TIKVAH-ETHIOPIA
የቤት ማፍረስ ዘመቻው ... በአዲስ አበባ ዙርያ " ሸገር ከተማ " እየተካሄደ ያለውን የቤት ማፍረስ ዘመቻን በተመለከተ ኢሰመኮ የደረሰበትን የክትትል ውጤት በላከልን መግለጫ አሳውቋል። በመግለጫው፤ በኦሮሚያ ክልል በሸገር ከተማ እየተካሄደ ያለው ቤቶችን የማፍረስ እና በግዳጅ ማስነሳት እርምጃ የመኖሪያ ቤት አልባነትን አባብሷል ብሏል። ሕገ ወጥ የሆነ ግንባታን የማፍረስ እርምጃ ሕጋዊ ሂደትን መከተልና…
ከኢሰመኮ መግለጫ...

በሸገር ከተማ እየተካሄደ ካለው የቤት ማፍረስ እና በግዳጅ ማስነሳት ዘመቻ ጋር በተያያዘ ኢሰመኮ እርምጃው ተገቢ ልየታ ያልተደረገበት መሆኑን ገልጿል።

የቤት ፈረሳውና በግዳጅ ማንሳቱ የሚመለከተው የከተማውን መሪ ዕቅድ በሚጥሱ እና የመንግሥት ይዞታን በመውረርና ከአርሶ አደሩ ጋር በተደረገ ሕገወጥ የመሬት ግብይት የተገኙ ይዞታዎች ላይ የተደረጉ ግንባታዎችን ነው ቢባልም #ሁሉም ቤቶች ግን በተመሳሳይ ሥሪት ላይ የተመሠረቱ ባለመሆናቸው የሚገዛቸውም ሕጎች እና አሠራሮች በዚያው ልክ የተለያዩ ሊሆኑ ይገባ ነበር ብሏል።

ኮሚሽኑ ባደረገው ክትትልና ምርመራ እየፈረሱ ያሉ ቤቶች በተለያየ አይነት ክፍል የሚመደቡ መሆኑን ገልጿል

👉 የመጀመሪያው ክፍል ፦

ከ2005 ዓ.ም. በፊት የተገነቡ ቤቶች ሲሆኑ እነዚህን ቤቶች በተመለከተ በሀገሪቱ የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ በወጣው አዋጅ ቁጥር 721/2004 አንቀጽ 6(4) እና (5) እንደተደነገገው አዋጁ ከመውጣቱ በፊት በኢመደበኛ መልኩ የተገነቡ ቤቶች የከተሞችን ፕላን እና የሽንሻኖ ስታንዳርድ ሲያሟሉ ወደ መደበኛ ስሪት እንደሚዞሩ ደንግጓል። ነገር ግን ኮሚሽኑ ባደረገው ማጣራት እነዚህን ቤቶች ሕጉ በደነገገው መሠረት በወቅቱ ወደ መደበኛ ሥሪት እንዲዘዋወሩ የሚያስችላቸውን መስፈርቶች ማሟላታቸውን በማረጋገጥ የማዘዋወር ሥራ ሳይሠራ እንዲሁ #እንዲፈርሱ ተደርጓል።

👉 ሁለተኛው ክፍል ፦

በግዢ የተገኙ ቤቶች ሲሆኑ ከእነዚህ ቤቶች ውስጥ መደበኛ ካርታ፣ የአየር ላይ ካርታ እና አረንጓዴ ደብተር ያላቸው እንዲሁም እንዳይፈርሱ የፍርድ ቤት እግድ ያለባቸው ቤቶች ከከተማ ፕላን ጋር የማይሄዱ ናቸው ከተባለ፤ በሕግ አግባብ በተደነገገው መሠረት ተለዋጭ የቤት መሥሪያ ቦታ እና ተገቢው ካሳ ተከፍሏቸው መነሳት የሚገባቸው ነበሩ። ቤቶቹ በገጠር መሬት ላይ የተሠሩ ናቸው የሚባል ቢሆን እንኳ በኦሮሚያ የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 130/1999 አንቀጽ 6(8) መሠረት በቂ ጊዜ ተሰጥቶ ንብረቶቻቸውን እንዲያነሱ ይደረጋል እንጂ በድንገት ማፍረስ አይገባም ነበር።

👉 ሦስተኛው እና አራተኛው ክፍል ፦

ከአርሶ አደሮች ጋር በተደረገ ሕገ ወጥ የመሬት ሽያጭ በተገኘ ቦታ ላይ የተሠሩ ቤቶች እና ከ2005 ዓ.ም. በኋላ ያለሕጋዊ ፈቃድ በመንግሥት ይዞታዎች ላይ የተገነቡ ቤቶች ናቸው።

ስለሆነም እንዲፈርሱ የተደረጉት ቤቶች በተለያየ አይነት ሥሪት ላይ የተመሠረቱ ስለሆነ እንደየነገሩ ሁኔታ ተገቢው መለየት እና ማጣራት እየተደረገ ሊፈጸም ይገባው ነበር፡፡

ሕገወጥ ግንባታ ማፍረስና የመንግሥት ይዞታ የሆነን ቦታ መልሶ መውሰድ ሕጋዊ እርምጃ ቢሆንም እንኳን፣ የመኖሪያ ቤት ማፍረስና በግዳጅ ማስነሳት ዜጎችን መኖሪያ ቤት አልባ በሚያደርግ መልኩ መደረግ እንደሌለበት እና በሕግ የተፈቀደ እና ለቅቡል አላማ የተደረገ መሆኑ ብቻ በቂ ምክንያት ሊሆን እንደማይችል ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ሕግ ይደነግጋል።

ዜጎች የመኖሪያ ቤት መብት እንዳላቸው ኢትዮጵያ ያጻደቀችው ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ባህላዊ መብቶች ቃልኪዳን በአንቀጽ 11 የደነገገ ሲሆን ኢመደበኛ በሆነ መንገድ እንኳን የተገኙ የመኖሪያ ቤቶችን በሚመለከት መኖሪያ ቤት አልባነትን ለመከላከል ሲባል ሕጋዊ የይዞታ ዋስትና ሊሰጣቸው ወይም አማራጭ መፍትሔ ሊመቻች እንደሚገባ የኢኮኖሚያዊ፣ ማኀበራዊ እና ባህላዊ መብቶች ኮሚቴ በግዳጅ ማንሳትን በተመለከተ ባወጣው አጠቃላይ አስተያየት ቁጥር 7 ላይ አስቀምጧል፡፡

ሙሉ መግለጫ ፦ https://publielectoral.lat/s/tikvahethiopia/77467?single

ፎቶ፦ Tikvah Family

@tikvahethiopia