወረራ ለማስወገድ ታላቅ ጦርነት የሚካሄድበት ቀን ነው " ብለው እስካሁን 5,000 ሮኬቶች ተወንጭፈዋል ሲሉ ተናግረዋል።

ሃማስ ኦፕሬሽኑ በአል-አቅሳ እየተካሄደ ላለው ትንኮሳ እና በእስራኤል እስር ቤቶች ውስጥ በፍልስጤም እስረኞች ላይ እየተወሰደ ያለውን እርምጃ ምላሽ ለመስጠት ነው ብሏል።

በደቡባዊ እስራኤል በሲዴሮት ከተማ የታጠቁ ተዋጊዎች በአላፊ አግዳሚ ላይ ተኩስ እንደከፈቱ የእስራኤል ሚዲያዎች ዘግበዋል


በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ የፍልስጤም ዩኒፎርም የለበሱ ተዋጊዎች በድንበር ከተማ ውስጥ ግጭት ሲፈጥሩ እንዲሁም የሚነድ የእስራኤል ታንክ ታይቷል።

" ሃማስ ለድርጊቱ እጅግ ከባድ ዋጋ ይከፍላል " - እስራኤል

የእስራኤል ጦር በጋዛ ሰርጥ ዙሪያ የሚኖሩ እስራኤላውያንን በቤታቸው እንዲቆዩ አሳስቧል።

ሃማስ "ለድርጊቶቹ እጅግ ከባድ ዋጋ " እንደሚከፍል ዝቷል።

ጦሩ ሃማስ ላይ ኦፕሬሽን መጀመሩ ተነግሯል።

" ከዚህ ጥቃት ጀርባ ያለው ሃማስ፣ ለቀጣይ ውጤት እና ክስተቶች ሁሉ ሃላፊነቱን ይወስዳል። " ያለው የእስራኤል ጦር ' ሰራዊቱ ለጦርነት ዝግጁ " እንዲሆን አውጇል።

አሜሪካ ሁኔታውን ብቻ ቅርበት እየተከታተለች እንደሆነ አሳውቃለች።

@tikvahethiopia
#ዓለምአቀፍ : የባንግላዴሽ ጠቅላይ ሚኒስትር ሺክህ ሃሲና ስልጣን ለቀው ሀገር ጥለው ወጡ።

በባንግላዴሽ ምን ተፈጠረ ?

➡️ ተማሪዎችና ሌላውም ዜጋ የመንግስትን የስራ ቦታ ኮታ ስርዓት በመቃወም ሰላማዊ ተቃውሞ የጀመሩት ከሳምንታት በፊት ነው።

ይህ የኮታ ተቃውሞ ምንድነው ? እኤአ በ1971 ባንግላዴሽ ለነጻነቷ ከፓኪስታን ጋር ጦርነት አካሂዳ ነበር። በዚህም " 30% የመንግሥት ስራ ለነዚሁ ተዋጊዎች ቤተሰቦች እንዲሆን " የሚል አዲስ ኮታ በመንግሥት ወጥቷል።

ተቃዋሚዎች ግን " ይህ ፍጹም አግላይና አድሏዊ ፤ ሆን ተብሎም የጠ/ሚኒስትሯን ፓርቲ ደጋፊዎች ለመጥቀም የተደረገ ነው  " በማለት ነው ተቃውሞ የጀመሩት።

➡️ በኃላ ይህ ተቃውሞ ወደ አመጽ ተቀይሯል። ይህ የሆነው ተማሪዎች ከጸጥታ ኃይሎች እና ከመንግሥት ደጋፊዎች ጋር በመጋጨታቸው ነው።

➡️ መንግሥት በተቃውሞው 150 ሰዎች ሞተዋል ቢልም የሀገሪቱ መገናኛ ብዙሃን 200 ነው የሞቱት ብለዋል።

➡️ ኢተርኔትም ተዘግቶ ነበር።

➡️ የሀገሪቱ ጠቅላይ ፍ/ቤት ተቃውሞው ሲያይል በጉዳዩ ላይ ገብቶ የሰልፈኞቹ ቁልፍ ጥያቄ የሆነውን የኮታ ስርዓቱን ለማስተካከል ሞክሮ ነበር።

እንዴት ? ለተዋጊ ቤተሰቦች የተሰጠው ኮታ ወደ 5% እንዲቀንስ ፤ 93% በሚገባው ችሎታ ብቻ እንዲሆን ፤ 2% ለአናሳ ብሔር አባላትና ለሌሎች እንዲሆን የሚል ነው።

በዚህም ነገሮች የተቀዛቀዙ መስለው ነበር። በኃላ ግን ተቃውሞውም እጅግ ሰፋ።

➡️ ተቃዋሚዎቹ " ጠቅላይ ሚኒስትሯ ለዚህ ሁሉ ቀውስ ተጠያቂ ናቸው " በማለት ስልጣን እንዲለቁ መቃወም ያዙ።

➡️ ዛሬ ሰኞ ጠቅላይ ሚኒስትሯ ስልጣን ለቀው ሀገር ጥለው ወጥተዋል።

➡️ ተቃዋሚዎች በዋና ከተማው ዳካ የሚገኘውን መኖሪያቸው / ቤተመንግስት ውስጥ ገብተው ወረዋል።

➡️ ተቃዋሚዎች ለደስታ አደባባይ ወጥተዋል ተብሏል። -
@thiqaheth

@tikvahethiopia