#update ሰመጉ⬇️

ሰሞኑን በአዲስ አበባ ከተማ የተካሄደው #ጅምላ እስር በመንግሥት ሙሉ ማብራሪያ ሊሰጥበት እንደሚገባ፣ የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ጥያቄ አቀረበ፡፡ #ሰመጉ ይህን ጥያቄ ያቀረበው ዓርብ መስከረም 18 ቀን 2011 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ነው፡፡

ሰመጉ በመግለጫው ምንም እንኳን ፖሊስ ከተማዋን #ለማረጋጋት ዕርምጃ መውሰዱ #ተገቢ እንደሆነ ቢያምንም፣ ‹‹ከሕግ አግባብ ውጪ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መጠነ ሰፊ እስራት መፈጸሙ፣ የጅምላ እስራቱ ሰላማዊ ዜጎችንም ጭምር ዒላማ ማድረጉ፣ ጥቂት የማይባሉ ታሳሪዎች ላይ ፖሊስ ድብደባ መፈጸሙ፣ በሕግ ወንጀል  እንዳልሆነ በግልጽ ባልተደነገጉ ሥፍራዎች ያገኛቸውን ዜጎች ማሰሩ፣ ከሕግ አግባብ ውጭ ከምሽቱ 12 ሰዓት በኋላ እስራቶቹ መፈጸማቸው፣ እንዲሁም ሰላማዊውን ሕዝብ ጭንቀት ውስጥ በከተተና ግልጽነት በጎደለው ሁኔታ የጅምላ እስሩን መነሻ ምክንያትና የታሳሪዎችን ዕጣ ፈንታ በፍጥነት ለሕዝብ ይፋ አለማድረጉ››፣ የፖሊስን ዕርምጃ ሕጋዊነት ጥያቄ ውስጥ የሚጥል እንደሆነ አስታውቋል፡፡

የእስሩን ገፈት የቀመሱ ግለሰቦች፣ ‹‹የተቀናቃኝ ፓርቲዎች አመራሮች ወደ አገር ቤት ሲመለሱ የአቀባበል ዝግጅቱን ለምን #አስተባበራችሁ? ለምን የፓርቲዎች ደጋፊዎች ሆናችሁ? የሚሉና ተመሳሳይ የምርመራ ጥያቄዎች እንደቀረበላቸው›› ሰመጉ ከታሳሪዎች ባገኘው መረጃ መሠረት ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡

ፖሊስ ታሳሪዎቹን በመደበኛ ፖሊስ ጣቢያዎች ለማቆየት ያልቻለበትን ምክንያት ግልጽ አላደረገም የሚለው ሰመጉ፣ ይህ የፖሊስ ድርጊት ‹‹የዜጎችን ሕገ መንግሥታዊ መብት በግልጽ የጣሰ በመሆኑ፣ ከሕግ አግባብ ውጪ የተያዙ፣ ክስ ሳይቀርብባቸው ወይም ሳፈረድባቸው የታሰሩ ዜጎች እንዲፈቱ፤›› በማለት ጥሪውን አቅርቧል፡፡

አገሪቱ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ውስጥ በነበረችበት ወቅት በተለያዩ ወታደራዊ ካምፖች ታስረው የነበሩ ዜጎች ይደርስባቸው የነበራት የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ትውስታ ከአዕምሮ ባልጠፋበት በዚህ ወቅት፣ ለሥልጠና በሚል ሰበብ መንግሥት ዜጎችን ወደ ወታደራዊ ካምፕ በማጋዙ ለሌላ ዙር መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳያጋልጣቸው የሚል ሥጋቱንም ሰመጉ ገልጿል፡፡

‹‹በሁከትና በግርግር ውስጥ ተሳትፈዋል በሚል በሕግ ሥር የሚገኙ ዜጎች ሰብዓዊ መብታቸውን ተጠብቆ የመያዝ መብታቸው እንዲከበር፣ በቤተሰቦቻቸው፣ በወዳጆቻቸውና በሕግ አማካሪዎቻቸው የመጎብኘት መብታቸው እንዲጠበቅላቸው፣ እንዲሁም #ክስ ያልተመሠረተባቸው ዜጎች በፍጥነት እንዲለቀቁ፤›› ሲል ሰመጉ ጥያቄውን አቅርቧል፡፡

ምንጭ፦ ሪፖርተር
@tsegabwolde @tikvahethiopia