#AfricanDevelopmentBank

የአፍሪካ ልማት ባንክ ዓለም አቀፍ ሰራተኞቹን በአስቸኳይ #ከኢትዮጵያ ሊያስወጣ ነው።

ባንኩ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ከአንድ ወር በፊት ዋና የኢትዮጵያ ተወካዩ እና ሌላ የባንኩ ሰራተኛ ላይ በፀጥታ አካላት ድብደባ መፈፀሙን ተከትሎ ነው።

በወቅቱ ባንኩ ቅሬታውን ለመንግስት አቅርቦ የነበረ ሲሆን መንግስትም አስቸኳይ ማጣራት አድርጎ ውጤቱን ይፋ እንደሚያደርግ ገልፆ ነበር።

አሁን ባንኩ ዓለም አቀፍ ሰራተኞቹን " በአስቸኳይ " ከኢትዮጵያ እንዲወጡ ሊያደርግ የወሰነው ድብደባውን ፈፅመዋል በተባሉት የፀጥታ አካላት ዙርያ ስለተደረገው ምርመራ የኢትዮጵያ መንግስት ለባንኩ መረጃ ባለማጋራቱ እንዲሁም በሰራተኞቹ ዘንድ በደህንነታቸው ዙርያ ሙሉ እምነት ሊያገኝ ባለመቻሉ እንደሆነ የባንኩ ፕሬዝደንት ዶ/ር አኪንዉሚ አዴሲና አሳውቀዋል።

ምንም እንኳን ባንኩ ዓለም አቀፍ ሰራተኞቹን ከኢትዮጵያ በአስቸኳይ ለማስወጣት ውሳኔ ላይ ቢደርስም በኢትዮጵያ ያለው ቢሮው ክፍት ሆኖ እንደሚቆይና ውሳኔው ከኢትዮጵያ የተቀጠሩ ሰራተኞችን እንደማይመለከት ገልጿል።

እነዚህ ከኢትዮጵያ የተቀጠሩ ሰራተኞች በስራ ገበታቸው እንደሚቀጥሉና በባንኩ ሙሉ የስራ ስምሪት ውስጥ / የባንኩ ሰራተኞች ሆነው እንደሚቆዩ ማረጋገጫ ተሰጥቷል።

አንድ ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉ የባንኩ የኢትዮጵያ ቢሮ ሰራተኛ ከኢትዮጵያ ባስቸኳይ እንዲወጡ የሚደረጉት ዓለም አቀፍ ሰራተኖች ወደ ደቡብ አፍሪካ እና ኬንያ ሊዛወሩ እንደሚችሉ ጠቁመዋል።

እንደ ሬውተርስ ዘገባ የአፍሪካ ልማት ባንክ ኢትዮጵያ ውስጥ የ308 ሚልዮን ዶላር ዋጋ ያላቸው ስምንት ፕሮጀክቶች አሉት።

Credit - Journalist Elias Meseret

@tikvahethiopia