TIKVAH-ETHIOPIA
#እግድ " የማህበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት ቴሌቪዥን ጣቢያ " በመንግስት #በጊዜያዊነት ታገደ። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዛሬ እሁድ በፃፈው ደብዳቤ " ማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጣቢያ " ን በጊዜያዊነት እንዳገደ አሳውቋል። ባለስልጣን መ/ቤቱ ፤ ማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጣቢያ ዛሬ በግንቦት 13 ቀን 2015 ዓ.ም " ሰበር ዜና " በሚል ባሰራጨው መግለጫ ከሐይማኖት መገናኛ ብዙኃን…
#ኢዜማ

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ በላከው መግለጫ ፤ የመገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን በማህበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ላይ ያሳለፈው የእግድ ውሳኔ ህጋዊ ግዴታውን የጣሰ ነው ሲል ገልጿል።

ኢዜማ ፤ " የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን ከተልዕኳቸው ውጪ የገዢው ፓርቲ ልሳን ሆነው የህዝብን በደል እና የመንግሥትን ብልሹ አሰራር ጆሯቸውን ደፍነው ዘወትር የውዳሴ ዘገባ ለገዢው ፓርቲ እና መንግሥት በማቅረብ ለተጠመዱት የህዝብ መገናኛ ብዙኋን ምንም አይነት #ተግሳጽ እንኳ ሳያቀርብ ባለፈው እሁድ ግንቦት 13/2015 ዓ.ም ለማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት በፃፈው የእግድ ደብዳቤ ብሮድካስት ባለፍቃዱን በጊዜያዊነት ማገዱን ገልጿል " ብሏል።

" ይህ የእግድ ውሳኔ ምክንያቱ ሕጋዊ ሆነም አልሆነ በመገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣኑ በአዋጅ ቁጥር 1238/2021 አንቀጽ 73 ፣ 76 እና 81(2) የተጠቀሱትን በቅድሚያ #ማስጠንቀቂያ የመስጠትም ሆነ የሚዲያ ተቋሙ #ራሱን_እንዲከላከል ቀድሞ እድል የመስጠት ሕጋዊ ግዴታውን የጣሰ ነው " ሲል ኢዜማ ገልጿል።

" ተቋማት የሚወስዷቸው እርምጃዎች በእርግጥም ሕግን ከማስከበር መነሻነት ይልቅ በማን አለብኝነት ድርጅታዊ ፍላጎትን ብቻ ታሳቢ ያደረገ ነው " ያለው ኢዜማ የመገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን በማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት ላይ የወሰደው እርምጃ ይህን በግልፅ ያስረዳል ብሏል።

ተቋማት ከእንደዚህ አይነት ወጥነትና ገለልተኝነት የጎደለው ተግባር በአስቸኳይ እንዲወጡም አሳስቧል።

ፓርቲው ፦

- የመገናኛ ብዙኀንን ጨምሮ ገለልተኛ ሊሆኑ የሚገባቸው ተቋማት ከገዢው ፓርቲ አባላት ተጽዕኖ ነፃ ማውጣት፤

- የመንግሥት እና የፓርቲ አሠራር የተለያዩ መሆናቸውን በሕግም በተግባርም ማረጋገጥ፤

- የሚወሰዱ እርምጃዎች ሕግ እና ሕግ ላይ ብቻ መሠረት ያደረጉ ብቻ ሊሆኑ ይገባል ብሏል።

ኢዜማ ፤ የመገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን የወሰደው እርምጃ " በአዋጅ ከተሰጠው ሥልጣን ወሰን ተላልፎ የወሰደው " ነው ያለ ሲሆን ፓርቲው ሕገ ወጥ ነው ያለው ውሳኔ እንዲሽር፤ ባለስልጣኑ ይህን ውሳኔ ያሳለፉትን አካላት ተጠያቂ በማድረግ ለሕዝብ እንዲያሳውቅ ጥሪ አቅርቧል።

(ሙሉ መግለጫው ከላይ ተያይዟል)

@tikvahethiopia