#ቀረጥ_ነጻ

ወደ አገር በሚገቡ እቃዎች ላይ ከተጣለው የማህበራዊ ልማት ቀረጥ ነጻ የሚሆኑ እቃዎችን ለመወሰን ገንዘብ ሚኒስቴር መመሪያ አውጥቷል።

ይኸው መመሪያ " መመሪያ ቁጥር 1023/2017 " ይሰኛል።

በዚህ መመሪያ መሰረት ፥ ለህብረተሰቡ በነጻ የሚሰጡ የትምህርት እና የጤና አገልግሎቶችን ለማስፋፋት እንዲሁም በሰው ሰራሽ እና በተፈጥሮ አደጋ ምክንያት ችግር ላይ የሚገኙ ወገኖችን ለመርዳት ከውጭ አገር በእርዳታ የሚላኩ እቃዎች የማህበራዊ ልማት ቀረጥ የተጣለበትን አላማ ለማሳካት የሚያግዙ በመሆኑ ከቀረጥ ነጻ እንዲሆኑ ተደርጓል።

ከማህበራዊ ልማት ቀረጥ ነጻ የተደረጉ እቃዎች ?

የሚከተሉት እቃዎች ከማህበራዊ ልማት ቀረጥ ነፃ ሆነው ወደ ሀገር ይገባሉ፡፡

1. ለሚከተሉት የማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማት ከውጭ አገር በእርዳታ የሚላኩ እቃዎች :-

ሀ/ በመንግስት ባለቤትነት ስር ያሉ ወይም ለህብረሰሰቡ ነጻ አገልግሎት የሚሰጡ :

- የትምህርት ተቋማት፣
- የጤና ተቋማት፣
- የሕጻናት፤ የሴቶች፤ የአረጋውያን፣ የአእምሮ ህመምተኞች እና የአካል ጉዳተኞች መርጃ ድርጅቶች

ለ/ በሰው ሰራሽ እና በተፈጥሮ አደጋ ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ለሚሰጡ ድርጅቶች ከውጭ አገር በእርዳታ የሚላኩ እቃዎች

2. ኢትዮጵያ በፈረመቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ከቀረጥ እና ታክስ ነጻ ሆነው ወደአገር እንዲገቡ የተፈቀደ እቃዎች።

3. የአገር መከላከያ ሚኒስቴር፣ የፌዴራል እና የክልል ፖሊስ ተቋሞች፣ የብሔራዊ መረጃ እና ደሕንነት አገልግሎት እና ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በሕግ በተፈቀደው መሰረት ወደ አገር የሚያስገቧቸዉ የመከላከያ እና የህዝብ ደህንነት መሳሪያዎች፣ ለነዚሁ አገልግሎት የሚዉሉ ክፍሎችና እና አክሰሰሪዎች፡፡

4. በብሔራዊ ባንክ ወደ ሀገር የሚገቡ ሳንቲሞች፣ የገንዘብ ኖቶች እንዲሁም የብርና የወርቅ ጠገራዎች፡፡

ከቀረጥ ነፃ #የማይሆኑ እቃዎች ምንድናቸው ?

ከዚህ በታች የተዘረዘሩት እቃዎች ከማህበራዊ ቀረጥ ነጻ ሆነው ሊገቡ #አይችሉም።

ሀ/ ከ8 መቀመጫ በታች ያላቸው አውቶሞቢሎች  እና የእነዚህ መለዋወጫዎች።

ለ/ ባለአንድ ወይም ባለሁለት ጋቢና ፒካፕ ተሽከርካሪዎች እና የእነዚህ መለዋወጫዎች።

ሐ/ ለቢሮ አገልግሎት የሚውሉ ዕቃዎችና መሣሪያዎች።


በዚህ መመሪያ መሰረት ከቀረጥ ነጻ ሆነው ሊገቡ የሚችሉ እቃዎች ማስረጃዎች ማቅረብ የግድ ይላል።

ምን አይነት ማስረጃዎች መቅረብ አለባቸው ?

1. እቃዎቹ በእርዳታ የተገኙ መሆኑን የሚያረጋግጥ የእርዳታ የምስክር ወረቀት።

2. የእቃዎቹን ዝርዝር እና ዋጋ የሚያሳይ ኢንቮይስ፣

3. እቃዎቹ ለተገለጸው አላማ የሚውሉ መሆኑን እንዲሁም ስለእቃዎቹ አጠቃቃም ለገንዘብ ሚኒስቴር እና ለጉምሩክ ኮሚሽን ሪፖርት የሚቀርብ መሆኑ የሚያረጋግጥ አግባብ ባለው ከመንግስት መስሪያ ቤት የተጻፈ የድጋፍ ድብዳቤ።

#TikvahEthiopia #MinistryofFiance

@tikvahethiopia