#Russia #Poland #Germany

አዲስ አበባ ያለው የሩስያ ኤምባሲ ያሰራጨው መልዕክት መነጋገሪያ ሆኗል፤ በኤምባሲዎች መካከልም ውዝግብ ፈጥሯል።

የሩስያ ኤምባሲ በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገፁ ለሩስያ ድጋፋቸውን የሚገልፁ በየዕለቱ ብዙ ደብዳቤዎች ፣ በመቶዎች የሚቆጠር አስተያየት እንደሚደርሰው ገልጿል።

ይህ መልዕክት እየደረሰው ያለው ከገፁ ተከታዮች መሆኑን አመልክቷል።

ኤምባሲው " ሀገሮቻችን በችግር ጊዜ በመደጋገፍ እና በመረዳዳት እንደዚህ አይነት ጠንካራ ፣ ረጅም ጊዜ የሚቆይ ፣ ወዳጃዊ ግንኙነት ስላላቸው ኩራት ይሰማናል " ብሏል።

አክሎም " ልክ አያቶቻችን ከ80 ዓመታት በፊት እንዳደረጉት ናዚዝምን እየተዋጋን ባለንበት በአሁን ጊዜ ያሳያችሁን ድጋፍ እና ከሩስያ ጎን ለመቆም ስለመረጣችሁ በእጅጉ እናደንቃለን " ብሏል።

የሩስያ ኤምባሲ ይህንን መልዕክት ካሰራጨ በኃላ የሌሎች ሀገራት ኤምባሲዎች ምላሽ ሰጥተዋል ፤ ምላሽ ከሰጡት መካከል የፖለንድ ኤምባሲ አንዱ ነው።

ፖላንድ ኤምባሲ ፤ ሩስያ የሀሰተኛ መረጃ እያሰራጨች ነው ሲል ወቅሷል።

ኤምባሲው " የናዚ መስፋፋት የጀመረው በ1939 በፖላንድ ላይ በተደረገ ሕገ-ወጥ ወረራ ነው ፤ በወቅቱም ሞስኮ እንደ አጋር ነበረች ብሏል።

" ሩስያ በዩክሬን ላይ ከፈፀመችው ህገ-ወጥ የሆነ ጥቃት ጋር በተያያዘ ፤ ማን ከናዚዎች ጋር መነፃፀር እንዳለበት ሁለት ጊዜ ማሰብ ይገባል " ሲል ኤምባሲው ገልጿል።

ሌላው ለሩስያ ኤምባሲ ምላሽ የሰጠው የጀርመን ኤምባሲ ሲሆን ኤምባሲው በጉዳዩ ዙሪያ ዝም ሊል እንደማችል ገልጿል።

" ናዚዝም " ን እንዋጋለን በሚል ሉዓላዊ ሀገርን መውረር ፣ ሰላማዊ ዜጎችን እና ሆስፒታሎችን ማፈንዳት (ልክ ትላንት በማሪፖል በሚገኘው የእናቶች እና ህፃናት ሆስፒታል እንደተደረገው) የሚያሳዝን እና የሀሰተኛ መረጃ ማሳያ ነው ብሏል።

ይህ ጦርነት " ናዚዝም " ን ለመዋጋት እንዳልሆነ ይታወቃል ያለው የጀርመን ኤምባሲ ጦርነቱ ለአምባገነን ስርአቶች ትልቁ ፈተና እና ስጋት የሆነውን ዲሞክራሲን፣ የፕሬስ ነፃነትን እና የህዝብ ድምጽን መዋጋት ነው ብሏል።

ኤምባሲው ፤ " የሩሲያ ታንኮች ሰላም ፣ ውሃ ወይም ምግብ አያመጡም ፤ መከራ እና ጥፋት ብቻ ነው የሚያመጡት " ብሏል።

@tikvahethiopia