TIKVAH-ETHIOPIA
1.48M subscribers
56.3K photos
1.4K videos
202 files
3.83K links
ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ
Download Telegram
በአዲስ አበባ የ2016 ትምህርት ዘመን የመማር ማስተማር ሒደት መስከረም 07/2016 ዓ.ም ይጀምራል።

በአዲስ አበባ ከ1.2 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎችን የሚያስተምሩ ከ2,200 በላይ የትምህርት ተቋማት መኖራቸውን ከመዲናዋ የትምህርት ቢሮ የተገኘ መረጃ ያሳያል።

በሌላ በኩል በኦሮሚያ ክልል ' ኪድ -ኢንተርፕረነርሺፕ ' የተሰኘ ከቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ጀምሮ ህጻናትን በክህሎት ለማነጽ የተዘጋጀ መጽሐፍና ' በርኖታ ሰፉ ' የተሰኘ ከ1ኛ ክፍል እስከ 6ኛ ክፍል የሚሰጥ የግብረ ገብ ትምህርት መፅሃፍ ተመርቋል።

በዚህም ፤ ' ኪድ-ኢንተርፕርነርሺፕ ' እና ' በርኖታ ሰፉ / የግብረ ገብ ትምህርት ' ይሰጣል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#Update በሊቢያ ባጋጠመው የጎርፍ አደጋ የሟቾች ቁጥር ወደ 5000 ሺህ ሳይጠጋ እንደማይቀር እየተነገረ ነው። 10 ሺህ ሰዎችም ያሉበት አይታወቅም ተብሏል። የሊቢያ ቀይ ጨረቃ እስካሁን ባለው 2,084 ሰዎች መሞታቸውን አረጋግጫለሁ ብሏል። በሊቢያ የሚገኘው ቀይ መስቀል በበኩሉ የገቡበት የማይታወቁ ሰዎች 10 ሺህ ደርሰዋል ሲል አሳውቋል። መቀመጫውን በ ' ምስራቃዊ ሊቢያ ' ያደረገው አስተዳደር…
#Update

" ዳንኤል " የተባለው አውሎ ንፋስ በፈጠረው ከባድ ጎርፍ በሊቢያ የሞቱ ሰዎች 20 ሺህ ገደማ ሊደርሱ እንደሚችሉ ቢቢሲ ዘግቧል።

በ10 ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎች ደግሞ እስካሁን ያሉበት አልታወቀም።

ደርና የተባለችው ከተማ ትልቁ ጉዳት የደረሰባት ሲሆን አብዛኛው የከተማዋ ክፍል በውሃ ተወስዷል።

በሌላ በኩል ፤ አርብ በሞሮኮ በደረሰው ከባድ የመሬት መንቀጥቀጥ የሞቱ ሰዎች 3000 ገደማ መድረሳቸው የተነገረ ሲሆን አሁንም ድረስ በህይወት ያሉ ሰዎች ካሉ በሚል ፍለጋ እየተደረገ ነው። በአደጋው ሰዎችን በህይወት የማግኘቱ ነገር እጅግ የመነመነ ነው ተብሏል።

በአደጋው ከ5,530 በላይ ሰዎች ተጎድተዋል።

@tikvahethiopia
" ክትትል እየተደረገ ነው ፤ በወረርሽኝ ምክንያት ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች አሉ " - ወ/ሮ ሰላማዊት ግርማቸው (በኢሰመኮ የሰሜንና ማዕከላዊ ሪጅን የክትትልና ምርመራ ዳይሬክተር)

በኦሮሚያ ክልል፣ ሸገር ከተማ በማቆያና በፓሊስ ጣቢያዎች የሚገኙ ወገኖች እንዳሉና በእነዚህ ወገኖች የሰብዓዊ መብት ሁኔታ ላይ ክትትል እያደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገለጸ።

