TIKVAH-ETHIOPIA
Photo
#Amhara

ለአንድ ቀን ይቆያል የተባለው የአማራ ክልል ምክር ቤት አስቸኳይ ጉባኤ በባሕር ዳር እየተካሄደ ይገኛል።

ጉባኤው በክልሉ ወቅታዊ የጸጥታ ችግሮች ዙሪያ እየመከረ ነው ተብሏል።

የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ኅላፊና የኮማንድፖስቱ አባል አቶ ደሳለኝ ጣሰው ለምክር ቤቱ ንግግር አሰምተዋል።

በዚህም ንግግራቸው ፤ በክልሉ የተፈጠረው ወቅታዊ ግጭት " ድህረ ጦርነት የፈጠረው ልዩነት ነው " ብለዋል።

አቶ ደሳለኝ ችግሩን በሰላም ለመፍታት ጥረት ተደርጎ ነበር ያሉ ሲሆን " ካለፈው ጥር ወር መጨረሻ ጀምሮ እየተስተዋለ የመጣውን የክልሉን የሰላምና ጸጥታ ችግር በክልሉ አቅም ለመፍታት የታየው ዳተኝነት እና የአመራሩ የተዛነፈ እይታ ችግሩ ውሎ ሲያድር አቅም እንዲያገኝ እና ከክልሉ መንግሥት አቅም ውጭ እንዲሆን አድርጎታል " ብለዋል።

ግጭቱ ፦
- በክልሉ ውስጥ እየተስተዋለ የመጣው ዋልታረገጥ ልዩነት፣
- #የሕዝብ_ጥያቄዎች_አለመመለሳቸው_የፈጠረው_ብሶት፣
-  የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት የፈጠረው የሥነ-ልቦና አለመረጋጋት የፈጠሩት ችግር እንደሆነ አቶ ደሳለኝ ለምክር ቤቱ ተናግረዋል።

የሃሰት ፕሮፖጋንዳ የሚያመርቱ የብዙሃን መገናኛ ተቋማት አቀጣጣይ ነበሩም ብለዋል።

ኮማንድፖስቱ ከታወጀ ማግስት ጀምሮ በክልሉ በርካታ አካባቢዎች ሰላም ታይቷል ያሉ ሲሆን አሁንም ቀሪ ሥራዎች በመኖራቸው የኦፕሬሽን ሥራዎች እየተሠሩ ነው ብለዋል።

አቶ ደሳለኝ ፤ በግጭቱ ተሳታፊ የሆኑ ኃይሎች የግጭት አማራጭን በመተው ለሰላማዊ ትግል እራሳቸውን ማዘጋጀት እንዳለባቸው ተናግረዋል።

" የሰላም አማራጮች አሁንም በሮቻቸው ዝግ አይደሉም " ያሉት አቶ ደሳለኝ " የሚፈለገው የሰላም አማራጭ ከተገፋ ግን ሕግን የማስከበር ሥራው ተጠናክሮ ይቀጥላል " ሲሉ ተደምጠዋል። #AMC

@tikvahethiopia