#Ethiopia

የኢፌዴሪ ገቢዎች ሚኒስቴር በንግድ ማዕከልነት የሚያገለግሉ ሕንፃዎችን በጋራ ገንብተው በባለቤትነት የሚያስተዳድሩ አክሲዮን ማኅበራት ፣ የተጨማሪ እሴት ታክስ እና የዲቪደንድ (የትርፍ ድርሻ) ታክስን ጨምሮ የተለያዩ የግብር ዓይነቶችን እንዲከፍሉ ወስኗል።

በንግድ ማዕከልነት የሚያገለግሉ ሕንፃዎችን ገንብተው በባለቤትነት የሚያስተዳድሩ አክሲዮን ማኅበራት የሕንፃውን ሱቆች በማከራየት ከሚያገኙት ገቢ ላይ ለሚገኙበት ከተማ ወይም የአካባቢ አስተዳደር የኪራይ ገቢ ግብር ብቻ ሲከፍሉ ቆይተዋል።

ሚኒስቴሩ በአክሲዮን ማኅበራት ባለቤትነት ሥር የሚገኙና የሚተዳደሩ የንግድ ማዕከላት ላይ ጥናት ያካሄደ ሲሆን የጥናቱ ግኝትም ፣ አክሲዮን ማኅበራቱ በሕግ የተጣለባቸውን ግብር በተገቢው መንገድ እየተወጡ አለመሆናቸው ያረጋገጠ ነው ተብሏል።

ገቢዎች ሚኒስቴር በጥናት የደረሰባቸውን ግኝቶች መሠረት በማድረግ ሊወሰዱ ይገባል ያላቸውን የማስተካከያ ዕርምጃዎች የተመለከተ ምክረ ሐሳብ ለመንግሥት አቅርቦ በቅርቡ ተቀባይነት ማግኘቱ ተጠቁሟል።

በዚህም መሠረት ፥ በአክሲዮን ተደራጅተው የተገነቡና በንግድ ማዕከልነት የሚያገለግሉ ሕንፃዎች ባለቤት አክሲዮን ማኅበሩ በመሆኑ፣ የንግድ ማዕከሉን የሚመለከቱ የግብር ግዴታዎች ላይ ሙሉ ኃላፊነት መውሰድ እንዳለበት ተወስኗል።

በመሆኑም በንግድ ማዕከልነት በሚያገለግለው ሕንፃ ውስጥ የሚገኙ ሱቆችን በማከራየት የሚገኘው ገቢ ላይ በግብር አዋጁ መሠረት የሚጣለውን የኪራይ ገቢ ግብር እንደ ከዚህ ቀደሙ በከተማ አስተዳደሮች እንደሚሰበሰብ የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።

ይሁን እንጂ ሚኒስቴሩ ባካሄደው ጥናት አክሲዮን ማኅበራቱ በሚያስተዳድሯቸው የንግድ ማዕከላት ውስጥ የሚገኙ የንግድ ሱቆች ኪራይ ተመን ፦
- ከወቅታዊ ገበያው በእጅጉ አነስተኛ መሆኑ፣
- በርከት ያሉ ማኅበራትም በንግድ ማዕከሉ ውስጥ የሚገኙ ሱቆችን በርካሽ ዋጋ ለማኅበሩ አባላት እንዳከራዩ ፣
- ሌሎች በርከት ያሉ አክሲዮን ማኅበራት ደግሞ የባለቤትነት ማስተላለፍ ሥርዓቶችን ሳይከተሉ በንግድ ማዕከሉ ውስጥ የሚገኙ ሱቆችን እንደ አክሲዮን ድርሻ ለማኅበሩ አባላት አከፋፍለው መገኘታቸው ተመላክቷል።

በመሆኑም ፣ ከ2016 ዓ.ም. የግብር መክፈያ ወቅት ጀምሮ በንግድ ማዕከላቱ ውስጥ የሚገኙ ሱቆች የኪራይ ተመን በገበያ ዋጋ ተሰልቶ የኪራይ ገቢ ግብር እንዲከፍሉ መወሰኑን ሪፖርተር ጋዜጣ ከገቢዎች ሚኒስቴር ያገኘውን መረጃ ዋቢ በማድረግ አስነብቧል።

@tikvahethiopia