ጎዳና ላይ ተይዘው በጅምላ በሸገር ከተማ " ገላን ሲዳማ አዋሽ " እንዲሁም በፖሊስ ጣቢያዎች ውስጥ ታስረዋል የተባሉ ንጹሐንን ሰዎችን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ በተመለከተ በዚህ ሳምንት ክትትል እየተደረገ መሆኑን ኮሚሽኑ ለቲክቫህ ገልጿል።

በኮሚሽኑ ሰሜንና ማዕከላዊ ሪጅን የክትትልና ምርመራ ዳይሬክተር ሰላማዊት ግርማቸው ለቲክቫህ በሰጡት ቃል ፤ ንጹሐን ሰዎች በፓሊስ ጣቢያዎች ውስጥ መታሰራቸውን በተመለከት ጥቆማ እንደደረሳቸው አስረድተው " መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም በቡራዩና በአሸዋ ሜዳ ክትትል እያደረግን ነው " ብለዋል።

በተጨማሪም በ " ገላን ሲዳማ አዋሽ " ከጎዳና ላይ የተያዙና ሌሎችም ሰዎች በጅምላ በሚገኙበት ማቆያ ወረርሽኝ ተከስቶ እንደነበር ጠቁመዋል።

የተከሰተውን ወረርሽኝ ምንነት በዝርዝር ያልገለፁት ዳይሬክተሯ ፣ ከዚህ በፊት ከጎዳና ላይ የተያዙ ከ4,000 በላይ ሰዎች ይገኙበት በነበረ ማቆያ ተከስቷል በተባለው ወረርሽኝ ጉዳይ ከጤና ቢሮ ጋር በመሆን ክትትል መደረጉን ተናግረዋል።

በማቆያ ውስጥ በሚገኙ ሰዎች ተከሰተ በተባለው ወረርሽኝ በርካታ ሰዎች እንደሞቱ በተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያዎች እየተዝዋወረ ይገኛል።

በወረርሽኙ ሕልፈተ ሕይወት እንዳጋጠመ እና እንዳላገጠመ ኢሰመኮ ክትትል አድርጎ እንደሆን እንዲያብራሩ ከቲክቫህ ጥያቄ የቀረበላቸው ሰላማዊት፣ " ክትትል እየተደረገ ነው። አሁን ወረርሽኙ በቁጥጥር ሥር ውሏል። ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች አሉ። በሕክምና ላይ ደግሞ ያሉ አሉ " ብለዋል።

የሟቾቹን ሙሉ ቁጥር ሙሉ ሪፓርቱ ተጠናቅሮ ሲጠናቀቅ በቅርቡ ይፋ እንደሚያደርጉ ዳይሬክተሯ አስረደተዋል።

መኖሪያ ቤት የሌላቸውና ከጎዳና ላይ በጀምላ ተይዘው በገላን ሲዳማ አዋሽ በሚገኝ ማቆያ ከሚገኙት መካከል መኖሪያ ቤት ያላቸው ሰዎችም ከመንገድ ላይ በጅምላ ተወስደው እንደተገኙ ዳይሬክተሯ ተናግረዋል።

መኖሪያ ቤት እያላቸው በጸጥታ ሃይሎች  በጅምላ ተይዘው ማቆያ የተገኙ 29 ንጹሐን ሰዎች ኮሚሽኑ እንዲለቀቁ ማስደረጉንም ገልጸዋል።

አክለውም፣ በአጠቃላይ በማቆያው እስከ 4,000 የሚሆኑ የጎዳና ተዳዳሪዎች ተይዘው እንደነበር፣ አብዛኛዎቹ ተለቀው ወደ 1,500 የሚሆኑ ሰዎች እንደቀሩና እንደሚለቀቁ ገልጸዋል።

ሲዳማ ክልል ተወስደው እንደታሰሩ ሲነገርላቸው የነበሩ ሰዎችን በተመለከተም ኮሚሽኑ ተከታዩን ማብራሪያ ሰጥቷል።

" ወደ ሲዳማ አፓስቶ ትምህርት ቤት የሄዱትም ካለፈው አሥር ቀን ጀምሮ በጣም በቅርበት ነው ስንከታተል የነበረው " ያሉት ዳይሬክተሯ፣ " ከነሐሴ 28 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ጳጉሜ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ለቀዋቸዋል " ብለዋል።

