#Breaking

በቅርቡ እጣ የወጣባቸው የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለባለ እድለኞች እንዳይተላለፉ በፍርድ ቤት ታገዱ።

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት 8ኛ የፍትሃብሄር ችሎት በቅርቡ እጣ የወጣባቸው የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለባለእድለኞች ስመ ሀብት/ካርታ/ እንዳይተላለፍ አግዷል።

የጋራ መኖሪያ ቤቱን ለማግኘት ተመዝግበው 100 በመቶ የከፈሉ 98 ዜጎች ክስ መመስረታቸውን ተከትሎ ነው ፍርድ ቤቱ በጉዳዩ ላይ የፍርድ ሂደቱ እስከሚጠናቀቅ ድረስ ለባለ እድለኞች እንዳይተላለፉ ያገደው።

ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር የቤቶቹን ዋጋ መቶ በመቶ በመክፈል ቅድሚያ ለማግኘት የገባነው ውል አለ ያሉ 98 ተመዝጋቢዎች ናቸው ክስ የመሰረቱት።

ተመዝጋቢዎቹም የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒቴርን፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቁጠባ ቤቶች ኢንተርፕራይዝን እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ነው የከሰሱት።

በመመሪያው መሰረት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዕጣ አውጥቶ ለእድለኞች ማከፋፈል ሲገባው የከተማ አስተዳደሩ መመሪያን በመጣስ 100 በመቶ የቆጠቡ ተመዝጋቢዎች እያሉ ከ40 በመቶ ጀምሮ የቆጠቡትን በእጣው በማካተት ዕጣውን በማውጣት ከሕግና ከውል ውጪ ቤቶቹ እጣ እንዳወጣባቸው በክሳቸው ላይ ጠቅሰዋል።

ዛሬ ጉዳዩን የተመለከተው ፍርድ ቤቱ አሁን የተጀመረው የፍርድ ሂደት እስኪቋጭ ድረስ የቤቶቹን ካርታ ለባለ እድለኞች እንዳይተላለፍ አግዷል።

በዚህ ጉዳይ ላይ የተከሳሽ ተቋማትን ምላሽ ለመስማት ለግንቦት 29 ቀን 2011 ዓመተ ምህረት ቀጠሮ ሰጥቷል። እንደዚሁም ፍርድ ቤቱ በጉዳዩ ላይ ሰኔ 10 ክርክር ለመጀመር ቀጠሮ ሰጥቷል።

ባለፈው የካቲት 27 ቀን 2011 ዓመተ መህረት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ18 ሺህ 576 የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ላይ እጣ ማውጣቱ ይታወሳል።

Via FBC
@tsegabwolde @tikvahethiopia