110 ሺሻ ቤቶች ተዘጉ‼️

በፍቼ ከተማ 110 የሚሆኑ የሺሻ ማጨሻ ቤቶች #መዝጋቱን የከተማው ፖሊስ አስታወቀ።

የከተማው ፖሊስ የኮሚኒቲ ፖሊሲንግና ወንጀል መከላከል ኃላፊ ኢንስፔክተር #ደረጄ_ፈዬ ለኢዜአ እንደገለፁት የሺሻ ማጨሻ ቤቶቹ ሰሞኑን እንዲዘጉ የተደረገው ህብረተሰቡ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት ነው፡፡

ፖሊስ የህብረተሰቡን ጥያቄ መሰረት በማድረግ ባለፉት አስር ቀናት ህግን ተከትሎ ባደረገው አሰሳ 97 የሺሻ መጠቀሚያ እቃዎችንና ድርጊቱን ሲፈፅሙ የነበሩ ሰዎችን እጅ ከፍንጅ መያዙን ገልፀዋል፡፡

እንዲሁም የማደንዘዝ አቅማቸው ከፍተኛ የሆኑ ሲጋራዎችንና ሌሎች ቁሳቁሶችን በኤግዚቢትነት መያዙንና በፍርድ ቤት ውሳኔም እንደሚወገዱ ተናግረዋል፡፡

ቤቶቹ የተዘጉት በህጋዊ የቡናና የሻይ ማፍላትና መሸጥ ሰበብ ህገወጥ ድርጊት ሲፈፅሙና ሲያስፈፀሙ በመያዛቸው መሆኑን ኢንስፔከተሩ ገልፀዋል።

የከተማው አንዳንድ ወጣቶች በሃሽሽና በሌሎች ደባል ሱሶች በመጠመድ የሚፈፅሙት ህገወጥ ድርጊት ከጊዜ ወደ ጊዜ አየጨመረ መምጣቱን ሃላፊው ጠቅሰው ሁኔታውን ለመከላከል ፖሊስ ባደረገው ጥረት የከተማው ሕዝብ ያሳየው ትብብር የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል።

በከተማው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከመቶ በላይ ሸሻ ቤቶች የተዘጉ ሲሆን ቁሳቁሳቸው በፍርድ ቤት ትዕዛዝ መወገዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

ፖሊስ ወጣቱን በተለያየ መድረክ በማሰባሰስብ በወንጀል አስከፊነትና አደነዛዠ እፅ ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት እየሰጠ እንደሚገኝም ተናግረዋል።

ፖሊስ በትምህርት ቤቶች አቅራቢያ የሚገኙ ሽሻና ጫት ቤቶች መዝጋቱ ለሰላማዊ የመማር ማስተማር ሰራ የሚያግዝ መሆኑን የገለፁት የአብዲስ አጋ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርእሰ መምሀር አቶ ሃይሉ ታፈሰ ናቸው።

ይህም የአንድ ወቅት ዘመቻ ሳይሆን ክትትልና ደጋፍ በማድረግ ለዘለቄታው እንዲቆም ማድረግን ታሳቢ ያደረገ መሆን እንዳለበትም አሳስበዋል።

ከህብረተሰቡ ጋር በመተባበር ፖሊስ ሽሻ ቤቶችን በመዝጋቱ፣ በከተማው አንዳንድ አካባቢዎች ሲፈፀም የነበረው የስርቆት፣ የዘረፋና የድብደባ #ወንጀል ይቀንሳል የሚል እምነት እንዳላቸው የገለፁት ደግሞ በቀበሌ 04 በንግድ ስራ የሚተዳደሩት አቶ ሙሃባ ነጂብ ናቸው።

ምንጭ፦ ኢዜአ
@tsegabwolde @tikvahethiopia