TIKVAH-ETHIOPIA
" እኔ እድሜዬን በሙሉ እንዲህ አይነት ድርቅ አይቼ አላውቅም " በትግራይ ክልል፤ የኢሮብና አፅቢ ወረዳ ነዋሪዎች አስከፊ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ቃላቸውን ለድምፂ ወያነ ቴሌቪዥን የሰጡ ነዋሪዎች ምን አሉ ? አንድ አባት ፦ " ክረምት አልነበረም ማለት ይቻላል። በጣም ጥቂት ዝናብ ነው የዘነበው። እንኳን እህል የእንስሳት መኖ አልሰበሰብንም። አካባቢያችን ለከፍተኛ ችግር ተጋልጧል። በድርቁ…
#ትግራይ

በትግራይ ያለው ድርቅ . . .

" ከ1977 የባሰ ጊዜ መጣብን፤ ...መሬት እህል አላበቅል አለ  "

እናት #1፦ " ችግር በዛብኝ ፤ እራሴም እየዞረብኝ ነው። እግሬንም ማንቀሳቀስ አቅቶኛል። ልቤም እየደከመብኝ ነው። በረሃብ በችግር ምክንያት ነው እንዲህ የሆንኩት። "

እናት #2 ፦ " የዘራነው እህል ዝናብ ባለመኖሩ አሯል። በዚህ ምክንያት ተርበናል። እህቴም ሁለት ልጆቿን የምታበላቸው አጥታ ቆሎ ስታገኝ የእናት ነገር ሆኖባት ለራሷ ሳትበላ ለእነሱ እያካፈለች በረሃብ በቤቷ ደርቃ ነው የተገኘችው። እኔም አሁን የምበላው የለኝም ረሃብ ሲበረታብኝ ወደ ጎረቤት ሄጄ ቡናም ካገኘው እሱን ጠጥቼ ውላለሁ። "

እናት #3 ፦  " የ2 ዓመት ከ4 ወር መንታ ልጆችን ይዤ በረሃብ ተሰቃይቼ ነው ያለሁት። ለራሴ ተሰቃይቼ ልጆቹንም አሰቃየዋቸው። የምበላው አጥቼ ፆሜን ነው ተደፍቼ የማድረው። ለምኜ እንዳልበላ ልመናው የለም። ልጆቼ ጡቴን ሲጠቡኝ ልቤን ያንሰለስለኝና ያመኛል። ለሊቱን ሙሉ ሳቃስት ነው የማድረው። "

እናት #4 ፦ " ልጄ 8 አመቱ ነው ዘንድሮ ሁለተኛ ክፍል ጨርሶ ወደ 3ኛ ክፍል ያልፍ ነበር አሁን ግን ባጋጠመን ድርቅ ተቸግረን ትምህርቱን መማር አልቻለም። በጣም ተርበናል። ልጆቻንን ካገኙ ይበላሉ ካልሆነም ውሃ ጠጥተው ይውላሉ። በረሃብ ተሰቃየን። "

ድርቅ ባመጣው ረሃብ  ምክንያት ተማሪዎችም ከትምህርት ገበታቸው ቀርተዋል።

ተማሪዎች ደብተርና እስክሪብቶ የሚገዛላቸው ስላጡ ወደ ትምህርት ቤት መሄድ አቁመዋል።

ወላጆች አይደለም ለእነሱ የትምህርት ቁሳቁስ ለማሟላትና ሊያስተምሯቸው ለሆዳቸውም መሆን አቅቷቸዋል። ከባድ ችግር ላይ ናቸው።

በድርቅ የተጠቁ ወገኖች ለረሃብ ማስታገሻ ከመሬት ስር እና ከእፀዋት ፍራፍሬ በመልቀም ህይወታቸውን ለማቆየት ሲጥሩም ተስተውሏል።

እናት ፦ " ልጆችን የማበላቸው አጥቼ ጨንቆኝ ለለቀማ ኑ እንሂድ ብያቸው በረሃብ ምክንያት ከትምህርት ቀርተዋል። ትንፋሻችንን ለማቆየት ኩዕንቲ እየለቀም ነው የምንበላው። መሬት እህል አላበቅል አለ፤ እንኳን እህል ኩዕንቲ አላበቅል አለ። ከ1977 የባሰ ጊዜ መጣብን፤ በረሃብ ምክንያት ልጆቼ ቤት ውስጥ ታጥፈው እየዋሉ ነው። "

እናት ፦ " ይህ መሬት ጤፍ ያበቅል ነበር አሁን ግን ጊዜ ከዳን "

እናት ፦ " ጠኔና ረሃብ ካጋጠመን በኃላ ከፍተኛ ችግር ላይ ነው ያለነው። ኩዕንቲ እንኳን የሚለቅመው አይኑ በደንብ የሚያይ ነው። ይህን ለመብላትም ጥርስ ያስፈልጋል። "

ድርቁ ሰው ላይ እያደረሰ ካለው ጉዳት በተጨማሪ እንስሳት የሚበሉትን አጥተው እየሞቱ ነው።

በትግራይ ውስጥ የነበረው ደም አፋሳሽ አስከፊ ጦርነት ፣ በክረምቱ ዝናብ አለመኖር፣ ወቅቱን ያልጠበቀው ዝናብ፣ እንዲሁም የአንበጣ መንጋ ተዳምሮ ህዝቡን የከፋ ችግር ላይ ጥሎታል።

እንደ ክልሉ አስተዳደር መረጃ ከሆነ 2 ሚሊዮን ሰው ለረሃብ ተጋልጧል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ የነዋሪዎችን ቃል ያዳመጠው ከክልሉ ቴሌቪዥን ጣቢያ ነው።

@tikvahethiopia