TIKVAH-ETHIOPIA
#Update ባለፈው ሳይሰጥ የቀረው የመንግሥት ሰራተኞች ፈተና ቅዳሜ ታህሳስ 20/04/2016 ዓ.ም ከጠዋቱ 2:00 ጀምሮ ይሰጣል ተባለ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፐብሊክ ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ባለፈው ለደረሰው መጉላላት እና እንግልት ሁሉ መላው ሰራተኞችን በይፋ ይቅርታ ጠይቋል። የቴክኒክና ባህሪ ብቃት ፈተና፦ - ለአመራሮች ፣ - ለባለሙያዎች - ለሰራተኞች አርብ 12/04/2016…
#AddisAbaba

" ... አስተዳደሩ የብሔር ኮታ ምደባን አስመልክቶ ለከተማዋ ነዋሪዎች በአፋጣኝ ግልጽ ማብራሪያ ይሰጥ " - ኢዜማ

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ፓርቲ ፤ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ሊሰጥ በዝግጅት ላይ ስላለው የመንግሥት ሰራተኞች የብቃት ምዘና ፈተና ጉዳይ ግልጽ ማብራሪያ እንዲሰጥ ጠይቋል።

ፓርቲው ፤ በመርኅ ደረጃ ምዘናው ለማኅበረሰቡ የሚሰጡ አገልግሎቶች በተሻለ ብቃት እና ኢትዮጵያዊ ጨዋነት በተላበሰ ሥነምግባር እንዲሠጡ ታላሚ ያደረገ ከሆነ ለአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ጥራት ያለው ቀልጣፋ አገልግሎት ለማግኘት የሚረዳ መሆኑን ለሠራተኞች ደግሞ ሁልጊዜም ተወዳዳሪ የሚያደርግ አሠራር ስለሚሆን የሚበረታታ ተግባር እንደሆነ ገልጿል።

" በእነዚህ አስተዳደር መ/ቤቶች ፦
- የተገልጋይን ስም እንኳ በቅጡ በሠነዶች ላይ ማስፈር የማይችሉ፣
- ፈጣን አገልግሎት እንዲሠጡ ታስበው አገልግሎት ላይ የዋሉ ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ መጠቀም የማይችሉ፣
- ከሥነምግባር ያፈነገጡ እና በሌብነት የተተበተቡ ሠራተኞችን መመልከት የተለመደ ሆኗል " ያለው ኢዜማ ፤ " ሌላው ቀርቶ አንድ ዜጋ በነፃነት ለመንቀሣቀስ የሚያስፈልገውን የነዋሪነት መታወቂያ ለማግኘት እንኳ ሲጉላላ እና እጅ መንሻ ሲጠየቅ ይስተዋላል። " ብሏል።

ከዚህ አንጻር የአገልግሎት ጥራትን ለማስፈን የምዘና ጅምሩ የሚበረታታ መሆኑን አመልክቷል።

ነገር ግን እነዚህን አስተዳደር መስሪያ ቤቶች የሚመሩት #የገዢው_ፓርቲ አመራሮችም ሆነ ገዢው ፓርቲ እንደተቋም #ለብሄርተኝነት ባላቸው የተዛባ ውግንና በተደጋጋሚ በሚያደርጓቸው አግላይ የአደባባይ ንግግሮች እና አሠራሮች ምክንያት እያንዳንዱ በነዚህ አካላት የሚደረግ እንቅስቃሴና ውሳኔ በማኅበረሰቡ በጥርጣሬ የሚታይ እንዲሆን አድርጎታል ብሏል።

በመሆኑም አስተዳደሩ " የብቃት ደረጃን ለማረጋገጥ እና አገልግሎትን ለማሻሻል የሚደረጉ እርምጃዎች ናቸው " ቢልም ከላይ በተጠቀሰው ምክንያት በጥርጣሬ እንዲታዩ መሆናቸውን መገንዘብና ተገቢውን ማብራሪያ በወቅቱ መስጠት ዜጎችን ከስጋትና ከውዥንብር ያድናል ሲል አሳውቋል።

ከዚህ ጋር ተያይዞ በአንድ መ/ቤት የሚገኙ ዳይሬክተሮች እና የቡድን መሪዎች ከአንድ ብሔር ከ 40 % በላይ ሊበልጡ እንደማይገባ መገለጹ አገልግሎት የሚሰጡ መሥሪያ ቤቶች ውሰጥ ለምዘና ሊቀመጥ የሚገባውን ዋነኛውና መሠረታዊ የሆነውን ከትምህርት ዝግጅት እና ከሥራ ልምድ የሚመነጩ የችሎታና የብቃት ጉዳይ አሳንሶ እንዳይመለከት ጥብቅ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ፓርቲው አሳስቧል።

ፓርቲው ፤ የከተማ መሥተዳደሩ ስለፈተናው እና ለማኅበረሰቡ ጥራት ያለው አገልግሎት ከመስጠት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም ስላለው #የብሔር ኮታ ምደባን አስመልክቶ ለነዋሪዎች በአፋጣኝ ግልጽ ማብራሪያ እንዲሰጥ ጠይቋል።

ኢዜማ በኃላፊነት ቦታዎች ላይ ለሚደረጉ ምደባዎች በምንም ዓይነት መንገድ የብሔር ማንነትን መሠረት ያደረገ መድልኦ የሚደረግባቸው እንዳይሆኑ፤ አሠራሩም ለሁሉም ዜጎች ግልፅና ችግር በሚፈጥሩ አመራሮች ላይ የማያወላዳ ተጠያቂነት ማስፈን የሚችል እንዲሆን ማድረግ ይገባል ብሏል።

(ፓርቲው የላከው ሙሉ መግለጫ ከላይ ተያይዟል)

@tikvahethiopia