አክለው፤ " ወደየ መጡበት ከተሞች እንዲመለሱ ተደርጎ ሂደው ንብረታቸውን ተረክበዋል። የተለቀቁት ወደ 1,400 የሚሆኑ ሰዎች ናቸው " ብለዋል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ በዚህ ጉዳዮች ላይ ተጨማሪ መረጃዎችን እየተከታተለ የሚያቅረብ ይሆናል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
#Earthquake ትግራይ ድረስ ንዝረቱ የተሰማ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከሰተ። ከአንድ ሰዓት በፊት በሬክተር ስኬል 5.0  የተለካ የመሬት መንቀጥቀጥ ከኤርትራ፣ አስመራ በ59 ኪሎሜትር ርቀት መከሰቱን የአሜሪካ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ ሪፖርት አድርጓል። የመሬት መንቀጥቀጡን የሚመለከት ዝርዝር መረጃዎች በሰዓታት ውስጥ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል። የመሬት መንቀጥቀጡን በተመለከተ አንድ ኤርትራዊ ፤ " ከደቂቃዎች…
" የደረሰ ጉዳት የለም " - የኤርትራ ማዕድንና ኢነርጂ ሚኒስቴር

የኤርትራ ማዕድን እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ትላንት ምሽት በሬክተር ስኬል 5.0 የተመዘገበ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከስቶ እንደነበር አረጋግጧል።

የመሬት መንቀጥቀጡ ከመሬት በታች 10 ኪሎ ሜትር ጥልቀት እንደሆነ አመልክቷል።

ዋና መነሻው (epicenter) ከምፅዋ በስተደቡብ 41 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ መሆኑን ገልጿል።

ሚኒስቴሩ ፤ የመሬት መንቀጥቀጡ በአዲ-ቀይህ፣ ጊንዳ፣ ምፅዋ እና አስመራ በተለያየ መጠን መሰማቱን አመልክቶ በዚህም ጉዳት እንዳልተመዘገበ አሳውቋል።

በኤርትራ መነሻውን ያደረገው በሬክተር ስኬል 5.0 የተመዘገበው የመሬት መንቀጥቀጥ ንዝረቱ ትግራይ የተለያዩ ከተሞች ድረስ መሰማቱን በትላንትናው ዕለት በተለያዩ የትግራይ ከተሞች የሚገኙ የቲክቫህ ቤተሰቦቻችን መግለፃቸው ይታወሳል።

@tikvahethiopia
TIKVAH-ETHIOPIA
ፈረንሳይ iPhone 12ን አገደች። ፈረንሳይ iPhone / አይፎን 12 ከልክ በላይ ጨረራ ያመነጫል በሚል የስልኩ ሽያጭ እንዲታገድ አዘዘች። ትናንት መስከረም 1/2016 ዓ.ም. የሬዲዮ ሞገዶችን የሚቆጣጠረው አካል አይፎን 12 ከሚፈቀደው የኤሌክትሮማግኔቲክ ራዲዬሽን በላይ እያመነጨ ነው ብሏል። ተቋሙ ስልክ አምራቹ አፕል ችግሩን በሚያደርጋቸው ማሻሻያዎች በአስቸኳይ የማይቀርፍ ከሆነ በመላው አገሪቷ…
#ቴክኖሎጂ #iPhone

ፈረንሳይ " አይፎን 12 " ን ከልክ በላይ ጨረራ ያመነጫል በሚል የስልኩ ሽያጭ እንዲታገድ ማዘዟን ተከትሎ የአውሮፓ ሀገራት ጉዳዩን እየተከታተሉ ነው ተብሏል።

