TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
#እንድታውቁት🚨

በአዲስ አበባ የጭነት ፣ ማሽነሪዎችን እና መሰል ተሸከርካሪዎችን እንቅስቃሴ ለመወሰን የወጣ መመሪያ ቁጥር 149/2016 ምን ይላል ?

- መመሪያው ወደ አዲስ አበባ ከተማ ክልል በሚገቡና በከተማ ውስጥ በሚንቀሳቀሱ እንዲሁም ከተማዋን አቋርጠው በሚያልፉ የመጫን አቅማቸው ከ1 ቶን ወይም ከ1ዐ ኩንታል በላይ የሆኑ የተለያዩ የፈሳሽና የደረቅ ጭነት ተሽከርካሪዎች እና የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች ላይ ተፈፃሚ ይሆናል፡፡

- ማንኛውም የጭነት ማመላለሻ ተሽከርካሪ እና የኮንስትራክሽን ማሽነሪ ከጠዋቱ 1፡00 እስከ 3፡00 ሰዓት ከሰዓት በኃላ ከቀኑ 10፡30 እስከ ምሽቱ 1፡ዐዐ ሰዓት ወደ ከተማ ውስጥ መግባትም ሆነ በከተማ ውስጥ መንቀሳቀስ፣ ጭነት መጫንም ሆነ ማራገፍ እንዲሁም በዋና ዋና የትራፊክ ፍሰት በሚበዛባቸው መንገዶች ላይ መቆም የተከለከለ ነው፡፡

- በዚህ መመሪያ መሠረት ወደ ከተማ መግባትም ሆነ በከተማ ውስጥ መንቀሳቀስ የተከለከለ የጭነት ተሽከርካሪ ወይም የኮንስትራክሽን ማሽነሪ ወደ ከተማ ለመግባት በእንቅስቃሴ ላይ እያለ የሰዓት ገደቡ ቢደርስበት በከተማዋ መግቢያ በሮች ላይ ከዋና መንገድ ወጣ ብሎ በሚገኝ ቦታ ላይ የአካባቢውን የትራፊክ እንቅስቃሴ በማያውክ መልኩ በመቆም የሰዓት ገደቡ እስኪያልፍ መጠበቅ አለበት።

- ማንኛውም የጭነት ተሽከርካሪ ወይም የኮንስትራክሽን ማሽነሪ በከተማ ውስጥ በእንቅስቃሴ ላይ እያለ በዚህ መመሪያ የተደነገገው የጊዜ ገደብ ቢደርስበት የአካባቢውን የትራፊክ እንቅስቃሴ በማያውክ መልኩ ከመንገድ በመውጣት መቆም አለበት።

- በዚህ መመሪያ የተደነገገው የሰዓት ገደብ #እሁድ እና #የበዓል_ቀናት ላይ ተግባራዊ የማይደረግ በመሆኑ ማናቸውም የጭነት ተሸከርካሪ ወይም የኮንስትራክሽን ማሽነሪ ወደ ከተማ ውስጥ መግባትም ሆነ በከተማ ውስጥ መንቀሳቀስ፣ ጭነት መጫን ሆነ ማራገፍ ይችላል፡፡

የሰዓት ገደብ የማይመለከታቸው ተሽከርካሪዎች የትኞቹ ናቸው ?

1. ሰሌዳቸው በሀገር መከላከያ ወይም በፖሊስ የተመዘገቡ የሀገር መከላከያ እና ሌሎች የፀጥታ ስራዎችን የሚያከናወኑ ከባድና ቀላል የጭነት ተሽከርካሪዎች፤

2. በህግ መሠረት የድንገተኛ አደጋ ተሸከርካሪዎች ተብለው የተለዩ የድንገተኛ አደጋ የሚሰሩ ቀላልና ከባድ የጭነት ተሽከርካሪዎች፤

3. ነዳጅ የሚያመላልሱ ቦቴዎች

አስተዳደራዊ ቅጣቱ ምን ይመስላል ?

🔵 በተከለከለ ሰዓት ወደ ከተማ ውስጥ በመግባትና በዋና ዋና መንገዶች ላይ የቆመ ብር 10,000 (አስር ሺህ ) ይቀጣል፡፡

🔵 በዋና ዋና መንገድ ላይ የተንቀሳቀሰም ሆነ የጭነት መጫንና ማውረድ ተግባር የፈፀመ ወይም የኮንስትራክሽን ስራ የሰራ ብር 20,000 (ሃያ ሺህ) ይቀጣል፡፡

🔵 በመመሪያው ላይ የተደነገገወን የሰዓት ገደብ በመተላለፍ ከተቀጣ በኃላ ለሁለተኛ ጊዜ ጥፋቱን በመድገም የተገኘ ማንኛውም ሰው ከላይ የተገለፀውን ቅጣት በእጥፍ ይከፍላል፡፡

NB. በተከለከለው ሰዓት በከተማው ውስጥ ሲንቀሳቃስ በመገኘቱ ቅጣት የተጣለበት አሸከርካሪ ሰዓቱ ሳይደርስ የቅጣት ወረቀት ይዞ በተከለከለው ሰዓት እንዲንቀሳቀስ አይፈቀድለትም። የትራፊክ ተቆጣጣሪው ፍሰት በማያሰናክል ቦታ ላይ ተሸከርካሪው እንዲቆም በማድረግ ቅጣቱን እንዲከፍል ማድረግ አለበት፡፡

🗓 ይህ መመሪያ ከመስከረም 2 ቀን 2017 ዓ/ም ጀምሮ ተግባራዊ መሆን ይጀምራል።

#TikvahEthiopiaFamilyAA

@tikvahethiopia
Please open Telegram to view this post
VIEW IN TELEGRAM