#ለጥንቃቄ🚨

“ በተለይ እንቅስቃሴያቸውንና ኑራቸውን አፋፍ ሥር ያደረጉ ነዋሪዎች ጥንቃቄ ያድርጉ " - ኮሚሽኑ

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 በተለምዶ ሰላም ሰፈር አካባቢ 4 ሜትር ከሚገመት ከፍተኛ ቦታ በተከሰተ የአለት ናዳ 3 ሰዎች መሞታቸውን የእሳትና አደጋ ሥራ አመራር ኮሚሽን ገልጿል።

አደጋው የደረሰው ዛሬ ነው።

የኮሚሽኑ የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ባደረጉት ጥረት የ8 ሰዎች ሕይወት ማትረፍ ተችሏል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ፦
- የአደጋው ምንስኤ ምንድን ነው ?
- ይህ አደጋ በከተማዋ ሲከሰት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ?
- ማህበረሰቡ ምን አይነት ጥንቃቄ ማድረግ አለበት? የሚሉ ጥያቄዎችን ለኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ አቅርቧል፡፡

አቶ ንጋቱ ምን ምላሽ ሰጡ ?

“ እንዲህ አይነት አደጋዎች በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች እያጋጠሙ መሆኑ ይታወቃል። የኢትዮጵያ ሜትሮሎጅ ኢንስቲትዩትም የመሬት መንሸራተት፣ ጎርፍ አደጋ ሊያጋጥም ስለሚችል ጥንቃቄ ይደረግ የሚል መረጃ ሲያስተላልፍ ነበር፡፡

ያልተጠበቀ ዝናብ ያጋጥማቸዋል የተባሉ ከተሞችን ሲጠቅስም አዲስ አበባም እዛ ውስጥ ተጠቅሳለች፡፡

በእርጥበት ምክንያት ናዳ፣ የአፈር መደርመስ ሊኖር ስለሚችል በተለይ እንቅስቃሴያቸውንና ኑራቸውን አፋፍ ሥር ያደረጉ ነዋሪዎች ጥንቃቄ ያድርጉ፡፡

ለአደጋ ተጋላጭ የሆኑ አካባቢዎች ላይ መፍትሄ ለመስጠት በሚደረገው ጥረትም የመፍትሄው አካል መሆን ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ ሰዎችን ከቦታው ማንሳት ሊያስፈልግ ይችላል።

አዲስ አበባ ላይ የአለት ናዳ አደጋ አጋጥሞ አያውቅም፣ አላስታውስም፡፡ በእርግጥ ደረጃቸውን ያልጠበቁ፣ የአደጋ ደህንነት መስፈርት ሳይጠብቁ አፋፍ ላይ የተሰሩ ቤቶች ተንደው የሰው ሕይወት ጠፍቶ ያውቃል።

ጠሮ መስጂድ የሚባለው (አዲስ ከተማ ፍለ ከተማ ውስጥ) ሰባት ሰዎች ሕይወታቸው ያለፈበት ሁኔታ ነበር ከኮንስትራክሽን ጥራት ጋር በተያያዘ፡፡

ይሄኛው (የአሁኑ የአለት አደጋ) እዛው መሬቱ ጋር ተያይዞ የበቀለው አለት ከዝናብ ብዛት በመሬት መሸርሸር የሚያጋጥም ነው፡፡

የአለት አደጋውን መስንስኤ ማጣራት የሚጠይቅ ነው ግን ከክረምቱ ወቅት ጋር የሚያያዝ ሊሆን ይችላል ብለን እንገምታለን፡፡ አደጋ የደረሰባቸው መኖሪያ ቤቶቹ ከታች ነው ያሉት፤ አለቱ ደግሞ አፋፍ ላይ ነው ያለው፡፡ በግምት ወደ 4 ሜትር ከፍታ አለው፡፡

ብዙ ጊዜ አፋፍ ላይ ተንጠልጥለው ያሉ ቤቶች ላይ የመውደቅ እድልም አለው፡፡ የሰዎቹም የአኗኗር ሁኔታ፣ የቤቱ አቀማመጥና ደረጃ አስተዋጽኦ አድርጓል። ”


#TikvaEthiopiaFamilyAA

@tikvahethiopia