ፈረንሳይ አይፎን 12ን ያገደችው ከሚፈቀደው የኤሌክትሮማግኔቲክ ራዲዬሽን በላይ እያመነጨ ነው በማለት ሲሆን ይህን እገዳ ተከትሎ ፦
- ቤልጂየም፣
- ኔዘርላንድስ
- ጀርመን ጉዳዩን በልዩ ሁኔታ እየተከታተሉት ነው ተብሏል።

የጀርመን ባለሥልጣናት ሁኔታው ወደ አውሮፓ አቀፍ እርምጃዎች ሊመራ ይችላል ብለዋል።

የቤልጂየም መንግስት እ.ኤ.አ. በ2020 ለመጀመሪያ ጊዜ የተለቀቀው አይፎን 12 #የጤና_ጠንቅ መሆኑን እንዲገመግም ለተቆጣጣሪ አካል መመሪያ መስጠቱ ተነግሯል።

የቤልጂየም የዲጂታላይዜሽን ሚኒስትር ማቲዩ ሚሼል ፤ " ዜጎቻችን በሙሉ ደህንነታቸው የተጠበቀ እና ከማንኛውም አደጋ የተጠበቁ እንዲሆኑ ማድረግ የእኔ ኃላፊነት ነው። ጤና መቼም ቢሆን ችላ ሊባል የማይገባ ጉዳይ ነው። " ብለዋል።

ሁሉም የአፕል ሞዴሎችን እንዲመረምር ተቆጣጣሪውን አካል እንደተጠየቀ አመልክተዋል። ሌሎችም ብራንዶች ላይ ተመሳሳይ ስራ ይሰራል ብለዋል።

የኔዘርላንድ ዲጂታል መሠረተ ልማት ኤጀንሲ ፤ በፈረንሣይ ምርመራ ላይ በመመርኮዝ ከልክ በላይ የጨረር መጠን እንደሚያመነጭ ጥርጥር የለውም ያለ ሲሆን አፕልን እንደሚያነጋግር አሳውቋል።

ነገር ግን “ ምንም አጣዳፊ የደህንነት ስጋት የለም ” ብሏል።

የጀርመኑ BNetzA ኔትወርክ ኤጀንሲ ፤ የፈረንሣይ ምርመራ በሁሉም የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ላይ የሚተገበሩ እርምጃዎችን ሊያስወስድ የሚችል ነው ብሏል።

አፕል የፈረንሳዩን እገዳ ከሰማ በኃላ ለቢቢሲ በሰጠው ቃል ፤ አይፎን 12 የጨረራ መጠኑ በሰዎች ላይ ጉዳት እንደማያስከትል በመላው ዓለም ባሉ ተቆጣጣሪዎች እውቅና ያለው ምርት ነው ሲል ምላሽ ሰጥቷል።

በሌላ መረጃ ፤ አፕል አዲሱን " አይፎን 15 "  ከነገ ጀምሮ ማዘዝ እንደሚቻል አሳውቋል።

አዲሱ ምርት እንደየአይነቱ በተለያየ የገንዘብ መጠን ለገበያ ቀርቧል።

አይፎን 15 በስንት ዶላር ነው ለገበያ የቀረበው ?

👉 አይፎን 15 ከ$799 እስከ $1,099 (በኢትዮጵያ ብር በባንክ ቢሰላ ከ44,952 ብር እስከ 61,830 ብር ይሆናል)

👉 አይፎን 15 ፕላስ ከ$899 እስከ $1,199 (በኢትዮጵያ ብር በባንክ ቢሰላ ከ50,578 ብር እስከ 67,456 ብር ይሆናል)

👉 አይፎን 15 ፕሮ ከ$999 እስከ $1499 (በኢትዮጵያ ብር በባንክ ቢሰላ ከ56,204 ብር እስከ 84,335 ብር ይሆናል)

👉 አይፎን 15 ፕሮ ማክስ ከ$1,199 እስከ $1,599 (በኢትዮጵያ ብር በባንክ ቢሰላ ከ67,456 ብር እስከ 89,961 ብር ይሆናል)

