TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.4K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
አብዲ ኢሌ ላይ ክስ ተመሰረተ‼️

በሶማሌ ክልል የቀድሞው ፕሬዚዳንት አቶ አብዲ #መሃመድ_ዑመርን ጨምሮ በ47 ግለሰቦች ላይ #ክስ ተመሰረተ።

ተከሳሾቹ አቶ አብዲ ሙሃመድ፣ ራህማ መሀመድ ሀይቤ፣ አብዱራዛቅ ሰሀኔ ኢልሚ፣ አቶ ፈርሃን ጣሂር በርከሌ፣ ጉሌድ ኦበል ዳውድ እና ወርሰሜ ሼህ አብዲ ሸሂድን ጨምሮ 47 ግለሰቦች ናቸው። ተከሳሾች በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ የወንጀል ችሎት ነው ክስ የተመሰረተባቸው። ግለሰቦቹ ለጊዜው ካልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን በቀጥታ ወይም በአድራጎታቸው በወንጀሉ ተካፋይ በመሆን በህብረትና በማደም፥ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ቀኑ ባልታወቀ ሰኔ ወር 2010 ዓ.ም እስከ ሀምሌ 30 ቀን 2010 ዓ.ም ድረስ ባሉት ቀናቶች በክልሉ ውስጥ አንዱ ወገን በሌላው ወገን ላይ የጦር መሳሪያ እንዲያነሳ ለማድረግ በማሰብ መንቀሳቀሳቸው
ተጠቅሷል።

በዚህም በአንዳንድ የሶማሌ ብሔር ተወላጆች እና በሶማሌ ክልል በሚኖሩ የሌሎች ብሄር ተወላጆች መካከል አለመግባባት እንዲፈጠር በማሰብ በግጭቱ ውስጥ የሚሳተፉና ሄጎ በሚል ወጣቶችን ማደራጀታቸውም በክሱ ተነስቷል። የተደራጀውን የሄጎ ቡድን በገንዘብ እና በተለያዩ ቁሳቁሶች በመደገፍ፣ መሳሪያ በማስታጠቅ፣ ግጭቱ የሚመራበትና መልዕክት የሚተላለፍበት ሄጎ ዋሄገን የሚል የፌስቡክ ገጽ በመክፈትና በተለያዩ ስብሰባዎች ላይ ሰዎችን ሊያነሳሱ የሚችሉ መልእክቶችን አስተላልፈዋልም ነው ያለው የአቃቢ ህግ ክስ።

በኦሮሞ ወታደሮች ተወረናል፣ የኦሮሞ ተወላጆች መሬታችንን ለቀው መውጣት አለባቸው፣ ነዳጃችንን፣ መሬታችንን እና ወርቃችንን በጉልበት ሊወስዱብን ነው፣ የፌደራል መንግስት በህገወጥ መንገድ ሊወረን እና አዲስ መንግስት ለማቋቋም እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፣ ሁላችንም አንድ በመሆን በክልላችን ውስጥ ከሶማሌ ብሄር ውጭ ያሉ ብሔረሰቦችን መግደል፣ ንብረታቸውንም መዝረፍ እና ማውደም፣ ባንኮችን እና ኢንሹራንሶችን መዝረፍ፣ ቤተክርስቲያኖችን እና ነዳጅ ማደያዎችን ማቃጠል አለብን የሚል ይዘት ያላቸውና ሌሎች መልዕክቶችም ተላልፈዋል ነው ያለው አቃቢ ህግ።

ከዚህ ጋር ተያይዞም ይህንን ማድረግ የሚያስችል የራሳችን ወታደሮች እና የተደራጁ የሔጎ አባላት አሉን በሚል እንዲሁም በስብሰባና በፌስ ቡክ ቅስቀሳ በማድረግ እንዲሁም የክልሉ አድማ ብተና ሃይልም ሄጎዎች የሚሰሩትን ማንኛውንም ነገር እንዳይከላከል ከካምፕ እንዳይወጣ ትእዛዝ ሰጥተዋልም ተብሏል።

እንዲሁም በክልሉ ውስጥ ግጭት እንዲነሳ በማድረግና በግጭቱ ምክንያት የሰው ህይወት እንዲጠፋ፣ በመንግስት እና በእምነት ተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ንብረት ላይ ጉዳት እንዲደርስ፣ ሴቶች እንዲደፈሩና እና በርካታ የከተማው ነዋሪ እንዲፈናቀል ማድረጋቸውም በክሱ ተካቷል። በአጠቃላይ ከ1ኛ እስከ 26ኛ ተራ ቁጥር የተመለከቱት ተከሳሾች ከላይ በተገለጸው አግባብ በመቀስቀስና በማነሳሳት በዚህ የማነሳሳት ተግባራቸው በሶማሌ ብሔር ተወላጆች እና በክልሉ የሚኖሩ ሌሎች ብሔሮች መካከል አለመግባባት እና ግጭት እንዲፈጠር አድርገዋልም ነው የተባለው።

