TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
#ETHIOPIA

ከሰሞኑን የፌዴራሉ መንግስት የ #ሰላም_ስምምነቱን በተመለከተ ከ50 በላይ ለማሆኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች ማብራሪያ ሰጥቶ ነበር።

ማብራሪያውን ከሰጡት መካከል የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን (አምባሳደር) ነበሩ።

በወቅቱ ፤ የመድረኩ ተሳታፊ የነበሩት የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ጠንከር ያሉ ጥያቄዎችን አቅርበው ነበር።

ምን ተጠየቀ ? ምንስ ምላሽ ተሰጠ ?

- ስለወልቃይት ባለቤትነት፣
- ስለኤርትራ ወታደሮች፣
- ስለሰላም ስምምነቱ ግልጽነትና የመረጃ አሰጣጥ፣
- ስለሰላም ስምምነቱ ተደራዳሪዎች ጥያቄዎች ቀርበው ነበር።

የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራሲ ፓርቲ (የኢሶዴፓ) ምክትል ፕሬዚዳንት ራሔል ባፌ (ዶ/ር) ፦

" ከወልቃይት ጋር እየተነሳ ያለው ጉዳይ፣ ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ በአንድ በኩል የባህር በር ስታጣ በሌላ በኩል ደግሞ ወልቃይትን በመቀማት አገሪቱ ከሌላ አገር ጋር እንዳትገናኝ ለመዝጋት የተደረገ እንቅስቃሴ በመሆኑ መንግሥት ጉዳዩን እንዴት እየተከታተለው ነው ? "

የኢዜማ ተወካይ ጫኔ ከበደ (ዶ/ር) ፦

" በሰላም ስምምነቱ ትግራይ ክልል ከአማራና ከአፋር ክልሎች ጋር በሚዋሰንባቸው አካባቢዎች የሚነሱ ጉዳዮችን በተመለከተ ስምምነቱ ምን ይላል ? በዚህ የተዳፈነ እሳት ላይ የታሰበ ነገር ካለ ቢነገረን ? "

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረንስ (ኦፌኮ) አመራር አባል አቶ ሙላቱ ገመቹ ፦

" የኤርትራ ሠራዊት ከትግራይ ክልል አልፎ በቤኒሻንጉል ጉሙዝና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ እየተንቀሳቀሰ ነው። መንግሥት ለምን ዝምታን መረጠ ? "

የእናት ፓርቲ ፕሬዚዳንት ሰይፈ ሥላሴ አያሌው (ዶ/ር) ፦

" የሰላም ስምምነት ለአገር ተሰፋ የፈነጠቀ ቢሆንም፣ ድርድሩ ሲካሄድ የተሳተፉ የብልፅግና እና የሕወሓት ሰዎች ብቻ መሆናቸው ቅሬታ ፈጥሮብናል።

በጦርነቱ ውስጥ ዋነኛ ሰለባና ገፈት ቀማሽ የነበሩት የአማራና የአፋር ክልሎች ሕዝቦች ለምን እንዲሳተፉ አልተደረገም ?

በተጨማሪም እየተከናወኑ ያሉ ውይይቶችና ድርድሮች ለሕዝብ እየተነገሩ አይደለም።

ሲዋጋ፣ ሲሞትና ሲቆስል የነበረው ሕዝብ በመጨረሻ ስለተደረሰበት ስምምነት መንግሥት መረጃ ሊሰጠው የገባል።

ከአራት ዓመት በፊት የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ከነበረበት ኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ እንዲገባ ሲደረግ መንግሥት ፈጸምኳቸው ያላቸውን ስምምነቶች በርካታ ቢሆኑም፣ ለሕዝብ ግልጽ ሳይደረጉ አሁን የሚታየው ጥፋት ተከስቷል። "

የጠ/ሚኒስትሩ ብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ምን ምላሽ ሰጡ ?

አምባደር ሬድዋን ሁሴን ፦

ወልቃይት ...

" የወልቃይት ጉዳይ በ #ሕገ_መንግሥቱ መሠረት ይፈታል።

ከጅምሩ የጦርነቱ ዓላማ ወልቃይትን ማስመለስ እና ሕወሓትን ማጥፋት አልነበረም።

የጦርነቱ ዋና ዓላማ የነበረው የአገሪቱን ሉዓላዊነት ማስከበርና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት ማስፈን ነው

ሕወሓትን እንደ ፖለቲካ ኃይል የማጥፋት ዓላማ ያለው ሰው ይኖራል፣ ነገር ግን የፌዴራል መንግሥቱ ዓላማ አይደለም።

ወልቃይት በአማራ እና በትግራይ ክልሎች መካከል ያለ ፀብ ነው፣ በሁለት ክልሎች መካከል ያለው ፀብ ደግሞ የሚፈታው የፌዴሬሽን ምክር ቤት በሚመራው ሥርዓት።

የፌዴራል መንግሥት አቋም ተራ በተራ ጡንቻ እየተፈታተን አንዳችን ሌላችንን ማንበርከክ ይቁም የሚል ነው።

ወልቃይትን ከዚህ ቀደም ሕወሓት ጡንቻ ስለነበረው በጉልበት ወስዷል፣ አሁን ደግሞ ሕወሓት ሸብረክ ሲል ጡንቻ ያለው አካል ይውሰድ ካልን መጪው ትውልድ 20 ዓመታትን ጠብቆ ድንገት ጡንቻ ካገኘ ይወስደዋል ፤ ስለዚህም ዘላቂው መፍትሔ ጡንቻ ሳይሆን ሕግና ሥርዓት ነው።

አንድ ሰው ትግራይን ሲወድ ካርታውን ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን ነው፣ ነገር ግን ካርታውን ወዶ ሕዝቡን መጥላት አይቻልም።

ቲፎዞና ደም መርጠን መለቃቀስ ይቅር፣ የትም ቦታ ሰው ሲሞት ሁላችንም  ሊሰማን ይገባል። "

ኤትራን በተመለከተ ...

