TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
አቶ ታዬ ከሰሞኑን ምን ሲሉ ነበር ?

ዛሬ ታህሳስ 1/2016 ዓ/ም የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ፊርማ ባረፈበት ደብዳቤ ከሰላም ሚኒስትር ዴኤታነት መነሳታቸው የተገለፀላቸው አቶ ታዬ ደንደአ ከሰሞኑን አነጋጋሪ ቃለ ምልልሶችን ሲሰጡ ነበር።

ለአብነት ፦

▪️የቲክቫህ - ኢትዮጵያ የቤተሰብ አባልን ጨምሮ ፤ ለተለያዩ ብዙሃን መገናኛዎች በአዳማ በነበረ አንድ ፕሮግራም በሰጡት ቃለ ምልልስ ተከታዮቹን ብለው ነበር ፦

* እንደ ሰላም ሚኒስቴር የሚገባንን ሁሉ #ሥልጣን ተሰጥቶናል ብለን አናምንም። በሀገሪቱ የሰላም ችግር ሲፈጠር፣ #ሰው ሲፈናቀል ያንን የማስቆም ስልጣን ለእኛ አልተሰጠንም። ይሄ #የአወቃቀር ችግር ነው።

* የአደጋ ሥጋት እንኳን #ለእኛ አይደለም ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስቴር ፅሕፈት ቤት ነው። #ፓሊስ ለእኛ ተጠሪ አይደለም። መሆን የነበረበት እዚህ ነው። #የግጭት ሥጋት ሲኖር የምናዘው አንድም #ሚሊሻ የለንም። ስለዚህም ለሚፈጠሩ ግጭቶች የሰላም ሚኒስቴር #ሊወቀስ_አይገባም።

* የስልጣን ፣ የኢኮኖሚ ፣ የፍትህ ችግሮች አሉብን። ሥልጣን ካልተገደበ፣ ተጠያቂነት ካልተረጋገጠ፣ ኢኮኖሚው በፍትሃዊነት ካልተሰራጨና ሌቦች ከተቆጣጠሩት …በፍፁም ሰላም ሊመጣ አይችልም።

* ተጠያቂነትን መስፈን አለበት። ከተጠያቂነት አኳያ ደግሞ ሥልጣን የተሰጣቸው አሉ። ለምሳሌ የፍትህ ሚኒስቴሩ ሥራው ተጠያቂነትን ከማስፈን አኳያ መሆን ነበረበት #ድርድር ከመሄድ ይልቅ።

* በኦሮሚያ ክልል #ለ5_ዓመታት ጦርነት እየተካሄደ በአማራ፣ በኦሮሚያ ክልል የሚስተዋለው ችግር አለ። የትግራይ ክልሉም በጣም ይጸጽተናል። ግን ይህንን የሚያደርገው ከጀርባ ያለው ማነው ? እሱን ነው ማወቅ የሚያስፈልገው።

* መከላከያ ሰራዊት ወንድሞቹን መግደል የለበትም ፤ ወንድሞቹም መከላከያን መግደል የለባቸውም።

▪️ከቀናት በፊት ከ " ቢቢሲ አፋን ኦሮሞ " ክፍል ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ደግሞ ተከታዮቹን ብለው ነበር ፦

- በአሁኑ ወቅት በመንግስት ወስጥ ሙስና እና ብልሹ አሰራር በከፍተኛ ሁኔታ የተንሰራፋ ነው።

- ድሮ መሬት ይዘረፋል ከሚባለው በላይ አሁን ሕጋዊ ሆኖ በቃላት መግለጽ በሚከብድ መልክ እየተንሰራፋ የአስተዳደር ቀውስ ተፈጥሯል።

- የኑሮ ውድነት ሰማይ ደርሶ የመንግሥት ሠራተኛ ቤት ኪራይ መክፈል አቅቶት ከዚህ ቀደም ዘመዶቹን ይረዳ የነበረው ሠራተኛ አሁን በቤተሰቦቹ ይደጎማል።