ገንዘቡ #ዝቅተኛው እና #ከፍተኛውን ጣሪያ የሚያሳይ ሲሆን እንደ ስልኩ GB እና አይነት ይለያያል።

@tikvahethiopia
#Bank_of_Abyssinia

የአቢሲንያ ባንክን የተለያዩ አገልግሎቶች አጠቃቀም እንዲሁም ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት ከዚህ ጋር የተያያዘውን ሊንክ በመጠቀም ትክክለኛ የቴሌግራም ቻነላችንን ይቀላቀሉ።

https://publielectoral.lat/BoAEth
#SafaricomEthiopia

ዛሬውኑ *777# በመደወል የሳፋሪኮምን የድኅረ ክፍያ ጥቅል እንግዛ ፤ ፈታ ብለን እንዝናና።

#SafaricomEthiopia #FurtherAheadTogether
TIKVAH-ETHIOPIA
#Mekelle " በአምባገነን ስርአት ምክንያት መብታችን እንዲቀማ እንፈቅድም " - አቶ ዓምዶም ገ/ስላሴ በትግራይ መቐለ ከተማ " ኪዳን ንሱር በቆስ ለውጢ " በሚል መሪ ቃል ከጳጉሜን 2/2015 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት ሊካሄድ ከተጠራው ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ጋር በተያዘዘ በቁጥጥር ስር የነበሩ የተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲ ሊቃነመናብትና  ከፍተኛ አመራሮች በሙሉ መለቀቃቸው ታውቋል። የዓረና…
#Tigray

" ሰልፍ እንዳናደርግ አፈና ተደርጎብናል " ያሉ 3 የትግራይ ፓርቲዎች ከትግላችን ወደኃላ አንመለሰም አሉ።

ፓርቲዎቹ ይህን ያሉት ባወጡት የጋራ መግለጫ ነው።

የጋራ መግለጫ ያወጡት ፦

- ውድብ ናፅነት ትግራይ
- ሳልሳይ ወያነ ትግራይ
- ብሔራዊ ባይቶና ዓባይ ትግራይ ፓርቲዎች ሲሆኑ " ኪዳን ንሱር በቆስ ለውጢ " በሚል መሪ ቃል ያስተባበሩት ከጳጉሜን 2-4/2015 ዓ.ም ሰልፍ ለማድረግ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ እንደነበር አስታውሰዋል።

ፓርቲዎቹ፤ " ሃሙስ ጳጉሜን 2 ቀን 2015 ዓ.ም ሰልፉን እንዲያስተባበሩና እንዲመሩ በቆረጡ የፓለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ይሁን ፤ ያነገቡት የህዝብ ጥያቄ ለህዝቡ እንዲያደርሱ በቆራጥነት ወደ ሮማናት አደባባይ በከተቱ የህዝብ ልጆች ፤ ስልጣን ላይ ባለው ሃይል የማፈን ፣ የማሰር ፣ በድብደባ አካል ማጎደል እስከ መግደል ሙከራ የሚደርስ የጭፍጨፋ ወንጀል በመፈፀም የሰልፉ አላማ እንዳይሳካ ተደርጓል " ብለዋል።

የህዝብ ጥያቄዎች ያነገበ ሰላማዊ ሰልፍ " አመፅ ነው " በሚል የማጥቆርና ስም የማጥፋት ዘመቻ ተካሂዷል ያሉት ፓርቲዎቹ " ገዢው የትግራይ ሃይልን ህዝቡ አንቅሮ ተፍቶታል " ሲሉ ገልጸዋል።

" ህዝቡ የትግራይ ወጣት፣ የትግራይ ፓለቲካ ፓርቲዎች ያነሱዋቸውን ቀና የህዝብ ጥያቄዎች በመቀበል አደባባይ ወጥቶ ከወንድሞቹ ጎን በመሰለፍ የጨካኞች በትር በመቀበል አዲስ የፓለቲካ ባህል በትግራይ እንዲያብብ ከፍተኛ ሚናውን ተወጥቷል " ብለዋል።  

