#Update

የትምህርት ሚኒስቴር በትግራይ ክልል በጦርነቱ ምክንያት ሥራ አቁመው የነበሩ ዩኒቨርሲቲዎች ከአክሱም ዩኒቨርሲቲ በስተቀር ከአንድ ወር በኃላ ነባር ተማሪዎቻቸውን እንደሚቀበሉ ከመስከረም (2016) ጀምሮ ደግሞ #ሙሉ_ለሙሉ ሥራ እንደሚጀምሩ አስታውቋል።

የሚኒስቴሩ የአስተዳደርና ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ሰለሞን አብርሀ (ዶ/ር) ለኢፕድ የሰጡት ቃል ፦

" ከአክሱም ዩኒቨርሲቲ በስተቀር ሦስቱ ዩኒቨርሲቲዎች በመጭው ወር ነባር ተማሪዎችን መቀበል ይጀምራሉ።

በመጪው ዓመት በትግራይ ክልል የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎችን ወደ መደበኛ የመማር ማስተማር ሂደት ለማስገባት ዝግጅት እየተደረገ ነው።

ዩኒቨርሲቲዎቹን ወደ ሥራ ለማስገባት የትምህርት ሚኒስቴር ዩኒቨርሲቲዎቹ ያሉበት ሁኔታ ከዩኒቨርሲቲዎቹ አመራሮች ጋር በመቐለ ተደጋጋሚ ውይይት አድርጓል።

ሥራ ለማስጀመር የሚያስችሉ ሥራዎችን ለመስራት ወደ ተግባር ተገብቷል።

ዩኒቨርሲቲዎቹ የመማር ማስተማር ሂደት ከመጀመራቸው በፊት ፦
- የምግብ ፣
- የመኝታ፣
- የሕክምና አገልግሎቶች ቅድሚያ የሚያሟሉበት ሁኔታ እየተመቻቸ ነው።

ራያ ዩኒቨርሲቲም ይህንን አሟልቶ በትናንትናው ዕለት የተማሪዎች ምዝገባ ጀምሯል።

መቐለና ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ በቀጣይ ወር ትምህርት መጀመር የሚያስችላቸውን ተግባር ጨርሰው ተማሪዎችን መቀበል እንደሚጀምሩ ይጠበቃል።

አክሱም ዩኒቨርሲቲ ከሌሎቹ ዩኒቨርሲቲዎች በበለጠ በጦርነቱ ጉዳት በማስተናገዱ የተወሰነ ጊዜ ሊዘገይ ይችላል።

አራቱ ዩኒቨርሲቲዎች ከጦርነቱ በፊት 45 ሺሕ ተማሪዎችን ሲያስተምሩ ነበር። ከእነዚህ ውስጥም ባለፉት ዓመታት 22 ሺሕ የሚሆኑ ተማሪዎች እንዲወጡ ተደርጎ በጊዜያዊነት ወደ ሌላ ዩኒቨርሲቲ ተመድበው ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ ተደርጓል።

እነዚህ ዩኒቨርሲቲዎችም አሁን ላይ ቅበላ የሚያደርጉት ወደ ሌላ ዩኒቨርሲቲ ሳይመደቡ የቆዩ 20 ሺሕ የሚሆኑ ተማሪዎችን ነው።

በመጪው አገር አቀፍ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ፈተና ወስደው የሚያልፉ ተማሪዎችም የዩኒቨርሲቲዎቹ ዝግጁነት ተጠንቶና ታይቶ ተማሪዎች ሊመደቡባቸው ይችላል።

ከዚህ ቀደም በትግራይ ክልል ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩና ወደ ሌላ ዩኒቨርሲቲ ሄደው ያጠናቀቁ ተማሪዎች ውጤታቸውን የሚገልጽ የትምህርት ማስረጃ ሳያገኙ መቆየታቸውን ይታወሳል ፤ አሁን ላይ ከነበሩበት ዩኒቨርሲቲ ያገኙት ውጤት ወደ ትግራይ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲላክ አቅጣጫ ተቀምጧል።

ዩኒቨርሲቲዎቹም ውጤቱ ሲደርሳቸው የነበራቸውን ውጤት ደምረው ጥቅል ውጤታቸውን የሚገልጽ ጊዜያዊ ዲግሪ ማግኘት ይችላሉ። "

Via EPA

@tikvahethiopia