ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ምንድነው ያሉት ?

#ብፁዕ_ወቅዱስ_አቡነ_ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት አንድ ተቀማጭነቱን ውጭ ሀገር ላደረገ የቴሌቪዥን ጣቢያ ከሰሞኑን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተፈፀመውን የሰው ልጆችን በእሳት የማቃጠል ድርጊት " አረመኔያዊ " ሲሉ በማውገዝ የተሰማቸውን ከባድ ሀዘን ገልፀዋል።

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በዚህ ንግግራቸው ድርጊቱ " አለምን ያሳዘነ ፤ የአረመኔነት ድርጊት ነው " ሲሉ ገልፀዋል።

ብፁዕነታቸው " ባለፈው 2013 ዓ/ም ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ያላየነው ያልሰማነው " የለም ያሉ ሲሆን " በትግራይ ህዝብ ላይ የደረሰው መከራ እጅግ የሚያሳዝን እጅግ የሚያስለቅስ ነው፤ መፈጠረን ሁሉ የሚያስጠላ ድርጊት ተፈፅሟል " ብለዋል።

ነገር ግን የአሁኑ ድርጊት ከሁሉ የባሰ ነው ብለውታል።

ከሰሞኑን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከተፈፀመው ድርጊት በተጨማሪ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ከዚህ ቀደም በትግራይ ክልል ተፈፅሟል ያሏቸውን የጭካኔ ተግባራት ዘርዝረዋል።

" በትግራይ ክሊኒኮች፣ ሆስፒታሎች ፣ ት/ቤቶች ፣ መድሃኒት ቤቶች ፋብሪካዎች በጠቅላላ ወድመዋል፣ የቀረ ነገር የለም አሁን ደግሞ እንደገና ህፃናት በእናቶች እቅፍ ሆነው፣ ምግብ አጥተው እያለቀሱ እንደቅጠል ደርቀው በምግብ እጦት በእናቶቻቸው እቅፍ ሲሞቱ ፤ እናቶቻቸው እያለቀሱ ጡት እንዳያጠቧቸው እነሱም እራሳቸው በረሃብ ስለደረቁ ወተት የለም እንደዚህ ያለውን ሁኔታ እያየን ነው " ብለዋል።

ብፁዕነታቸው እከዛሬ የሆነው ሆኗል ፣ የጠፋው ጠፍቷል፣ የሞተው ሞቷል፣ ያለቀው አልቋል፤ አሁን ግን ቢበቃ ሲሉ ተደምጠዋል።

" ሀዘናቸው እጅግ ከባድ " መሆኑን የገለፁት ብፁዕነታቸው " ይሄ የሁሉም የኢትዮጵያዊያን በተለይም የትግራይ ህዝብ ሀዘን ነው እና መከራው ግን በሁሉም ደርሷል ቀስ እያለ እየተስፋፋ በመላ ኢትዮጵያ ደርሷልና በቃው ከእንግዲህ ወዲህ ምናለ ለተረፈው ህዝብ ይቅርታ ቢደረግለት ወይም ደግሞ ቢያሳዝነን ለምን እንዲህ አይነት ችግር ይፈጠራል ፤ ይብቃ " ሲሉ ተናግረዋል።

ብፁዕነታቸው ፤ በትግራይ ክልል ስላለው ሁኔታ ለመናገር እስካሁን እድል እንዳላገኙ በመግለፅ ፤ ከዚህ በፊት ሾልኮ የወጣውን ቪድዮ ላይ ሁኔታውን ለመግለፅ ከሞከሩበት ውጭ ሌላ እድል አግኝተው እንደማያውቁ አስረድተዋል።

ከዚህ በፊት ሾልኮ በወጣ ቪድዮ ላይ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በትግራይ ያለውን ሁኔታ ከተናገሩ በኃላ በወቅቱ ከፍተኛ መነጋገሪያ ሆኖ እንደነበር አይዘነጋም።

ቅዱስ ፓትርያርኩ መነጋገሪያ ሆኖ በነበረው ቪድዮ ትግራይ ክልል ውስጥ ይሰራል ያሉት አረመኒያዊ ስራ እንዲቆም ያቀረቡት ጥይቄ አለመሳካቱን ፤ ፍቃድም እንዳልተሰጠ ገልፀው ሚናገሩት ሁሉ በተደጋጋሚ እንደሚመለስና ፍቃድ እንዳላገኙ ተናግረው ነበር።

ከዚህ በኃላም የቤክርስትያኒቱ ሲኖዶስ ዋና ፀሀፊው ብጹዕ አቡነ ዮሴፍ ሰጥተው በነበረው መግለጫ ፤ የትኛውም መልዕክት ከመተላለፉ በፊት በሲኖዶስ በሚደረግ ስብሰባ ውሳኔ ሊሰጠው እንደሚገባና አቡነ ማትያስ ያስተላለፉት የግል አቋም እንጂ የሲኖዶሱ ውሳኔ እንዳልሆነ አሳውቀው ነበር።

የቅዱስ ፓትርያርኩ ፤ የሰሞኑ ንግግር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሚወክል ስለመሆን ፤ አለመሆኑ ቅዱስ ፓትርያርኩ በግልፅ አልተናገሩም ፤ አልያም ከዚህ ቀደም እንደነበረው በሲኖዶስ በኩል የተገለፀ ነገር እስካሁን የለም።

ቅዱስ ፓትርያርኩ የተናገሩትን ሙሉውን ያንብቡ 👇

https://telegra.ph/Holiness-Abune-Mathias-03-20