" ኪዳን ንሱር በቆስ ለውጢ " የአንድ ቀን ስራ ሆኖ የሚቆም አይደለም ያሉት ፓርቲዎቹ  በቀጣይነት እየሰፋና ጥልቀት እያገኘ የሚሄድ የትግራይ የፓለቲካ ፓርቲዎች ጠንካራ ስምረት ነው ብለዋል።

አደባባይ የወጣን የትግራይ ብሄራውያን የፓለቲካ ፓርቲዎች ትግል ወደ ኋላ የሚመልሰው የለም ብለዋል።

@tikvahethiopia
#AddisAbaba

" የክረምቱ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ያልተጠናቀቀ በመሆኑ ጥንቃቄ አድርጉ " - የአዲስ አበባ እሳትና አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን

በአዲስ አበባ ከተማ ትላንት በጣለው ከባድ ዝናብ ምክንያት ሁለት ሰዎች #በጎርፍ ተወስደው ህይወታቸው አለፈ።

ትላንት ምሽት 3:00  ሰዓት ጀምሮ ሲጥል የነበረዉን ዝናብ ተከትሎ በተፈጠረ ጎርፍ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ዳርፉር ወንዝ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ሁለት ሴቶች በጎርፍ ተወስደዋል።

ይህን ተከትሎ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞችና ጠላቂ ዋናተኞች ፍለጋ ሲያካሂዱ ቆይተው ዕድሜያቸዉ 18 ዓመት የሆኑ ሁለት ሴቶችን በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 ከተለያየ ቦታ ማግኘት ችለዋል።

የክረምቱ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ያልተጠናቀቀ በመሆኑ ኑሮአቸዉን እና እንቅስቃሴያቸዉን ወንዝ አካባቢ ያደረጉ ሁሉ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግና ከአካባቢዉ እንዲርቁ የአዲስ አበባ እሳትና አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አሳስቧል።

@tikvahethiopia
#ዓለምአቀፍ

የጣሊያኗ " ላምፔዱሳ " ደሴት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አወጀች።

አዋጁን ያወጀችው ባለፉት ሁለት ቀናት ከአፍሪካ የተነሱ ወደ 8,000 የሚጠጉ ስደተኞች ወደ ደሴቷ መድረሳቸውን ተከትሎ ነው።

ስድተኞች ከተለያዩ አፍሪካ ሀገራት ወደ ጣልያን እየገቡ የሚገኙት በጀልባ ለህይወታቸው እጅግ አስጊ በሆነ መንገድ ተጉዘው ነው ተብሏል።

አንድ ከጊኒ ተነስቶ ጣልያን የገባ ስደተኛ ፤ በሕይወት ተርፎ ጣልያን በመግባቱ ዕድለኛ እንደሆነ ተናግሯል።

ሀገሪቱ አሁን እየገቡ ያሉትን ስደተኞች ወደ ሌሎች የመቀበያ ቦታዎች ለማዘዋወር እየሰራች ነው ተብሏል።

የጣልያን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የትራንስፖርት ሚኒስትር ማትዮ ሳልቪኒ ፤  በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ስደተኞች ጣልያን መድረሳቸውን " የጦርነት አነይት ድርጊትን " ይወክላል ብለዋል።

ሚኒስትሩ " ጣሊያንን ለማተራመስ ሆን ተብሎ የተነደፈ ስልት መሆኑን እርግጠኛ ነኝ " ያሉ ሲሆን ከዚህ ሴራ ጀርባ ማን እንዳለ ለመግለፅ አልወደዱም።

" ከዚህ በስተጀርባ አንድ እቅድ እንዳለ እርግጠኛ ነኝ " ያሉት ሚኒስትሩ " ከ100 በላይ ጀልባዎች በጥቂት ሰአታት ውስጥ መድረሳቸው ድንገተኛ ሳይሆን የተደራጀ የጦርነት አይነት ድርጊት ነው። " ብለዋል።