" የእኛ ወገን ናቸው የምንላቸው የሕወሓት ሰዎች ለ30 ዓመታት ታገልኩለት ያሉትን ሕዝብ ለ30 ዓመታት እየቀለበ፣ እየጠበቀ፣ አብሮ እየሠራና እያረሰ የኖረውን ሠራዊት ከጀርባው አርደው ሜዳ ላይ ሲጥሉት የታደጉት እነዚህ ሰዎች ናቸው፡፡ ለአጭር ጊዜም ቢሆን ውለታን መርሳት ነውር ነው።

በሦስተኛው ዙር አገሪቱን ለመጨረሻ ጊዜ ለማፍረስ በተካሄደው ጦርነት የፌዴራል መንግሥት በቆቦ በኩል ባለው ዳገት ወደ ላይ መውጣት ላዳገተው፣ ሕወሓት ያለውን መልክዓ ምድራዊ ጠቀሜታ ተጠቅሞ ቆቦን ተቆጣጥሮ ነበር።

ወቅቱ ክረምት ስለነበር በምዕራብ በኩል ተከዜን ሠራዊቱ ማቋረጥ ባለመቻሉ ፣ #በዛላምበሳ እና #በአዲግራት ለመምጣት ተከዜን መሻገር የኤርትራ መንግሥት በመፍቀዱ ጦርነቱ ሊቀለበስ ችሏል።

ለአጭር ጊዜም ቢሆን በራቸውን ባይፈቅዱልን ኖሮ ይኼንን ጦርነት መቀልበስ አይቻልም ነበር፡፡ እንደ አገር ከባድ ፈተና ውስጥ እንወድቅ ነበር።

የኤርትራ መንግሥት ይኼን ያደረገው ሕወሓት በዚያ ጊዜ የጋራ ጠላታችን ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ሕወሓት የጋራ ጠላት የሚሆነው ትጥቁን እስኪፈታ ነው። ትጥቁ ከሌለ አደጋ አይሆንም።

በፖለቲካ መጠላላት እና መለያየት ሲኖር ያለ ሦስተኛ ወገን በራችንን ዘግተን መነጋገር እንችላለን። "

የኤርትራ ሰራዊት ጉዳይ ...

" ' የኤርትራ ሠራዊት ከኢትዮጵያ ይውጣ ' የሚሉት አካላት ለኢትዮጵያ አዝነው አይደለም። ኤርትራ ይውጣ የሚሉ አካላት ሱዳን 50 ኪሎ ሜትር አልፎ ድንበር ወሮ በነበረበት ወቅት አፋቸውን ዘግተው ነበር።

በተመሳሳይ #ግብፅ በሚሊዮን በሚቆጠር ገንዘብ መድባ ወደ ኢትዮጵያ መሣሪያ እያስገባች በጋምቤላ ለኦነግ ሸኔና ለሕወሓት ጭምር በአየር እና መሬት ላይ ስታስታጥቅ፣ እነዚህ ምንም አላሉም ፤ ይህ የሚያሳየው መንግሥትን የሚያዳክም ሲሆን ዝምታ፣ መንግሥትን የሚያግዝ ሲሆን ደግሞ ጩኸት ማብዛት የሚወዱ በመኖራቸው ነው።

በመሆኑም ኤርትራ እኛን አስቸገረን ካላልን ምን አሳሰባቸው ? ኤርትራ ባስቸገረን ጊዜ እኛ ራሳችን በቃን እንላለን፡፡

የኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ካሳሰባችሁ ሱዳን ትውጣ ብላችሁ መግለጫ አውጡ፡፡ ከዚያ ኤርትራ ትውጣ ብትሉ እኛ መረዳት እችላለን።

በሌላ በኩል በእኛ አስታኮ የኤርትራ መንግሥትን መውጋት ለሚፈልግ ኃይል አንተባበርም፡፡ ቢያንስ ከተፈጠረው የሰላም ስምምነት አንፃር እኛ እንዳንፈርስ አግዘውናል፡፡

የጋራ ጠላት የነበረን ቢሆንም ትጥቁን የፈታ የሕወሓት ታጣቂ ግን ኢትዮጵያዊ ነው። ስለዚህ አቅማችን ባለበት እስኪጠናከር ሕወሓት መጀመሪያ ትጥቁን መፍታት ይጀምርና እንደማንወጋ ስናረጋግጥ፣ ከጀርባችን ያለው አካል ማንም ይሁን ማን ይውጣልን ማለት እንችላለን። "

ምንጭ፦ www.ethiopiareporter.com

@tikvahethiopia