TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
ተሳዳቢው ማነው? | ምክንያቱስ? |

በኢትዮጵያ ውስጥ ከምክንያታዊነት ይልቅ ስሜታዊነት፣ በሰከነ መንፈስ ከማሰብ ይልቅ ፈጥኖ መኮነንና ማውገዝ እየበዛ ነው፡፡ ይህ በሁሉም የሕይወታችን ዘርፍ ላይ የሚታይ ይመስላል። በማኅበራዊ ግንኙነታችንም ሆነ በማኅበራዊ ድረገጽ አጠቃቀማችን ላይ ምክንያታዊነት በስሜታዊነት ተበልጧል፡፡ በተለይ ስድብ፣ ከስድብም ክብረ-ነክ የሆኑ ቃላት ያጀቡት ስድብ የድረገጽ (የፌስቡክና የቲዊተር) ተጠቃሚዎች መገለጫ ከሆነ ዓመታት እየተቆጠሩ ነው፡፡ እንዲህ ያሉት ነገሮች፣ ጤናማ አከባቢንና ሰላማዊ ሁኔታዎችን አብዝተው ለሚሹ ሰዎች ስሜት የሚነካ ነው፡፡

ለዚህ ማሳያ ሩቅ መሄድ አይጠበቅብንም፡፡ ከፌስቡክ በሚሰራጩ ጽሑፎች ሥር የሚቀርቡትን ዛቻዎች፣ ማስፈራሪያዎችና ስድቦች ብቻ ማየት በቂ ነው፡፡ ሃሳቡን በምክንያታዊ መከራከሪያ ከማሸነፍ ይልቅ የስድብ ካራን ከሰጎባው የሚመዝ ቁጥሩ ትንሽ አይደለም፡፡ በጣም የሚገርመው ደግሞ ከርዕሰ ጉዳዩ ጋር (ከተለጠፈው ጽሁፍ ጋር ) የማይገናኙት ስድቦችን በአስተያየት መስጫ ቦታው ላይ የሚያስቀምጡ ከጥቂት በላይ መሆናቸው ነው፡፡

‹ሰዎች በማኅበራዊ ድረገጽ ለመሳደብ የሚዳርጋቸው ነገር ምንድን ነው?› የሚለው ጥያቄ በባለሙያዎች በተደጋጋሚ ብዙ ተብሎለታል፡፡ የአውሮፓ ሕብረት በሚያዚያ 2017 ባወጣው መረጃ ላይ ስድብ አዘል የማሕበራዊ ድረገጽ አስተያየቶች ሰዎችን እንደሽብር ላሉ መጥፎ ሀሳቦች የሚያነሳሳ እንደሆነ ይገልጽና፣ በማህበራዊ ድረገጾች ላይ ክትትል ማድረግ ያስፈልጋል ሲል ይመክራል፡፡ የሕብረቱ ውሳኔ የተሳዳቢዎቹን ምክንያት አይገልጽም፡፡ ውጤቱ ወደ ሽብርተኝነት ያድጋል ሲል ማስጠንቀቁ ግን አልቀረም፡፡

እኛ ስድብ የምንለውን ጉዳይ ፈረንጆቹ ‹Hate Speech› ሲሉ ይጠሩታል፡፡ስለድረገጽ ስድቦች ጥናት ያደረጉ ሰዎች ሰዎች የሚሳደቡበት ምክንያት በተሳዳቢዎቹ አስተዳደግ ላይ ይወሰናል ይላሉ፡፡ የችግሩን መነሻ ወደ ስነልቦናዊ ትርጉም የሚወስዱት እነዚህ ተመራማሪዎች፣ሰዎች ያደጉበት ከባቢ ለስነምግባራዊነት የተመቸ ካልሆነ ተሳዳቢ ሊሆኑ እንደሚችሉ ያነሳሉ፡፡ከዚያም ለአንድ አከራካሪ ሀሳብ ከሞጋች ምክንያት ይልቅ ቀድሞ የሚመጣላቸው ስድብ ነው ይላሉ፡፡

ሌላኛው ጭፍን ጥላቻ ነው፦ አንድን አካል (ግለሰብ፣ቡድን፣የፖለቲካ ድርጅት፣ ተቋም ወዘተ) ያለበቂ ምክንያት መጥላት ከተጀመረ ጭፍን ጥላቻ ይባላል፡፡ከዚያም እርሱ የነካውንና ያየውን ሁሉ #ለማራከስና #ለማጥላላት ስድብ ጥቅም ላይ ይውላል፡፡