" ይህ የሚያመጣው ተፅእኖ በላምፔዱሳ ላይ  ብቻ የሚያበቃ አይደለም ፤ ወደ ሮም፣ ሚላን፣ ቱሪን፣ ኔፕልስ፣ ፓሌርሞ ስለሚሄዱ አሳዛኝ መዘዞችን ያስከትላል። " ሲሉ ተናግረዋል።

ጣልያን ከፍተኛ የስደተኞችን ቁጥር የምታስተናግድ አውሮፓዊት ሀገር ስትሆን በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየታየው ያለው ነገር ውጥረት መፍጠሩ ተገልጿል።

በላምፔዱሳ ያለው ከመደበኛ በላይ ሁኔታ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ አስገድዷል።

ባለፉት 2 ቀናት ብቻ 8,000 ከአፍሪካ የተነሱ ስደተኞችን የቀበለችው የጣልያኗ ደሴት ላምፔዱሳ አጠቃላይ የነዋሪዎቿ ብዛት 6000 ብቻ እንደሆነ መረጃዎች ያሳያሉ።

በሌላ በኩል ፤ የጀርመን የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር በጣሊያን በኩል ወደ #አውሮፓ የገቡ አዲስ ስደተኞችን ለጊዜው መቀበል እንዳቆመ አስታውቋል።

ጀርመን እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰችው ጣልያን ባአውሮፓ ህብረት በኩል በስደተኞች ላይ የተደረሰውን ስምምነት ለማክበር ፈቃደኛ ባለመሆኗ ነው ተብሏል።

የጀርመን መገናኛ ብዙሀን እንደዘገቡት " ከፍተኛ የስደተኞች ጫና አለ " በሚል ምክንያት ጀርመን ከጣሊያን የሚገቡ አዲስ ስደተኞችን ላልተወሰነ ጊዜ መቀበል አቋርጣለች።

ፈረንሳይ በበኩሏ ወደ ግዛቷ ለመሻገር የሚሞክሩ ስደተኞች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ በመምጣቱ ከጣሊያን ጋር በሚያዋስናት ድንበር ላይ የሚገኙ የፖሊስ እና የጦር ሃይሎች ጥበቃን በከፍተኛ ሁኔታ እንደምታጠናክር ይፋ አድርጋለች።

ቪድዮ ፦ ከማህበራዊ ሚዲያዎች የተገኘ

@tikvahethiopia
#ኦሮሚያ

በመንገደኞች ላይ በተፈፀመ ጥቃት የሰዎች ህይወት ማለፉ ተነገረ።

በኦሮሚያ ክልል፣ ምስራቅ ወለጋ ዞን ጊዳ አያና ወረዳ መንገደኞችን አሳፍሮ በሚሄድ ተሽከርካሪ ላይ በደረሰ ጥቃት ህይወት መጥፋቱን እና ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች ሆስፒታል መግባታቸው ታውቋል።

ግድያው የተፈፀመው ዛሬ አርብ መስከረም 4 ቀን 2016 በ " አንዶዴ ዲቾ " የሚባል ቦታ ላይ መሆኑን ተነግሯል።

ግድያውን በተመለከተ የዞኑ አስተዳደር የፀጥታ ቢሮ ፤ " ድርጊቱ የተፈፀመው ዲቾ ላይ ነው " ያለ ሲሆን ከአንገር ጉተን ወደ ጊዳ በሚጓዝ የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ ላይ ነው ጥቃቱ የተፈፀመው " ሲል ገልጿል።

የፀጥታ ቢሮው የድርጊቱ ፈፃሚዎች " የአማራ ፅንፈኛ ታጣቂዎች " ናቸው ብሏል።

ቢሮው ፤ " በአካባቢው ጸጥታውን የሚያውኩ ታጣቂዎች አሉ። ታጣቂዎቹ በተሽከርካሪ የሚጓዙ ሰዎችን በመንገድ ላይ በማስቆም ነው ድርጊቱ የፈፀሙት " ሲል ገልጿል።