በዚህ ግጭትም በሰነድ ማስረጃው ላይ በተገለፀው አግባብ ከ59 ሰዎች በላይ ህይወት እንዲጠፋ፣ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አገልጋይ የሆኑ ካህናት እና የእምነቱ ተከታይ የሆኑ ግለሰቦች በአሰቃቂ ሁኔታ ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ በመግደልና በእሳት እንዲቃጠሉ ማድረጋቸው በክሱ ተነስቷል። ከ266 በላይ ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት እንዲደርስ፣ በምስክርነት የተጠቀሱ ሴቶችን በሄጎ ቡድን እና በክልሉ ልዩ ሀይል ፖሊስ አባላት እንዲደፈሩ በማድረግ እንዲሁም ግምቱ 412 ሚሊየን 468 ሺህ 826 ብር በላይ የሚሆን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን፣ የመንግስት፣ በግለሰብ መኖሪያ ቤትና የንግድ ድርጅት ንብረቶች እንዲቃጠሉ፣ እንዲዘረፉ እና ብዛታቸው በውል ያልታወቁ ከሶማሌ ብሔር ተወላጅ ውጭ የሆኑ የከተማው ነዋሪዎች ከቤትና ንብረታቸው እንዲፈናቀሉ አድርገዋልም ነው የሚለው ክሱ።

በዚህም ተከሳሾች በፈፀሙት የጦር መሳሪያ ይዞ በማመጽ ወይም የእርስ በእርስ ጦርነት በማስነሳት በመንግስት ላይ የሚደረግ ወንጀል ክስ ቀርቦባቸዋል። በዛሬው እለት ተከሳሾች ከጠበቆቻቸው ጋር የቀረቡ ባለመሆናቸው ክሳቸውን በንባብ ለመስማት ፍርድ ቤቱ ለጥር 29 ቀን 2011 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል። በተያያዘም አቶ ቴዎድሮስ አዲሱ (ቴዲ ማንጁስ) በ80 ሺህ ብር ዋስ እንዲወጣ ተፈቅዶለታል። ቴዲ ማንጁስ በሶማሌ ክልል በተፈጠረው ግጭት የሰው ህይወት መጥፋትና መፈናቀል ወንጀል ላይ ተሳትፏል በሚል መጠርጠሩ ይታወሳል።

ምንጭ፦ fbc
@tsegabwolde @tikvahethiopia
TIKVAH-ETH ማጠቃለያ🗞ጥር 22/2011 ዓ.ም.