ለማኅበራዊ ድረገጽ ተሳዳቢዎች እንደሶስተኛ ምክንያት የሚጠቀሰው የአማራጭ ሃሳብ ማፍለቅ እጥረት ነው፦ አንድ ጉዳይ ላይ አስተያየት ለመስጠት የሚያስችል ዕውቀት ሳይኖር ሲቀርም ስድብ የአቅም ማነስን ለመሸፈን ይውላል፡፡ ሰዎች አንድን ጉዳይ በጭፍን ከመጥላታቸውም ባሻገር ሃሳብን በሃሳብ ለመሞገት የሚያስችል ዳራዊ ዕውቀት ሳይኖራቸው በሚቀር ወቅት የስድብ ካዝናቸውን ይከፍታሉ፡፡

ሰዎች ወደ #ፌስቡክ በመጡ ወቅት #ስድብን ለምን ይመርጣሉ ለሚለው ጥያቄ ብዙ አስረጂዎች ይቀርባሉ፡፡በርግጥ በኢትዮጵያ ያለው የማኅበራዊ ድረገጾች አጠቃቀም ወደ ስድብ ያደገበት ምክንያት #አልተጠናም፡፡ የሆነው ሆኖ ከላይ የተዘረዘሩት ዓለማቀፋዊ ምክንያቶች እኛንም መዳሰሳቸው አልቀረም፡፡

ይሁን እንጂ ጉዳዩን ከትምህርት ሥርዓታችን ጋር አገናኝተው አስተያየት የሚሰጡ ሰዎች አይጠፉም፡፡ለድሬ ቱዩብ ሃሳቡን ያጋራ (ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ) አንድ የስነ-ማኅበረሰብ ተመራማሪ እንደሚለው፣የፌስቡክና የሌሎች ማኅበራዊ ድረገጾች ላይ ስድብ ይዘው የሚቀርቡ ግለሰቦች የትምህርት ጥራቱ ያለበትን ደረጃ የሚያሳዩ ናቸው፡፡

እንደሚታወቀው የፌስቡክ ‹አካውንት› ለመክፈት የሚያስፈልገው ዋና ጉዳይ ማንበብና መጻፍ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥም ያለው ፌስቡክ ተጠቃሚ እነዚህን መሰረታዊ ሃሳቦች የሚያውቅና ቢያንስ የ8ኛ ክፍል ትምህርቱን ያጠናቀቀ (አንዳንዶች ዳያስፖራና ከ12ኛ ክፍል በላይ የሆነው ይበዛል ብለው ይሞግታሉ) ነው፡፡ ይሁን እንጂ በትምህርት ቤት በነበረበት ጊዜ #ኢሞራላዊና ከስነምግባር ያፈነገጡ ሃሳቦችን መሰንዘር ብልግና መሆኑን ሳያውቅ የወጣ በመሆኑ #ስድብን እንደማሸነፊያ ሀሳብ ይወስደዋል፡፡

ባለሙያው እንደሚሉት፣ እነዚህ ማንበብና መጻፍ በመቻላቸው ብቻ የፌስቡክ አካውንት የከፈቱ ሰዎች መከራከሪያ የሚሆን ምክንያታዊ ሐሳብ ስለሚቸግራቸው (Lack of alternative rationality) ስራቸው ስድብ ብቻ ይሆናል፡፡ እያንዳንዷን የፌስቡክና የቲዊተር ሃሰብም እየተከታተሉ፣ ሁሉም የፌስቡክ ሰው እንደነሱ ያስብ ዘንድ ይጠብቃሉ፤ ሁሉም ሰው #እነርሱ የሚጠሉትን #እንዲጸየፍ፣ የሚወዱትን ደግሞ እንዲወድ ይሻሉ፡፡ያንን ያላደረገውን #ይሰድቡታል፡፡ እነዚህ የስድብ ደርዘን መዝዘው የማይጨርሱ ሰዎች ያለፉበት የትምህርት ሥርዓት፣ ምክንያታዊነትን፣ የሰውን ሃሳብ ማክበርን፣ ሰውን ማክበርን፣ወዘተ አላስተማራቸውም፡፡

ይህንና ሌሎች ማስረጃዎችን እየጠቀሱ አስተያየት የሚሰጡ ብዙ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ለመሆኑ ማኅበራዊ ድረገጾቻችን ስለምን መከባበርን ሊያስተምሩን አልቻሉም? ስለምንስ መሰዳደብ በዛ? ይህስ ወዴት ያደርሰናል? የወቅቱ አንገብጋቢ ጥያቄ ይመስላል! 

Via መላዕክነሽ ሽመልስ በድሬቲዩብ (DIRETUBE)

#ሼር #share
@tsegabwolde @tikvahethiopia