- በኦሮሚያ ያለው ሕዝባችን ባለፉት 5 ዓመታት ይሞት ነበር። ስንት እንደሞተም በቁጥር አይታወቅም። በጋዛ ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በእስራኤል ስንት አንደሞተ፣ ከፍልስጤም ስንት አንደሞተ በቁጥር ይታወቃል። በኦሮምያ ያለው እልቂት ግን የሚታወቅ ነገር የለም።

- ስንት የደሃ ሰው ቤት ተቃጠለ፣ ስንት ሰላማዊ ዜጋ ሞተ፣ ምን ያህል ንብረት ተዘረፈ፣ ስንት ሰው አካሉ ጎደለ፣ የሚለውን የሚያውቀው ሰው የለም።

- በኦሮሚያ ከየትኛውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ ነው ያለው ፤ ከዚህ በፊት ሆኖ በማያውቅ መልኩ ነው አሁን እየሆነ ያለው።

-  በመንግሥት እና በኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት መካከል የነበረው የሰላም ድርድር እንዲደናቀፍ ያደረገው እኔ ያለሁበት መንግሥት ነው።

- #እኔ_ያለሁበት_መንግሥት ‘ ችግር ውስጥ ነን ፤ ተወያይተን መፍትሄ እናመጣለን ’ ብዬ ስጠይቅ ቤቱ ለውይይት ክፍት አይደለም በማምታታትና በማደናገር ማለፍ ነው የሚፈለገው፤ የእኔ መንግሥት እንዲህ ዓይነት ጸባይ ነው ያለው።

- የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊትን (OLA) የሚመራው ጃል መሮ ፣ መንግሥት ከፈለገ ይግደለኝ ብሎ ፣ መንግሥት በሚቆጣጠረው የአየር ክልል አልፎ፣ ወደ ታንዛኒያ በአውሮፕላን መሄዱ ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት ነው የሚያሳየው ብዬ አምናለሁ።

- በታንዛኒያ ፣ የዳሬሰላሙ የሰላም ድርድር ተጀምሮ በ2ኛው ቀን ፣ ከመንግሥት ወገን ፕሮፓጋንዳ መንዛት ነው የተጀመረው " ሸኔን አጥፍተናል፣ አከርካሪውን ሰብረናል " የሚል ፕሮፓጋንዳ ተጀመረ። ፕሮፓጋንዳ ብቻ ሳይሆን ጦር ከያለበት ተንቀሳቅሶ በ5 ዓመት ውስጥ ያላለቀው ጦርነት በድርድሩ ጊዜ ለመጨረስ፣ እንቅስቃሴ ተደርጓል። ይህ ከመንግሥት ወገን ለሰላም ፍላጎት አለመኖሩን ያሳያል።

▪️የሰላም ሚኒስቴር የ2016 ዓ.ም. የ3 ወራት እቅድ አፈፃፀሙን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለውጭና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ካቀረበ በኃላ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት ቃለምልልስ ይህንን ብለዋል ፦

° በአማራ ክልል ጉዳይ ፤ የተ / ም / ቤት ጭምር ሄዶ ህዝብ ባነገረትበ ጊዜ እንደዚህ አይነት አዝማሚያዎች መኖራቸው ቀድም ብሎ ተለይቶ ነበር፤ ግን ችግሮችን ከመፍታትና አፋጣኝ የሆነ ምላሽ ከመስጠት አኳያ በሚመለከታቸው አካላት የፍጥነትና የቅንጅት ችግር ስለሚታይ እዚህ ደረጃ ደርሷል። እኛ ፖሊስ / ፀጥታ ኃይል #የማዘዝ_ስልጣን አልተሰጠንም።

° መንግሥት ከሕወሓት ጋር የፈታውም እና ከኦነግ ሸኔ ጋር የዘለቀበትን ግጭት ለመፍታት እያደረገ ያለውን ጥረት ጥሩ ነው። በአማራ ክልል ያለውም በዚያው መንገድ ሊታይ የሚችል ነው።

ዛሬ ከስልጣን እንደተነሱ የተነገረው አቶ ታዬ ደንደአ ፤
- የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት (ጨፌ) አባል፤
- አገሪቷን በሚያስተዳድረው የብልጽግና ፓርቲ ውስጥ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ናቸው።

@tikvahethiopia