በሶማሌ ክልል የቀድሞው ፕሬዚዳንት አቶ አብዲ #መሃመድ_ዑመርን ጨምሮ በ47 ግለሰቦች ላይ #ክስ ተመስርቷል።
.
.
ለከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች የትራንስፖርት አገልግሎት በመስጠት ላይ ያሉትን ‹‹ቪ8›› መኪኖች በሌሎች አዳዲስና ወጪ ቆጣቢ ተሽከርካሪዎች የመተካቱ ሂደት በመጠናቀቅ ላይ መሆኑ ተገልጿል።
.
.
በድሬዳዋ ከተማ ተፈጥሮ በነበረው #አለመረጋጋት እና የተቃውሞ ቀናት ጉዳት ሳይደርስበት በሀሰት ጉዳት የደረሰበት በማስመሰልና ይህንን የሃሰት ፎቶ በማህበራዊ ድረ ገፅ በመልቀቅ ግጭቶች እንዲፈጠሩ ለማድረግ የሞከረው ግለሰብ በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡
.
.
በቅርቡ የፀደቀውን የስደተኞች አዋጅ በመቃወም በአዲስ አበባና በጋምቤላ #የተቃውሞ_ሠልፍ ሊደረግ እንደሆነ ተሰምቷል።
.
.
በሶማሌ ክልል ግጭት፣ ግድያና ቃጠሎ ጋር በተያያዘ ከአራት ወራት በላይ በእስር ላይ የነበረው #ቴዎድሮስ_አዲሱ (ቴዲ ማንጁስ) በ80,000 ብር ዋስ ከእስር እንዲፈታ ፍርድ ቤት ትእዛዝ ሰጥቷል።
.
.
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን "ግዴታዬን እወጣለሁ ፣ መብቴንም እጠይቃለሁ!" በሚል መርህ ቃል የከተማ አቀፍ የታክስ ንቃናቄ መድረክ ተካሂዷል።
.
.
ከኮንሶ ዞን ወደ ሶያማ ቡርጂ ወረዳ ሲጓዝ በነበረ የጭነት መኪና ላይ ባልታወቁ #ታጣቂዎች በተከፈተ ተኩስ በትላንትናው ዕለት የአራት ሰዎች ህይወት አልፏል።
.
.
#በምሥራቅ_ወለጋ_ዞን በተለያዩ ወረዳዎች የሚገኙ በጎ ፈቃደኛ ተማሪዎች 2ሺህ 380 ዩኒት ደም መለገሳቸውን የነቀምቴ ደም ባንክ አገልግሎት አስታውቋል።
.
.
የመልካም አስተዳደርና የሥራ  አጥነት መሠረታዊ ጥያቄዎች በፍጥነት ለመመለስ የሚያግዝ የ60 ቀናት ዕቅድ ተዘጋጅቶ እንቅስቃሴ መጀመሩን የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ ተናግረዋል።
.
.
ሰሞኑን በድሬዳዋ በተፈጠረው ሁከትና ነውጥ #በማራገብ ሂደት #ፖሊስ እና #አድማ_በታኝ አሉበት፤ ይህም በፖሊስ ውስጥ መሠረታዊ ሪፎርም እንደሚያስፈልግ ያመለክታል ተብሏል።
.
.
15ኛው የኢትዮ-ጅቡቲ የጋራ ኮሚሽን ስብሰባ በዛሬው ዕለት በጂቡቲ ተጀምሯል፡፡
.
.
ትናንት በሶማሌ ክልል መዲና- ጅግጅጋ የሃይማኖት ክብረ በዓልን ተከትሎ በተፈጠረ ግጭት ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተነግሯል።
.
.
የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ እና የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው #በኔዘርላንድ የሚገኙ ኩባንያዎችን ጎብኝተዋል።
.
.
የኢትዮጵያ #ጉብኝታቸዉን አጠናቀዉ ወደ ሀገራቸው ለመመለስ በዝግጅት ላይ ያሉት የጀርመኑ ፕሬዝዳንት ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር የሚበሩበት አዉሮፕላን የቴክኒክ #እክል ገጥሞት መዘግየቱ ተሰምቷል።
.
.
ከአዲስ አበባ ወደ ነቀምት በህገ-ወጥ መንገድ ሲጓጓዝ የነበረ 11 ሺህ ሊትር ነዳጅ መያዙን የኢሉገላን ወረዳ ፖሊስ አስታውቋል።
.
.
በአማራ ክልል በአምሀራ ሳይንት ወረዳ በአጅባር ከተማ በተቀሰቀሰ #ተቃውሞ የመንግስትም ሆነ የግል ተቋማት ከትላንት ከሰዓት ጀምሮ አገልግሎት መስጠት ማቋረጣቸውን ነዋሪዎች ገልፀዋል።
.
.
ከጥረት ኮርፖሬት የሃብት ምዝበራ ጋር በተያያዘ የአምባሰል ንግድ ስራዎች ስራ አስኪያጅ የነበሩትን አቶ #ምትኩ_በየነን ጨምሮ አምስት ሰዎች ዛሬ በአዲስ አበባ ከተማ በህግ ቁጥጥር ስር ውለዋል።
.
.
የኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያና ዩጋንዳ የፖሊስ አመራሮችና አቃቤ ሕጎች የሶስት ቀናት አውደጥናትን ዛሬ #በኤርትራ_አስመራ ተጀምሯል፡፡
.
.
በአለም ላይ ያለውን የነዳጅ ምርቶች ዋጋ ጭማሪን ግምት ውስጥ በማስገባት እና በህዳር ወር ተደረገው ዋጋ #ማስተካከያ ዝቅተኛ በመሆኑ፥ በነዳጅ ምርቶች የችርቻሮ መሸጫ ዋጋ ላይ #መጠነኛ_ጭማሪ ማድረጉን የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አስታውቋል።

ምንጭ፦ etv፣ fbc፣ የጀርመን ራድዮ፣ ኢ.ፕ.ድ፣ ኢዜአ፣ የንግድ እና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር፣ የTIKVAH-ETH ቤተሰብ አባላት

ሰላም እደሩ!!
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!
@tsegabwolde @tikvahethiopia