#update የመግቢያ ጊዜ⬇️

የ2011 የትምህርት ዘመን የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የመግቢያ ጊዜ በትምህርት ፍኖተ- ካርታ ውይይት ምክንያት #መራዘሙን የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

በአዲሱ የትምህርት ፍኖተ-ካርታ በሚደረገው ውይይት ምክንያት የ2011 ዓ.ም የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ጊዜ ላልተወሰነ ጊዜ መራዘሙን የሚኒስቴሩ የኮሚኒኬሽን ዳይሬክተር ወይዘሮ #ሀረግ_ማሞ አስታውቀዋል።

መንግሥት በቅርቡ አዲስ ባዘጋጀው ረቂቅ የትምህርት ፍኖተ-ካርታ ላይ የተጀመረው ውይይት ላይ ተጨማሪ ግብዓት ማሰባሰቢያ ውይይት ስለሚደረግ ቀደም ብሎ ተላልፎ የነበረው የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ጥሪ መራዘሙን ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል።

ዩኒቨርሲቲዎች ከመምህራኖቻቸው እና ከአስተዳደር ሠራተኞቻቸው ጋር በረቂቅ ፍኖተ-ካርታው ላይ ውይይት አድርገው ሲያበቁ ከጥቅምት ወር መጀመሪያ አንስቶ እንደ የዩኒቨርሲቲዎቹ መርሀ-ግብር የተማሪዎች መግቢያ ጥሪ ይደረጋል ተብሎ የቆየ ቢሆንም ውይይቱ እየተካሄደ በመሆኑ ምክንያት ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል።

ባለፉት ሁለት ወራት ውይይት ሲደረግበት የቆየው የትምህርት ፍኖተ-ካርታ ረቂቅ ጥናት ግብዓት ማሰባሰብ ሂደት ከአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ማኅበረሰብ አባላት ጋርም በዛሬው ዕለት በመላ አገሪቱ ውይይት እየተደረገበት ይገኛል።

በመሆኑም ውይይቱ ሲጠናቀቅ በማዕከል በኩል ለሁሉም የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች #ጥሪ እንደሚደረግ ተናግረዋል።

በአገር አቀፍ ደረጃ የተዘጋጀው የትምህርትና ስልጠና ፍኖተ-ካርታ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ያለመ ሲሆን ለተግባራዊነቱ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር #ውይይት እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል።

ምንጭ፦ ኢዜአ
@tsegabwolde @tikvahethiopia