ዲቾ ላይ እስከ 30 የሚደርሱ ሰዎች እንደተገደሉ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በርካታ ዘገባዎች ተሰራጭቷል።

ሆኖም ግን የዞኑ አስተዳደር የተገደሉት አምስት ሰዎች እንደሆኑ ገልጿል።

ቃሉን ለቢቢሲ አፋን ኦሮሞ የሰጠው ተጎጂዎቹ ለህክምና የተወሰዱበት የጊዳ አያን ሆስፒታል ባለሙያ (ለደህንነቱ ስሙ ያልተጠቀሰ) በጥቃቱ የሞቱት ሰዎች ቁጥር አምስት ነው ብሏል።

ባለሙያው " በመጀመሪያ አምስት ሰዎች ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ወደ እኛ መጡ " ያለ ሲሆን እነዚህ አስቸኳይ ህክምና ካገኙ በኋላ የአራት ሰዎች አስክሬን ደረሰ ፤ ሆስፒታል ውስጥ ከነበሩት ውስጥ አንዱ በህክምና ላይ እያለ ህይወቱ አልፏል ሲል ተናግሯል።

እንደ ባለሙያው ገለጻ በህክምና ላይ የሚገኙት እና አስክሬናቸው እነሱ ጋር የመጣ ሰዎች በሙሉ #ወንዶች ናቸው።

" አሁን አራት ሰዎችን እያከምን ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ሦስቱ ከባድ ጉዳት ደርሶባቸዋል። እነሱን ለማዘዋወር ምንም ምቹ መንገድ የለም፣ ጉዳቱ ከአቅማችን በላይ ነው። የደም እጥረት አለብን  " ብለዋል ባለሙያው።

በነገው እለትም የጸጥታ ሃይሎች ተጎጂዎችን ወደ ተሻለ ህክምና መስጫ መውሰድ ከቻሉ ይህንን ለማድረግ መታቀዱንም ተናግረዋል።

በህክምና ላይ ያሉ ሁሉም የተጎዱ ሰዎች በጥይት ተመትተዋል ብለዋል።

የምስራቅ ወለጋ ዞን አስተዳደርና ጸጥታ ቢሮ በጥቃቱ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ እንደሆነ በማህበራዊ ሚዲያ የተሰራጨው ዘገባ ሀሰት ነው ብሏል።

አሁን ጥቃቱ በተፈፀመበት አካባቢ እና በሌሎች አካባቢዎች ታጣቂዎች በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጉዳትና ማፈናቀል እያደረሱ እንደሆነ የገለፀው የፀጥታ ቢሮው ታጣቂዎቹ ወደ ክልሉ አልፈው የገቡ ሳይሆን በዛው የሚንቀሳቀሱ ፤ ትናንሽ የታጠቁ ቡድኖች ናቸው ብሏል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ መረጃውን ያገኘው የ " ቢቢሲ አፋን ኦሮሞ " ነው።

NB. የሟቾች ቁጥርን በተመለከተ የሆስፒታል እና የዞን ባለስልጣናት የገለፁት ቁጥር አምስት ቢሆንም በጥቃቱ የተገደሉ ሰዎች ከ30 በላይ እንደሆነ የሚገልጹ መረጃዎች በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ ተሰራጭተዋል። አንድ የአካባቢው ነዋሪ ደግሞ ከሆስፒታል እና ከወረዳው ባለስልጣናት መረጃ በተለየ ሁኔታ የሞቱ ሰዎች 7 ናቸው ብሎ ተጨማሪ አስክሬን እየተፈለገ ነው ብሏል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ ተጨማሪ መረጃዎችን ሲያገኝ የሚያቀርብ ይሆናል።

@tikvahethiopia