ፈጣሪ ማስተዋል ይስጠን!

ዛሬ አንዳንዶች ባሉበት ሆነው ተዋልደው ተከባብረው የሚኖሩ #ብሄሮችን ለማጋጨት ይሞክራሉ፤ ሰዎችን ለጥል ያነሳሳሉ፤ እርስ በእርስ እንዲገዳደሉ ይቀሰቅሳሉ፤ በፍቅር የሚኖረውን ህዝብ ይከፋፍላሉ፤ ወጣቱ ሰብዓዊነቱን እንዲረሳና ብሄሩን እንዲያስቀድም በሙሉ አቅማቸውን ቀን ማታ ይቀሰቅሳሉ፤ ህግን ስርዓትን አክብሮ የሚኖረውን ወጣት ተነሳ ግደል፣ አጥፋ እያሉ ይመክራሉ፤ ብሄር መስደብ፣ ማንቋሸሽ ባህል እንዲሆን ይሰራሉ፤ ወጣቱን ሳያውቀው ከፈጣሪው ጋር ያጋጫሉ፤ የተወሰነ ሰው ባጠፋው ወንጀል ሚሊዮኖች መሰደብ፣ መገለል እንዳለባቸው ምንም ሳይፈሩ ይናገራሉ።

እንዲህ የሚያደርጉ ሰዎች ብዙዎቹ ከራሳቸው ጋር የተጣሉ፣ ሰውነታቸውን የረሱ፣ ፈጣሪን የካዱ፣ እውቀት የራቃቸው፣ ማስተዋል ያልፈጠረባቸው ናቸው።

ዛሬ በብሄሮች መካከል እሳት ለመለኮስ የሚጥሩ ሰዎች የለኮሱት እሳት እራሳቸውን እንደሚያነድ፤ እራሳቸውን እንደሚፈጅ ፍፁም አላስተዋሉም።

የዛሬዎቹ የጥላቻ ነጋዴዎች #ነገን አሻግረው አላዩም። ይህ ህዝብ በጣም የተዋሀደ፣ እርስ በእርሱ የተዋለደ ህዝብ ነው። ዛሬ ብሄር ለይተው በለው የሚሉት ተራ ግለሰቦች ነገ የራሳቸው ወንድም እና እህቶች ካሉበት አካባቢ ወጥተው እንደሚማሩ ረስተውታል፤ ከአንዱ ከተማ ወደ ሌላው ከተማ ሄደው የሚማሩትን #ምስኪን ልጆችን ረስተዋቸዋል።

የብሄር ተቆርቋሪዎች መስለው የራሳቸውን ወንድም እና እህቶች የሚያጋድሉት ሰይጣኖች ናቸው። ወንድም እና እህቶቻቸው በሄዱበት ቦታ ሁሉ በቋንቋቸውና በባህላቸው እንዲሸማቀቁ ሊያደርጓቸው ያሰቡ እነሱ እውነትም የዚህች ሀገር ጠላቶች ናቸው።

እናተ የጥላቻ ነጋዴዎች...

◾️ነገ ምስኪን እህት ወንድሞቻችሁ የት ተመድበው እንደሚማሩ አታውቁምና ከጥላቻ ይልቅ ፍቅርና አንድነትን አስተምሩ።

◾️ነገ ምንም የማያውቀው ሰራተኛ የዕለት ጉርሱን ፍለገ የትኛው ከተማ እንደሚሄድ አታውቁም ከጥላቻ ይልቅ ፍቅርና አንድነትን አስተምሩ።

ሁሉም ሰላምን የሚወድ፤ ሀገሩን የሚወድ ሰው በብሄር ማካከል ጥላቻ እንዲኖር የሚሰሩትን ያግልላቸው። የማዕበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች የጥላቻ ገፆች እና ግለሰቦችን #Block አድርጓቸው።

ለወጣቱ ፍቅርን እናውርሰው። ፍቅር እንደሚያሸንፍ ደጋግመን እንገረው። #ሰውነት ከሀገር፣ ከብሄር፣ ከዘር እንደሚበልጥ እንገረው።

ፈጣሪ ማስተዋልን ይስጠን!
ፀጋአብ ወልዴ-ኢትዮጵያ
@tsegabwolde @tikvahethiopia