ታጣቂዎች ሁለት ሰዎችን ገደሉ‼️

በደቡብ ክልል አማሮ ወረዳ ዛሬ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ሁለት ሰዎች መገደላቸውን የዐይን ዕማኝ እና የወረዳው ባለሥልጣን አስታወቁ። ጥቃቱ የተፈጸመው ወረዳውን ከኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ጉጂ ዞን በሚያዋስነውና #ጎልቤ በተባለ ሥፍራ ላይ ነው።

ጥቃቱን ተከትሎ በአካባቢው የሚገኘው መከላከያ ሠራዊት ወደ ሥፍራው በመንቀሳቀስ #ከበባ ማድረጉ ታውቋዋል፡፡ በሥፍራው የነበሩ የአይን እማኝ እንዳረጋገጡት ሠራዊቱ በሥፍራው ከመድረሱ አስቀድሞ የታጠቁ ቡድኖች ወደ መንደሩ በመግባት በነዋሪዎች ላይ #ተኩስ ከፍተዋል፡፡

አንድ የመንደሩ ነዋሪ "አማሮ ወረዳ ጎልቤ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር ልዩ ስሙ ላፊፋ በተባለ ቦታ ነው ታላቅ ወንድሜ እና የታላቅ ወንድሜ ልጅ ከብት ከሚጠብቁበት ከማሳቸው ገብተው ጨፈጨፏቸው በቀብር ሥርዓት ላይ ነን ያለንው" ሲሉ ለጀርመን ድምፅ ራድዮ ተናግረዋል።

የአማሮ ልዩ ወረዳ አስተዳደር የባህል ፤ ቱሪዝምና የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ #አማረ_አክሊሉ "ዛሬ አራት ሰዓት ገደማ ላይ ነው የጸረ-ሰላም ኃይሎች ሰዎች የገደሉት። ታጣቂዎቹ ወደ አማሮ ወረዳ ጎልቤ ቀበሌ የመጡት ከገላና ወረዳ በኩል ነው" ሲሉ ጥቃቱ መፈጸሙን አረጋግጠዋል። ኃላፊው በሰራዊቱ ክትትል ውስጥ መሆናቸውን የተረዱት ታጣቂዎቹ በገላና ሸለቆ ውስጥ ገብተው #መሰወራቸውንና ሠራዊቱም ወደ ጦር ሰፈሩ መመለሱን ገልጸዋል፡፡ "መከላከያ ሰራዊቱ ሁለት ሰው ከሞተ በኋላ መጥቶ ነበር። መከላከያ ሰራዊቶች መጥተው ክትትል አድርገው አላገኟቸውም። ወደ ኋላ ተመልሰው ወደ ካምፓቸው ተመልሰዋል። ታጣቂዎቹን ሊያገኟቸው አልቻሉም። ጫካ ነው የገቡት" ሲሉ አቶ አማረ ሁኔታውን ለጀርመን ራድዮ ጣቢያ አስረድተዋል።

በአካባቢው በተፈጸመው ጥቃትና በተካሄደው ወታደራዊ እንቅስቃሴ ዙሪያ እስከአሁን ከአገር መከላከያ ሚኔስቴርም ሆነ ከፌደራሉ መንግሥት የተሰጠ #ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ የለም፡፡

በደቡብ ክልል አማሮ ወረዳ ካለፈው የሰኔ ወር ጀምሮ የታጠቁ ሀይሎች በተደጋጋሚ በሚፈጽሙት ጥቃት እስከ አሁን ሰማኒያ አራት ሰዎች ሲሞቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ለአካል ጉዳት መዳረጋቸውን ከወረዳው አስተዳደር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

ምንጭ:- የጀርመን ራድዮ
@tsegabwolde @tikvahethiopia